የወያኔን የጥፋት መንገዶች ማክሸፍ ይጠበቅብናል !!! – ነፃነት በለጠ

 

በወያኔ/ኢሕአዴግ የሚመራዉን ስርዐት ምንነትና ማንነት በተግባርም የታየ እና ህዝቡም በሚገባ የሚያዉቀዉ ነዉ፡፡ ሆኖም ጥንቃቄ የሚያሰፈልጋቸዉን ጉዳዮች ማስገነዘብ እጅግ አስፈላጊ ነዉ፡፡ ይህ ፅሁፍ የስርዐቱን አደገኛ አካሄዶች ላይ በማተኮር፣ ሁላችንም እንድንጠነቀቅ በማስገነዘብ እና አንዳንድ እዉነታዎችን ለማሳወቅ የተዘጋጀ ጽሑፍ ነዉ፡፡ በቅድሚያ ወደ ዋናዉ ጉዳይ ከመግባቴ በፊት ስለ ወያኔ/ኢሕአዴግ መንግስት የማስተደዳር አቅም ላይ ማብራሪያ ልስጥ፡፡

የማስተዳደር አቅም ማጣት

በማርክሳዊ ሌኒናዊ አስተምህሮ መሠረት በአሁኑ ወቅት በኢትዮጲያ ህዝቡ ለለዉጥ እንዲነሳ ለማድረግ የሚያስፈልጉ ነባራዊ እና ህሊናዊ ሁኔታዎች ተሟልተዉ የሚገኙበት አብዮታዊ ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ ነባራዊ ሁኔታዎች የምንላቸዉ ለህዝቡ የሚያስፈልጉ መሰረታዊ አገልግሎቶች በበቂ ሁኔታ ተማልተዉ አለመቅረብ እና ከናካቴዉ አለመኖር፣ የኑሮ ዉድነት እየተባባሰ በመምጣቱ በየቤቱ ያለዉ ችግር ከሚገመተዉ በላይ መሆን (ብዙ ወላጆች ምግብ ሳይበሉ ወደ ስራ መሄዳቸዉ የተለመደ ሆኗል፤ ህፃናትም ምግብ ሳይበሉ በመሄዳቸዉ ራሳቸዉን መሳት በየጊዜዉ የሚደመጥ ነዉ)፣ ድርቁ ወደ ረሃብ ከመለወጡ በፊት መሰራት የነበረበት ስራ አለመሰራት (ለድግስ ቅድሚያ መስጠት)፣ የስራ አጡ ቁጥር ማሻቀብ (የድርጅት አባል ካልሆኑ የፈለገ ጥሩ ነጥብም ቢኖር እንኳ ስራ ማግኘት የማይቻል መሆኑ)፤ ውስጣዊ ፍልሰትና እና ከሀገር ዉጭ መሰደድ እየየተባባሰ መምጣት፣ ሙስና በከፍተኛ ደረጃ መስፋፋት (የተመቻቸላቸዉ ዋናኛዎቹ የሙስና ተዋናዮች በማይነኩበት የጨዋታዉ ሜዳ በነፃነት እየዘረፉ በአይናችን እያየን በአጭር ጊዜ ወደ ብልፅግና መሸጋገር) ፣ የተጠያቂነት ስርዐት አለመኖር (ጥፋት አጥፍተሃል ብሎ መጠየቅ ነዉር የሆነበት፣ ያወጡትን ህገ መንግሰት በአደባባይ መጣስ፣ የፍትህ ስርዐቱ ለህግ ልዕልና ሳይሆን ለወያኔ አገልጋይ መሆን፣ በየስራዉ ቦታ ህግን አክብሮ መስራት እየተዳከመ እና እየቀረ መገኘት እና ሌሎች ያልተገለፁትን ያጠቃልላል፡፡

ሕሊናዊ ሁኔታዎች የምንላቸዉ ህዝቡ ከፍርሃት መላቀቅና ስርዐቱን ፊት ለፊት ለመጋፈጥ መቁረጥ፣ እምቢ አልገዛም ማለት፣ የስርዐቱን አስከፊነት በጥልቀት መረዳት፣ ገዢዎች እንደቀድሞዉ መምራት አለመቻል እና የመሳሰሉት በግልፅ እያየናቸዉና እየተገበሩ የሚገኙ መሆናቸዉ ለዉጡ አይቀሬ መሆኑን ያመላክታል፡፡

በአሁኑ ወቅት በወያኔ/ኢሕአዴግ የሚመራዉ መንግስት የማስተዳደር አቅሙ የተሟጠጠ መሆኑ በግልፅ እየታየ ነዉ፡፡ በየትኛዉም የሲቪል ሰርቪስ መ/ቤት የሠራተኛዉ የመስራት ፍላጎት ከመቼዉም ጊዜ የወረደበት፣ በከተማ መስተዳድር / ክልል ጀምሮ ወደታች ባሉ የመንግሰት እርከኖች ያለዉ የስራ መጠንና የመስራት ፍላጎት ተዳክሞ ሲንቀሳቀሱ የሚገኙት ታክስ / ግብር የሚሰበስቡ፣ መታወቂያ፣ የልደት እና የሞት ማስረጃ የሚሰጡ እና አልፎ አልፎ ደንብ በማስከበር የሚሠሩ (ሊሞሰን የሚችል ነገር ሲያጋጥም) ክፍሎች ናቸዉ፡፡ በህግና በስርዐት ስራ የሚሰራበት ጊዜ ማለቁን በአይናችን እያነነዉ ነዉ፡፡ ጠያቂም ተጠያቂም የሌሉበት እና ወያኔ/ኢሕአዴግ አተኩሮ እየተፍጨረጨረ ያለዉ ዕድሜዉን እንዴት እንደሚያራዝምና ለዕድሜ ማራዘሚያ የሚጠቅሙ ስልቶችን ከመድረክ በስተጀርባ በጥቂት የስርዐቱ ሰዎች እየጎነጎነ መሆኑ ነዉ፡፡

ከዚህ ቀጥሎ ያለዉ ጽሁፍ የሚያተኩረዉ በወያኔ እየተደረጉና ወደፊት ሊያጋጥመን የሚችለዉን እኩይ ተግባራት ህዝቡ አስቀድሞ በመገንዘብ ለስርዐቱ መሳሪያ ሆንን ተግባራዊ እንዳናደርገዉ እና አደገኛ ጥፋቶችን እንዳንፈፅም  ለማስገነዘብ ነዉ፡፡

  1. ህዝቡን በዘር ማጋጨት
ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን በወያኔ በግፍ መፈናቀልን አስመልክቶ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ በቅርቡ የሰጡትን ጋዜጣዊ መግለጫ በሚመለከት የተሰጠ የግል አስተያየት

ላለፉት 24 ዓመታት ወያኔ/ኢሕአዴግ ላይ ታች ሲል የነበረዉ ዘርንና ሃይማኖትን ለዕድሜዉ ማራዘሚያ አገልግሎት እንዲሰጡት ሲያዘጋጃቸዉና ሲተግብራቸዉ እንደነበር ሁሉም የሚያዉቀዉ ነዉ፡፡ በተለይ ሁለቱን የዘር ግንዶች፡ ኦሮሞ እና አማራን እርስ በርስ ለማጋጨት እሰከዛሬም እየተሞከረ ያለ ሴራ ነዉ፡፡ በሁለቱ የዘር ግንዶች ሳይወሰን በተለያዩ የዘር ግንዶች መካከል መናቆር ወያኔ ስልጣን ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ እንደቀጠለ ነዉ፡፡ በመካከላችን በሚነሳ ግጭት በልዩነቱ አገዛዙ ዕድሜዉን ለማራዘም እየተጠቀመበት ይገኛል፡፡ በተለይ ፊደል የቆጠርነዉ ዜጎች አምነንበት ይሁን ሳናምንበት ለወያኔ መሳሪያ ሆንን ለማገልገል ላይ ታች የምንል አለን፡፡ በሁሉም  የዘር ግንዶች አለመተማመን እንዳይኖር ማድረግ፣ አንዱ አንዱን እንደናቀ አደርጎ ማራገብ፣ ሰዎችን ከሰፈሩበት ቦታ ማፈናቀል፣ ታሪክን በማጣቀስ ለልዩነት ምክንያት የሚሆኑ ነገሮች መድረክ ተሰጥቷቸአዉ እንዲራገቡ እና በሌላ ጎን የመተጋገዝ፣ የመተባበር እና ለጋራ ዓላማ የመነሳት ጉዳይ ቦታ እንዳይኖረዉ መንገዱን በማመቻቸት በጋራ እንዳንታገል ተንኮል እየተሰራ ነዉ፣ ካላከሸፍነዉ ለእኛም ሆነ ለሀገሪቱ አይበጅም፡፡

 

በተለይ ወያኔ የህዝብ ቁጥራቸዉ ከፍተኛ የሆኑት ኦሮሞና አማራ በመካከለቸዉ ግጭት እንዲኖር የተለያዩ ስልቶችን ስራ ላይ ያዉላል፡፡ በተለይ በወያኔ ተላላኪ በሆነዉ በኦህዴድ ካድሬዎች አማካኝነት ስስ የሆኑ ጉዳዮችን በመነካካት ልዩነቱን ማጋጋል፣ ታሪክ በማጣቀስ ግጭት መለኮስ፣ በኦሮሚያ ዉስጥ የሚኖሩ ኦሮሞ ያልሆኑትን ከቦታቸዉ እንዲፈናቀሉ ማድረግ፣ በተለያዩ የሶሻል ሚዲያዎች አንዱን ዘር የሚያንቋሽሽ ጽሁፎችን ማዉጣት (ወያኔ ሆን ብሎ ቀጥሮ ያሰማራቸዉ በዚህ መስመር ቀጥለዉበታል) እነዚህና ሌሎች በመርዝ የተለወሱ መንገዶችን ተግባራዊ ለማድረግ ወያኔ  ወደኃላ እንደማይል ልናስተዉል ይገባል፡፡

 

ሰለዚህ ኦሮሞዉ፣ ከንባታዉ፣ ትግሬዉ፣ አማራዉ፣ አፋሩ፣ ሱማሌዉ፣ አኝዋኩ፣ ወላይታዉ፣ ኑዌሩ፣  … ወዘተ ሆነ ሌላዉ የተማረ፣ ያልተማረ ገጠሬ ሆነ ከተሜ ይህንን መሰሪነት በእንጭጩ ካልቀጨነዉ ተመልሶ እሳቱ የሚለበልበን እኛኑ እራሳችን ነዉ፡፡ ኢትዮጲያ በጋራ ሆነን ሰንሰለፍ ብቻ ነዉ ሰላም የሰፈነባት፤ ህዝብን የሚያስቀድም መንግሥት መመስረት እና የተሻለች ሀገር መገንባት የምንችለዉ፡፡ መነታረክ እና መበጣበጥ ለማናችንም ሳይጠቅም ለግፍ አገዛዝ በመዳረግ ለወያኔ እድሜ ማራዘሚያ መሳሪያ ሆንን እናገለግላለን፡፡ ይህንን አስከፊ ሁኔታ በሀገራችን እንዳይከሰትና ህዝቦች ነፃነታቸዉ ተከብሮ ፣ በሰላም በብልፅግና እንዲኖሩ ልዪነትን ከማራገብ ተቆጥበን በአንድነት በመንቀሳቀስ ለዉጡን እዉን ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡

 

  1. ሃይማኖትን መሣሪያ በማድረግ ህዝቡን ማጋጨት

የሃይማኖት ጉዳይ ሌላዉ ለስልጣን ማራዘሚያነት የወያኔ ስርዐት እየተጠቀመበት ያለ መንገድ ነዉ፡፡ በኦፊሴል ኢትዮጲያ ሃይማኖት የልዩነት መሳሪያ ሳይሆን የብዝሃነት ምልክት ነዉ ይበል እንጂ በስልጣኑ ላይ አደጋ የሚደርስ መሆኑን ካወቀ በክርስትና እና በእስልምና አማኞች መካከል ልዩነት በማራገብ አርስ በርሳችን እንድንፋጅ አያደርግም ማለት ሞኝነት ነዉ፡፡ ለዘመናት በሁሉም ሃይማኖቶች መካከል በመተሳሰብ ተጠብቆ የቆየዉን ግንኙነት (የዚህ ጽሁፍ ፀሀፊ ከልጅነቱ ጀምሮ ያደገበት እና ያየዉ እዉነታ ነዉ) ለማደፍረስ

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአደዋ ድል በተሃድሶና በኢንላይተንሜንት መነፅር ሲታይ ! -  ፈቃዱ በቀለ(ዶ/ር)

 

  • የየእምነቶቹን አማኞች (ስሜታዊነት የሚያጠቃቸዉን፣ ለጥቅም ሲሉ ከማድረግ የማይቆጠቡትን …) በመጠቀም እርስ በእርስ እንድንጣላ ለማድረግ ይሞክራል፣
  • የእምነት ቤቶችን ለመገንባት የሚያስችል ቦታ አሰጣጥ ላይ አንዱን ቦታ ለሁለት / ለሶስት ሃይማኖቶች በመስጠት ግጭት እንዲቀሰቀስ እና ልዩነቱ እንዲሰፋ ይደረጋል፣
  • ቅዱሳን መጻህፍትን በመፀዳጃ ቤት አካባቢ ተቀደዉ እንዲጣሉ በማድረግ ነገሮች እንዲጦዙ ይደረጋል፣ በተለይ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተፈጻሚ እንዲሆን ሙከራ አይደረግም ማለት ወያኔን አለማወቅ ነዉ፣
  • በየእምነቱ ማምለኪያ ቦታዎች የሌላዉን እምነት የሚያንቋሽሽ ቅስቀሳ እንዲካሄድ ይደረጋል… ወዘተ

ከላይ የተዘረዘሩትና እና ሌሎች ተንኮሎች በስርዐቱ ሰዎችና ተላላኪዎች ሊፈፀም እንደሚችል በመረዳት ከስሜታዊነት ወጥተን እና ጅምላ ድምዳሜ ላይ ከመድረሳችን በፊት ነገሩን ከስሩ በመፈተሸ እንደዚህ ያለዉን ሴራ ለሀገራችን ዉድቀት ምክንያት ከመሆኑ በፊት ለማክሸፍ ነቅተን መጠበቅ አለበን፡፡

  1. የትግራይን ህዝብ ከሌላዉ ህዝብ ጋር ለማጋጨት መሞከር

ቀደም ባሉት ጊዚያት እንደሚታወቀዉ ወያኔ የፖሊቲካ ስልጣኔ አደጋ ላይ ነዉ ብሎ ባመነበት ወቅት የትግራይን ህዝብ ከጥቂት የስርዐቱ ተጠቃሚ የህወሃት አባለት እና አጃቢዎቻቸዉ ጎን እንዲሰልፍ የተለያዩ መሰሪ ስልቶችን ሲጠቀም ነበር ወደፊትም ይጠቀማል፡፡ ለምሳሌ ህወሃት ለሁለት በተሰነጠቀበት ወቅት (ሁለተኛዉ ህንፍሽፍሽ የሚሉት) እና በ1997 ምርጫ ተከትሎ በነበረዉ ወቅት የትግራይን ህዝብ በተለይ ወጣቶችን በመቀስቀስ ከሌላዉ ወንድሞቹና እህቶቹ ከሆኑት የኢትዮጲያ ህዝብ ጋር ለማጋጨት ብዙ ተደክሞአል፡፡ አሁንም ይህንን የተንኮል መንገድ ለመተግበር ወያኔ ወደኃላ  ስለማይል ስልቱን በመቀያየር ለኢትዮጲያ አንድነት ቀናኢ የሆነዉን እና ደሙን ያፈሰሰዉን ሰፊዉን የትግራይ ህዝብ ጥቂት የሰርዐቱ ተጠቃሚ የሆኑ የወያኔ አባላት ከሌላዉ ህዝብ ጋር ከማጋጨት አይቆጠቡም፡፡ ወያኔ ለመሰሪ እቅዱ ተግባራዊነት አንዳንድ ስሜታዊ የሆኑና ነገሮችን አሻግሮ ማየት የተሳናቸዉ ካድሬዎች እና ባለስልጣናት በሌሎች ክልሎች በሰላም፣ በፍቅር የሚኖሩትን የትግራይ ተወላጆችን ክልላችንን `ለቃችሁ ዉጡ` የሚል ዕኩይ ሃሳብ እንዲቀነቀን በማድረግ በዚህ ማለት ያልተገባ ድርጊት የትግራይ ህዝብ እንዲነሳ ሊሞክሩ ይችላሉ፡፡ ከዚህም አልፎ ሌሎች ረቀቅ ያሉ ደባዎች ሊሞከሩ እንደሚችሉ በመገንዘብ እና ግራ ቀኙን በማመዛዘን ይህንን መርዘኛ አካሄድ ከምንጩ ልናረክሰዉ ይገባል፡፡

 

  1. የታቀደ የሽብር ስራ መስራት

የተለያዩ የጥናት ስራዎች እንደሚያረጋግጡት ድንበር የማይሻገር መንግስታዊ የሽብር ተግባራት በየአገራቱ ሲፈፀሙ እንደነበር ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ እንደምናዉቀዉ በተለያየ ጊዜና ቦታ የመንግስት ኃይሎች ህዝብ በተሰበሰበበት ወይም በጉዞ ላይ ፈንጂዎች እና ቦንቦች እንዲፈነዱ በማድረግ ህዝቡ ሽብር ዉስጥ እንዲገባ ማድረግ ወይም የሽብር ተግባር ሊፈፀም ሲል እንዳይፈፀም አድርገናል በማለት ህዝቡ ወያኔ/ኢሕአዴግ ከሌለ ችግር ዉስጥ እንገባለን በማለት በስልጣን ላይ እንዲቆይ መንገዱን ያመቻቻል፡፡ በቅርቡ በአንዋር መስጊድ የተፈፀመዉን ልብ ይሏል፡፡ ሰለዚህ እንደዚህ ያሉ የታሰበባቸዉ መንግስታዊ የሽብር ተግባር ሊረብሽን እንደማይገባና መረጃዎችን በፍጥነት በመቀባበል የታሰበዉን እኩይ ድርጊት ልናወግዘዉ ይገባል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የድምጻችን ይሰማ ወቅታዊ ጽሑፍ፡ ሺህ ሆነን እንደ አንድ፤ አንድ ሆነን እንደ ሺህ - የፅኑዎች ትግል

 

ከላይ ከተጠቀሱት አደገኛ አካሄዶች በተጨማሪ ወያኔ ለያዘዉ የፖሊቲካ ስልጣን ሲል የማይሞክረዉ፣ የማይፈጽመዉ ነገር የለም፡፡ የሀገር ገንዘብ ከመጠቀም ጀምሮ፣ በደም እና በአጥንት የተከበረዉን የድንበር መሬት አሳልፎ ለመስጠት እስከመዘጋጀት ይደርሳል፡፡ ከዚሁ ጎን በሀገር ዉስጥ የሚቃወሙትን በማሰር፣ በማሰቃየት እና በማሰወገድ እንዲሁም ከዉጭ ያሉትን ለማሳፈን እና ለማፈን ብዙ ርቀት ይጓዛል፡፡

ዉስጣዊ እዉነታዉ

ይህ አፋኝ መንግሰት የህዝቡ ኑሮ መሻሻል እያሳየ እንደሆነ ለማሳመን ብዙ ይደክማል፡፡  ለምሳሌ የተነካካ አኃዛዊ መረጃ (ማኒፑሌትድ ስታትስቲክስ) በመጠቀም ሁሉ ነገር እንደተሳካ፣ ገበሬዉ ከአምናዉ የተሻለ ምርት እንዳመረተ፣ ድህነት በከፍተኛ ደረጃ እንደቀነሰ፣ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ከመጠነኛ ችግር በስተቀር ጥሩ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነ፣ ሙስናን የመዋጋት ስራዉ ተጠናክሮ ዉጤት እያመጣ እንደሆነ፣ ከወጭ ገበያ ዉጤት እንደተገኘበት፣ በአጠቃለይ ኢኮኖሚዉ የተረጋጋ እንደሆነ የሚገልጹ ዘገባዎች ለህዝቡ እስከሚሰለች ድረስ በመንግስት ቁጥጥር ስር ባሉ የህትመትና የኤሌክትሮኒክ ሚዲያዎች ይቅርብለታል፡፡ በዉጭ የሚገኙ አንዳንድ የዉጭ ጋዜጠኞችን እና የፋይናንስ ተቋማት ባለሙያዎችን በገንዘብ በመደለል ልማት እንደመጣ እና ድህነት እንደተራገፈ የሚገልጽ ጽሁፍ በማጻፍ እና በኢንተርኔት መስኮት እንዲለቀቅ በማድረግ የእኛዎቹ ‘ልማታዊ ጋዜጠኞች’ ለማደንቆር እንዲጠቀሙበት ይደረጋል፡፡ የአገራችን ሚዲያዎች የኢትዮጲያዉያንን ችግሮች፣ ጉዳዮች፣ ትኩረቶች፣ ጥያቄዎች … ምን እንደሆኑ እያወቁ ከመንግሰት ጋር የማያነካካ ማህበራዊ ጉዳይ፣ ምንጩ ከዉጭ የሆነ መረጃ እና ጭፍን ፕሮፓጋንዳ ህዝቡ በየቀኑ ይጋታል፡፡ አልፎ አልፎም ዉዥንብር ዉስጥ የሚከቱ መረጃዎች የሚለቀቁበት ወቅትም አለ፡፡

ድህነት ቀንሶ ህዝቡ የተሻለ ህይወት እንደሚኖር የሚነገረን ስልጣንን ለማራዘም እና ሀብት ለማጋበስ በመሆኑ የማደንቆር ስራዉ ተጠናክሮ መቀጠሉ አይቀሬ ነዉ፡፡  ስለዚህ እንደዚህ ያለዉን ነጭ ፕሮፓጋንዳ ወደጎን በማድረግ እና መረጃዉ ተአማኒነት የጎደለዉ ስለሆነ ፀረ-ወያኔ ትግሉን ባለንበት ቦታ እና ሁኔታ ማፋፋም ያስፈልጋል፡፡ የትግል ስልቱ የተለያየ ቢሆንም ግቡ የወያኔ/ኢሕአዴግን ስርዐትን ከስሩ መንግሎ መጣል ስለሆነ የየበኩላችንን ጥረትና አስተዋጽኦ  ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡

ለማጠቃለል

በተለይ በዚህ ጽሁፍ በቁጥር ከአንድ አስከ ሶስት የተጠቀሱት በጣም ትኩረት ልንስጠባቸዉ የሚገቡ ቁልፍ ጉዳዮች ናቸዉ፡፡ ኢትዮጲያ አንደሀገር ለመቀጠል ፈተና ላይ ልንወድቅ ስለምንችል ሁላችንም ትኩረት ሰጥተን አንድ ልብ መሆን ይጠበቅብናል፣ ካልሆነ የኢትዮጲያ እጣ ፈንታ አደገኛ አጣብቂኝ ዉስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ ከእኛ ጥንቃቄ በተጨማሪ ሁሉም በየእምነቱ ለፈጣሪዉ ፀሎት ማድረግ አለበት፡፡ ከመጪዉ መከራ እንዲታደገን ሁላችንም ተግተን መፀለይ እና የድርሻችንን ሃላፊነት መወጣት ይጠበቅብናል፡፡

 

ድል ለኢትዮጲያ ህዝብ !!!

ኢትዮጲያ በነፃነት፣ በሠላም እና በህብረት ለዘላለም ትኑር !!!

ፈጣሪ ኢትዮጲያን ይጠብቅ !!!

 

1 Comment

Comments are closed.

Share