እኔና ስርጉተ–  አልተግባብቶም        ይገረም አለሙ

በቅድሚያ እህቴ ስርጉተ ለአስተያየትሽ አመሰግናለሁ፡፡ ሁለት ገጽ ጽሁፌ እያንገሸገሽሽ አንብበሽ በተረዳሽውና በገባሽ መልክ  በጨዋ አቀራረብ አስተያየት በመስጠትሽ፤- እኛ ኢትዮጵያውያን በእጅጉ ከሚጎድሉን በርካታ ነገሮች አንዱ ይህ ነው፤ በጽሞና መነጋገር ሀሳብ መለዋወጥ መደማመጥ አለመቻል፡፡ ሀሳብን በሀሳብ ከመሞገት ይልቅ ፈጥኖ ዘለፋና ፍረጃ፤

እህቴ  በጽሁፏ መጀመሪያ ሀይለ ቃሏን ብቻ አውጥቼ ጠረጴዛየ ላይ አድርጌ ፈተሸኳት ስትል በጥሞና አንብባዋለች በሚገባም  ተረድታኛለች የሚል ስሜት አድሮብኝ ነበር፡፡ ነገር ግን 6 ገጽ የፈጀውን ሀሳቧን አንብቤ ስጨርስ እንደገባኝ ሀይለ ቃል ብላ ያወጣቻቸውን ብቻ ይዛ  በእነኛ ላይ ተመስርታ አቶ ገብሩ አስራትን እያሰበች (ርሷ እንዳለችው) ሌላውን የጽሁፉን መልእክት በትኩረት ባለማየቷ  ያነበበችው በሀሳቧ ታወጣ ታወርድ ከነበረው  የተምታታባት ይመስላል፡፡ ይህም በመሆኑ ጽሁፉ የማይለውን ትርጉም በመስጠት በሀሳብ ሳንለያይ ተለያየን፤ አንድ ቋንቋ እየተናገርን ሳንግባባ ቀረን፡፡

በሀሳብ መግባባት ሲቻል መልካም ነው፡፡ ካልሆነ ደግሞ ላለመግባባትም መግባባት ጥሩ ነው፡፡ አንድ አይነት ሀሳብ እያንጸባረቁ አለመግባባት ያለመደማመጥ ውጤት በመሆኑ ምን አልባት ሀሳቤን በትትክል አልገለጽሁ ይሆን እንዴ ብዬ ጽሁፌን እንደገና አነበብኩት፡፡ ግና ስርጉተ የፈንጅ ያህል ነው ያቆሰለኝ ያለችውን ትርጉም የሚሰጥ ቃልም ሆነ አረፍተ ነገር ማግኘት አልቻልኩም፡፡ እናም ሲሆን ለመግባባት ከልቻልንም ላለመግባባት መግባባት መደማመጡ መልካም ነውና ከረዥሙ ጽሁፍ ትንሽ ማሳያዎችን በመጥቀስ  ሀሳቤን ግልጽ ለማድረግ ልሞክር፡፡

1-„የልማታዊ መንግሥትበለው! ይህም በራሱ አቅሙአይደለም። ያለማው አካባቢ ካለ ጥብቅናይቆምለት። ምን አልባት ብላለች ስርጉተ፡ ይህ ብቻውን የእኔ ጽሁፍና ስርጉተ እንዳልተገናኙ በቂ ማሳያ ነው፡፡ ምንም ማብራሪያ ሳያስፈልግ በጽሁፌ የገለጽኩትንና ይህን ለማለት ያበቃትን ዐ.ነገር  ደግሜ ላስፍረው፤ “አሁን ልማታዊ መንግሥት እያለ ራሱን እየጠራ ነው ታዲያ እኛ በዚህ  እንጠራዋለን?” ነው የሚለው የእኔ ጽሁፍ፡፡ ለራሱ በሰጠው ግብሩን በማይገልጽ መጠሪያ ልንጠራው አይገባም እያልኩ ስርጉተ ያለማው አካባቢ ካለ ጥብቅና ይቆምለት በማለት ልማታዊ መንግሥት ተብሎ ይጠራ እንዳልኩ አድርጋ ነው የተረዳችው፡፡

2-እኔ እርስዎ የጻፉት ጹሑፍ የፈንጅ ያህል ነውያቆሰለኝ። አይደለምሌላውን። እያቅለሸለሸኝ ነውያነበብኩት፤ ስለምን? በአጋጣሚዎች ምክንያት ብዙ ነገሮችን በጥልቀት ስለማዳምጣቸው በማለት እኔ ወያኔ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያውያን ላይ ያደረሰውን በደልና ጥፋት እንደማላውቅ ወይንም ወደ ጎን አድርጌ በደጋፊነት አንደተሰለፍኩ ገምታኛለች፡፡ ጽሁፌ ውስጥ የትኛው አገላለጽ ይህን ትርጉም እንደሰጣት አልገባኝም፡፡ ብታሳየኝ ጥሩ ነበር፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሐምሌ ጨረቃ! (ክፍል አንድ) - ከአንዱዓለም አራጌ ዋለ (አንድነት ም/ሊቀመንበር ከቃሊቲ ማጎሪያ)

ስርጉተ በሰፊው የገለጸችውን የሰው ልጅ ሊሰራው የማይገባ እርኩስ የሆነ የወያኔ ተግባር አውቃለሁ፡፡ የማውቀው ደግሞ  በስማ በለው ሳይሆን እየኖርኩበት በራሴ ጭምር ደርሶም እየደረሰም ነው፡፡ ማወቅ ብቻ ማውገዝ ብቻ አይደለም ስልጣን ጨብጦ የጫካ ርኩስ ተግባሩን ከቤተ መንግሥት ሆኖ መፈጸም ከጀመረበት ግዜ አንስቶ ከሰላማዊ ታጋዮች ጋር ተሰልፌ የታገልኩ ነኝ፡፡እናም በወያኔ ማንነት ምንነትና እንዴትነት ላይ ልዩነት ሳይኖረን ነው ያልተግባባነው፡፡

3- የነገ ኢትዮጵያ መከራው በቁርሾ እንዳይወራረድ በመቻቻል እንዲሰክንእንሻለን። ይህ የስርጉተ አባባል የእምነቴ መሰረት በጽሁፌ የተገለጸው ሀሳቤም ማጠንጠኛ ነው፡፡ ለዚህም ነው አልተግባብቶም ለማለት የበቃሁት፡፡ትግሉ ወያኔን ማሸነፍ ብቻ ሳይሆን ከወያኔ በኋላ ልጆቿ በፍቅር በሰላም በእኩልነትና በነጻነት የሚኖሩባት ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ከሆነ ዛሬ የምንናገረው የምንጽፈውም ሆነ ተግባራዊ የምናደርገው ይህን ያነዘበ መሆን አለበት፡፡ እናም ስርጉተ እንዳልሽው የነገ ኢትዮጵያ መከራው በቁርሾ እንዳይወራረድ በመቻቻል እንዲሰክን ከመሻት ባለፈ እውን እንዲሆን  ከተመኘን ወያኔና ትግረኛ ተናጋሪ ወገናችንን ለያይቶ ማየት  ይበጃል፡፡

4 በዘመነ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ነፃ ውጪ አስተዳደር እያንዳንዱ የእንቅስቃሴ ነጥብ በመርዝ የተበከለ ስለሆነ ሌላ የሰከነ የመንፈስ አብዮት የሚጠይቅ ተግባር ከፊት ለፊት ብሄራዊ ነፃነት ፈላጊውን ህዝብይጠብቀዋል። ወንድሜ ሆይይህ የሚጎረብጠዎት ከሆነ…….

የእኔኑ ሀሳብ የደገመ ሀሳብ እንደምን ይጎረብጠኛል፡፡ ወያኔን የትግሬ ነጻ አውጪ ማለት የሱን መርዝ ማራባት ነው፤ ምክንያቱም አንድም እሱ ሥልጣን ፈላጊ አንጂ ነጻ አውጪ ስላልሆነ፡ ሁለትም አባባሉ ትግረኛ ተናጋሪ ወገናችንን በሙሉ ጠቅሎ ከወያኔ ጋር በአንድ ቅርጫት የሚያስገባና ሌላው ኢትዮጵያዊ ትግረኛ ተናጋሪውን ወገን አንደሚጠላ አድርጎ በመስበክ የርሱ ጋሻና ዋሻ ለማድረግ የሚሰራውን ሴራ ማገዝ የሚረጨውን መርዝ ማሰራጨት ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ፈጣሪ ነብሳቸውን እንዳሻው ያድርጋትና አቶ መለስ መቀሌ ተኝተው በትግረኛ ቋንቋ “እኛ ከሥልጣን ብንወርድ ነፍጠኞች አንድ ቀን አያሳድሩዋችሁም” በማለት የረጩት መርዝ በምንም ምልኩ አላማቸውን አንዲያሳካ እኛ በማወቅም ይሁን በበደል ግፊት ተባባሪ መሆን የለብንም ነው የእኔ ጽሁፍ መልእክቱ፡፡ እርሱ በጥላቻ መርዝ የበከለውን እኛ በፍቅር እናጽዳው ነው፡፡ወያኔ ለሥልጣኑ እድሜ ሲል ለሚፈጥረው መለያየት እኛ በር አንክፈት መንገድ አንስጥ ነው፤እሱ ጎሰኝነትን ሲያቀነቅን እኛ ኢትዮጵያዊነትን እንዘምር ነው ሀሳቤ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ቴዲ የኩዋስ ሜዳ ልጅ ነው - (ሄኖክ የሽጥላ -ገጣሚው)

4በሌላ በኩል ተበድላችሁምተቀጥቅጣችሁምተገፍታችሁምየገፋችሁን የቀጠቀጣችሁን ዋጥ አድርጋችሁ የተገላቢጦሽ ይቅርታ መጠዬቅ አለባችሁምወይንም አትነካኩትይመስላል። ስርጉተ በፍጹም– ይህን ትርጉም ይሰጣል የምትይውን ቃል ወይንም አረፍተ ነገር ብታሰይኝ ጽሁፌ ሀሳቤን በትትክክል አልገለጸም ብዬ ለመማር ያስችለኝ ነበር፡፡ ከዚህ የሚያልፍ ከሆነም ይቅርታ ለመጠየቅ ፡፡ ወያኔ የትግሬ ነጻ አውጪ መባሉ ይበዛበታል ግብሩን አይገልጽም ለሥልጣን ሲል ሕዝብ ቢያልቅ ሀገር ቢፈራርስ ደንታ የሌለው ወያኔ እንደምን ነጻ አውጪ ይባላል ወዘተ ማለት እንዴት ሆኖ የዚህ አይነት ትርጉም ሊሰጠው እንደቻለ አይገባኝም ፡፡ በትንሹ የሀውዜንን እልቂት ፤የበደኖን የወተርንና የአርባ ጉጉን ጭፍጨፋ፤የወለጋውን አረመኔያዊ ግድያ ወዘተ ማስታወስ በቂ ይመስለኛል፡፡ እንኳን ይቅርታ ልንጠይቃቸው እነርሱ ልብ ገዝተው አገዛዛችንን ማሰመር አልቻልንም ባይሆን እንኳን አወራረዳችንን እናሳምር ብለው በደላቸውን  በንስሀ ለማስተስረይ ጥፋታቸውን በይቅርታ ለማወራረድ ቢፈቅዱ እንኳን በህግ ተጠያቂ ከሚሆኑባቸው ወንጀሎችና ጥፋቶች ነጻ ሊሆኑ አንደማይችሉ ነው የማምነው፡፡

5- ኢትዮጵዊነታችን ይበልጥብናል፤ ከብዙሃን  ጋር መኖር ይሻለናል ማለትአለባቸው

ትክክል፤-  ይህን ማድረግ የትግራይ ወገኖቻችንን ድርሻና ኃላፊነት ነው ስንል እኛ ደግሞ ወያኔዎች መጠቀሚያ ለማድረግ ሲሉ የሚነዙት አሉባልታና የሚረጩት መርዝ ሀሰት መሆኑን በተግባር ማሳየት ካልቻልን የምንለው ይሆን ዘንድ እንደምን ይቻላል፡፡ ለዚህ ነው ወያኔና ትግረኛ ተናጋሪውን ኢትዮጵያዊ መለየት አለብን፤ በወያኔ ሥልጣን ላይ መኖር ተጠቃሚ ቢሆኑ እንኳን በወያኔ ከሥልጣን መውረድ ተጎጂ እንደማይሆኑ  አምነን ማሳመን ስንችል ነው  ከብዙኑ ጋር መኖር ይሻለናል  ከማለት አልፈው  አታለያየን በስማችን አትነግድብን ወያኔ ዘወር በልልን ማለት የሚችሉት፡፡

6-እኔ የልጆችን መጸሐፍት ስጽፍ እንዴት ተጨንቄ እንደፃፍኩት፤ ምን ያህል ጊዜም እንደበላብኝምአውቃለሁ። እኛ ባለፍነበት ንትርክ እነሱ ማለፍ ስለሌለባቸው ነበር ያን ያህል በጥበብ ድክም ብዬየሠራሁት። የልጆች ራዲዮ ዝግጅቴም እንዲሁ ፍቅርንለማውረስ ይተጋል።  ይህን ሳነብማ እኔና ስርጉተ የባቢሎን ዘመን ሰዎች የሆንን ያህል ተሰማኝ፡፡ አንድ ሀሳብ እያራመድን አንድ ቋንቋ እየተናገርን መግባባት የተሳነን፡፡ እኛ ባለፍንበት ንትርክ ማለፍ የለባቸውም፣  ጥላቻን ሳይሆን ፍቅርን፣  መለያየትን ሳይሆን ተነጋግሮ መግባባትን፣ በአንድ ሀገር ልጅነት ስሜት በፍቅር ተሳስቦ  መኖርን ማውረስ አለብን የምንለው ዘር ሳንመነዝር፣ የቋንቋ ገደብ ሳናበጅ፣ የሀይማኖት ልዩነት ሳንፈጥር ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ከሆነ  ወያኔን ነጻ አውጪ ማለት አይገባም በሚል የቀረበው ጽሁፌ ከዚህ አስተሳሰብ አይቃረንም፡፡አልተግባብቶ ሆኖ አንጂ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  "ትናንት ከዉጭ ወራሪዎች የታደገን መከላከያ ሠራዊታችን ዛሬም ከአገር ዉስጥ ወራሪዎች ይታደገናል" - አርበኞች ግንቦት 7

በመጨረሻም ወያኔን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ለማንሳት የሚደረገው የትኛውም ትግል ልንደርስበት የምንፈልገውን ግባችንን አሸጋግሮ በማየት ላይ የተመሰረተ በስሜት ሳይሆን በእውቀት የሚካሄድ በጥላቻ ሳይሆን በአላማ የሚመራ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ በእኩልነትና በፍቅር የሚያይ ሊሆን ይገባል፡፡

ወያኔ የሰው ልጅ ይሰራቸዋል ተብሎ የማይታሰብ ድርጊቶችን ፈጽሟል ፤ አሁንም ወደ ፊትም እድሜ እስከሰጠነው ድረስ ሥልጣኔን የሳጣኛል ብሎ የሚፈራውን ነገር ባየ በሰማ  ቁጥር ተመሳሳይ ድርጊት ከመፈጸም ወደ ኋላ አይልም፡፡ የሰራውን ስናስታውስ አረመኔነቱ ሲታሰበን ያደረሰብን ቁስል ሲቆጠቁጠን ጥላቻችን መበረርታቱ ስሜታችን ለበቀል መነሳሳቱ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ እናም ለርኩስ ድርጊቱ የሚመጥን ተመሳሳይ ተግባር መፈጸም እንደሚገባን ሊሰማን ይችላል፡፡ ነገር ግን ክእነርሱ መሻላችንን የምናረጋግጠው፣ ለሀገርና ለሕዝብ የሚበጅ ራዕይ ያለን መሆናችንን የምናሳየው፣ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመሻታችን መገለጫ የሚሆነው  ይህን ስሜታችንን ገትተን የዛሬውን ድል ብቻ ሳይሆን የነገውን ውጤት አርቀን እያሰብን ለአላማችን ስኬት ስንታገል ነው፡፡ ደራሲ አያልነህ ሙላት በትያትር እንደገለጸው ኢትዮጵያ በጋሜ እንዳትቀር፡፡

በሰላማዊውም ሆነ በጠመንጃው ትግል በተቻለ መጠን የትግሉን ተሳታፊ ካልሆነም ደጋፊ ማብዛት፤ ብሎም የሚቃወምንና የሚጠላን መቀነስ ፤ በአንጻሩም የተቃራኒን(;ጠላትን)  ጎራ የሰው ኃይል ማሳሳት  ዋንኛ ስትራቲጂ ነው፡፡ ወያኔ ዘረኛ መርዙን የሚረጨው ከፋፋይ ፕሮፓጋንዳውን የሚነዛው በትግራይ ክልል የተሰሩ ግንባታዎችን ወዘተ ጠዋት ማታ የሚነግረንና የሚያሳየን ትግረኛ ተናጋሪውን ወገን ጋሻውና ዋሻው ለማድረግ የያዘውን እኩይ ሴራ ለማሳካት ነው፡፡  ይህን ሴራ ማክሸፍና የረጨው መርዝ ጥፋት እንዳያደርስ ማድረግ የሚገባን እኛ ከወያኔ በተቃራኒ የተሰለፍነው ነን፡፡  ተግባራዊ የሚሆነው ደግሞ ጥላቻን በማሳየት ሳይሆን ፍቅር በመስጠት፣ ጠላቴ ብሎ በማራቅ ሳይሆን ወገኔ ብሎ በማቅረብ፤ የዛሬ ተጠቃሚ ሆነሀል ብሎ በመግፋት ሳይሆን ና ስለነገ አብረን ራዕይ ይኑረን በማለት ወዘተ ነው፡፡ስርጉተ የመንፈስ አብዮት የሚጠይቅ ተግባር ያልሽው መገለጫው ይህ ይመስለኛል፡፡

 

Share