July 11, 2015
18 mins read

ይድረስ ለነጻነት ናፋቂ ኢትዮጵያዊያን – ከያህያ ይልማ

tplf rotten apple 245x300 1

አሁን ያለው የሕወሐት ሥርዓት ችግሮች ምን እንደሆኑ በውል ተመልክቶ በተቃራኒው ምን ዓይነት የትግል መስመር እንደሚያስፈልግ እኔ ያህያ ይልማ የሚከተሉትን ቁምነገሮች ሳስቀምጥ የሌሎቻችሁም አስተያየት ውሸት የሌለው እና ህሊናዊ ተጠየቅ ባለበት መልኩ እንዲሆን እያስገነዘብኩ በደስታ እጋብዛችኋለሁ::

1. የሕወሐት ሥርዓት ችግሮች

ሀ. የሕወሐት መስራቾች ወደ ትግል ለመግባት ያሰቡት እና የገቡት የንጉሱን ስርዓት ብሎም የአማራውን ገዥ መደብ በተለይም የሰሜን ሸዋን የበላይነት ተዋግቶ በማስወገድ የወልቃይትንና የራያን ለም መሬቶች አስገብቶ ታላቋን ትግራይ መመስረት አልሞ ሆኖ እያለ አምባገነኑን የደርግ ስርዓት ከኢትዮጵያ ህዝብ ጫንቃ በማውረድ በምትኩ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት አሰፈንኩ እያሉ ያጭበረብራሉ:: እዚህ ላይ የማይካድ ሐቅ አለ:: የሕወሐት ተራ ታጋዮች በቆራጥነት ተዋግተዋል፣ ስርዓጥ አልበኛ ከነበረው ከአምባገነኑ ደርግ አንጻር የሰራዊታቸው ዲስፕሊን የሚደነቅ ነበር፣ የመጨረሻ ደባቸው ምን እንደሚሆን በትክክል ባይታወቅም እንዲሁ በምንረዳው ሐሳባቸውን ከመገንጠል ወደ ኢትዮጵያን መምራት አስተሳሰብ ቀይረውም ነበር:: እነዚህ ሁኔታዎች በትግራይ እና በሌላው የኢትዮጵያ አካባቢ የሚኖሩ ገጠሬዎች እንዲደግፏቸውና አብረዋቸው እንዲሰለፉ ዳርጓቸዋል:: እየፈራረሰ የነበረውን የወቅቱን ሶሻሊስታዊ ርዕዮተ ዓለምን በብልጣብልጥነት የተው መስለው ከምዕራባዊያን ጋር ወዳጅነት መፍጠራቸውም በእጅጉ የጠቀማቸው አካሄድ ነበር::

ለ. የሀገር ድንበርን ከማስከበር እና የህዝቦችን አንድነት ከመጠበቅ አንጻር ሲነጻጻር የወረደ ቢሆንም ሕወሐት የአጼ ዮሐንስን ዘመን አምጥቸላችኋለሁ በሚል ስሜት ትግራዊያንን ተጠቀሙብኝ እያለ በሙስና የማይገባቸውን ሐብት እንዲያጋብሱ እያደረገ ይገኛል::

ሐ. የሕወሐት ስርዓት የለየለት ዘረኛ መሆኑን የራሱ አጋዥና ታዛዥ የሆኑት የብአዴን፣ የኦህዴድ፣ የደህዴንና ሌሎች አጋር ድርጅቶችም ተረድተውት ራሳቸውን ነጻ ለማውጣት ጊዜ እየጠበቁ ይገኛሉ:: ለዚህም ማስረጃ ጦሩና ደህንነቱ እንዲሁም ወሳኝ የመንግስት አውታሮች በሕወሐት ብቸኝነትና የበላይነት ተጨንፍረው ይገኛሉ::

መ. ሕወሐቶች በትግል ወቅት ያልነበራቸውን ጭካኔነት በአሁኑ በሰለጠነ ዘመን እንዴት ሊተገብሩት እንደቻሉ በሚያሳዝን ሁኔታ ዜጎችን ሲያስሩ፣ ሲያንገላቱና ሲገድሉ መመልከት የተለመደ ተግባር ሆኗል::

ሰ. የሕወሐት ስርዓት ለብዙሃኑ ኢትዮጵያዊያን ጨለምተኝነትንና ተስፋቢስነትን አስፍኗል:: መማር ትርጉም አጥቷል፣ የመኖር ዋስትና ጠፍቷል፣ ሀላፊነት ያላቸው ሰዎች በውሸት የተሞሉ በመሆኑ ውሸታቸውን እየነዙ በኢትዮጵያዊያን መካከል መተማመን ጠፍቷል፣ ከፋፍሎ የመግዛት ስልትን አጠናክረው ስለቀጠሉበትም ኢትዮጵያዊያን በጎሪጥ እንዲተያዩ ዳርጓል::

ረ. የሕወሐት ስርዓት ሉዓላዊነትን ከማስከበር እና ከማስጠበቅ ይልቅ ስልጣንን የሚያስቀድም በመሆኑ በድንበራችንና በህዝባችን ላይ እየደረሰ ላለው አሳፋሪ ውርደት ተጠያቂ ነው::

ሸ. የመሰረተ ልማት አውታሮች እየተዘረጉ ቢታዩም እንዴት ነው የሚዘረጉት፣ ጥቅሙስ ለህዝቡ እየደረሰ ነው ወይ ተብሎ ሲታይ መልሱ ተቃራኒ ነው:: የመሰረተ ልማት አውታሮቹ የሚገነቡት ኢትዮጵያ በረጅም ጊዜ እንኳ ልትከፍለው የማትችለው ወደ ፵ ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ የብድር እዳ እንድትሸከም ሆና ሲሆን ከዚሁ እዳ ከግማሽ በላይ የሚሆነው በፖለቲካ ጉዳይ የሚንቀሳቀሱ ዜጎችን ለማፈኛ ሆኖ ከማገልገል በተረፈ በሕወሐት ባለስልጣናት እየተዘረፈ የሚገኝ መሆኑን የተለያዩ መረጃዎች ያሳያሉ::

ቀ. በአጠቃላይ የሕወሐት ስርዓት ለዚህ ዘመን የማይመጥን ፍጹም አምባገነን ዘረኛ ስርዓት ነው:: ህዝቡም ይህን በደንብ ስለሚገነዘብ ሕወሐትን እንደ ዘራፊ ቡድን እንጂ እንደ መንግስት አይመለከተውም::

በመሆኑም የሕወሐት ስርዓት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መወገድ ያለበት የኢትዮጵያዊያን ካንሰር ነው:: ከዚህ በመነሳት የሕወሐት ስርዓት በመሳሪያ የታጀበ ህዝባዊ አመጽን በማቀጣጠል ሊወገድ ይገባዋል::

2. ሕወሐትን ለማስወገድ የሚያስፈልጉ የትግል መስመሮች

ሀ. ሰላማዊ ትግል እያሉ ጊዜን ከማጥፋትና ዜጎች እንዲሰቃዩና እንዲገደሉ ከማድረግ አሁን ባለው ሁኔታ የሕወሐት ስርዓትን ለማስወገድ የሀይል አማራጭ መጠቀም ብቻ መሆኑን ማወቅና ከልብ ማመን ነው::

ለ. ከታሪክ እንደምንረዳው እንኳንስ አምባገነኑ ሕወሐት ይቅርና ዴሞክራስያዊ የሆኑ ስርዓቶችም ይወለዳሉ፣ ያድጋሉ፣ ይሞታሉ:: ከዚህ አንጻር ሕወሐት ተወልዶ ሲያድግ ተመልክተናል:: አሁን ደግሞ የህዝብ እሮሮ በርክቶ ወደመሞቻው ጉዞ ላይ ይገኛል:: ይህንን መረዳትና የኢትዮጵያ ካንሰር የሆነውን ሕወሐት ማስወገጃ ጊዜው አሁን መሆኑን መገንዘብና መነሳት ያስፈልጋል::

ሐ. ተስፋ ሰጭ ሆኖ እየተንቀሳቀሰ ያለውን የአርበኞች ግንቦት ሰባትን ሀይል ከሁሉም የኢትዮጵያ አቅጣጫ መደገፍ፣ ቅስቀሳ ማካሄድና መቀላቀል:: አርበኞች ግንቦት ሰባትን መቀላቀልና ማጠናከር የሚጠቅመው ሕወሐትን ለማስወገድ ብቻ ሳይሆን ሕወሐት ከተወገደ በኋላም ሳይታወቅ የሕወሐት ዓይነት ቡድን ሳይፈጠር ሉዓላዊነት የሰፈነባት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት ስለሚጠቅም ነው:: የክርስትና እና የእስልምና ሀይማኖቶች እንዳይጨቆኑብን ካሰብን ክርስቲያኖችና እና ሙስሊሞች የሆን በሙሉ አርበኞች ግንቦት ሰባትን መደገፍና መቀላቀል ነው:: የብሔር ጭቆና አለ ብለን የምናምንም አላስፈላጊ የቃላት አተካራን ትቶ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ሀይል መሆንና ውሳኔዎችን በጋራ የምናስኬድ መሆን:: ድጋፉ ከተለያየ አቅጣጫ የማይመጣ ከሆነ ግን አርበኛች ግንቦት ሰባት ጎንደሬ ወይም ሰሜን ሸዋ ወይም ጎጃሜ ወይም ወሎየ የበዛበት ወይም አንዱን ሀይማኖት ብቻ ከፍ አድርጎ የሚመለከት ይሆንና በጋራ ወሳኝ ከመሆን የቡድኑን ይሁንታ የምንጠብቅ እንሆናለን:: በዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብና በፍትህ የሚያምነው አንዳርጋቸው ጽጌ በወያኔ መዳፍ እንደገባ ሁሉ አሁን በስም ከምናውቃቸው ታጋዮች የድሉን መጨረሻ ለማየት የሚታደሉት ጥቂቶች ሊሆኑ ይችላሉ:: ይህ ማለት የሁላችንም ተሳትፎ ከሌለ ከድል በኋላ የምናየው አርበኛች ግንቦት ሰባት መልኩን ቢቀይር ችግሩ አሁን ያለመሳትፋችን ውጤት ነው የሚሆነው:: ስለሆነም አሁን የምናደርገው ተሳትፎ ከኢትዮጵያችን ነጻ መውጣት ጋር ተያይዞ ለሚኖረው የህልውናችን፣ የማንነታችንና የአብሮነት ውሳኒያችን አካል መሆኑን ተገንዝበን ከአርበኛች ግንቦት ሰባት ጎን መቆም::

መ. አርበኛች ግንቦት ሰባት እንደ ድርጅት ትግሉን እያፋፋመ ጎን ለጎን ማኒፌስቶ ማዘጋጀት ይጠበቅበታል:: ማንፌስቶው የሚከተሉትን ሶስት ወሳኝ ጉዳዮች ቢያካትታቸው እሻለሁ::

1. ኢትዮጵያ ክብሯ ከፍ ያለች አገር ሆና እንድትቀጥል ህጋዊ ሰውነት ያለው ማንኛውም ተቋም መለሰ ዜናዊና ደቀመዝሙሮቹ እያላገጡ እንዳየነው የኢትዮጵያን ታሪክ የማንቋሸሽ ስራ ነውርና ተቀባይነት የሌለው ስለመሆኑ ትኩረት ማድረግ::

2. ሕወሐት ብሔር ብሔረሰብና ህዝቦች እያለ ትርጉሙ ላገሬው ግልጽ ያልሆነን ማደናገሪያ እንደተጠቀመበት ሳይሆን በቀናነት ከምር ራስን በራስ የማስተዳደር ተግባራዊነት አስፈላጊ ነው:: ለዚህም ፕ/ር መስፍን ከጻፏቸው መጽሀፍት መካከል «ኢትዮጵያና የመንግስት አስተዳደር» [ካነበብኩት ጊዜው ስለረዘመ የመጽሀፉ ትክክለኛ ርዕስ የጠቀስኩት ስለመሆኑ እርግጠኛ አይደለሁም] በሚለው እንደተመራመሩት አካባቢያዊ ስሜቶች የሚንጸባረቁባቸው ማህበረሰቦች የራሳቸው አስተዳዳሪዎች ኖሯቸው ተጠሪነታቸው በቀጥታ ለማዕከላዊ መንግስት መሆን:: ለምሳሌ የተንቤን፣ የአድዋ፣ የመቀሌ፣ የራያና የጁ፣ የላስታና ዋግ፣ የደላንታና ደቡባዊ ወሎ፣ የከሚሴ፣ የአፋር፣ የኦጋዴን፣ የጎጃም፣ የጎንደር፣ የሸዋ፣ የሐረሪና ድሬዳዋ፣ የወላይታ፣ የጋሞ፣ የጎፋ፣ የአርሲ፣ የሀድያ፣ የጉራጌ፣ የስልጤ፣ የባሌ፣ የወለጋ፣ የቤንችማጅ፣ የሐመር፣ የሙርሲና የቱርሲ፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ የጋምቤላ ወዘተ. የራሳቸው አስተዳደር ኑሯቸው ተጠሪነታቸው ለማዕከላዊ መንግስት እንዲሆን ማድረግ አንድ ነን በሚል ሽፋን የሚከሰቱ ዘረኛዊ የአስተዳደር በደሎችን በእጅጉ ለመቀነስ ይረዳል:: አካባቢን ለማልማትም ከልብ ተነሳሽነት እንዲኖር ይረዳል::

3. ታሪካዊ በደሎች እንደነበሩ አምኖ ሀገራዊ እርቅ እንዲኖር ቁርጠኝነትን ማሳየት::

ሠ. ሕወሐትን ለመጣል የሚደረገው ትግል ከተከማቸው መሳሪያ አንጻር አልጋ ባልጋ የሚሆን ባይሆንም እንደ ድሮው በቆራጥነት የሚታገል ታጋይ የሌላቸው መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል:: ቁርጠኝነት የነበራቸው አርጅተው በሙስና ተዘፍቀው ከመዋጋት ይልቅ ሁሉም አዛዦች ሁነው ያሉበት ወቅት ነው:: እንተማመንበታለን የሚሉት እንደ አግአዚ አይነት ያለው ጦርም ቢሆን እንኳ መሳሪያ ባልያዘ ሰላማዊ ዜጋ ካልሆነ በስተቀር መልስ የሚሰጥ ታጋይ ጋር የመዋጋት ሞራል የለውም:: መልቀምቀም የለመደ ስለሆነ ሞትን የሚጋፈጥ አይደለም:: ረባም አረባ ድሮ የሚሰብኩበት አይዲዮሎጂ ነበራቸው:: አሁን ግን እነሱን ግራ አጋብቶ ሌላውንም ግራ ያጋባው አብዮታዊ ዴሞክራሲ በማንም የተተፋ ስለሆነ የሞራል መቀስቀሻ የላቸውም:: አጭበርባሪና ውሸታም መሆናቸው ስለታወቀ አዲስ ሀሳብ እናምጣ ቢሉም የሚቀበላቸው የለም:: ከሕወሐቶችና ጥቅመኛ አለቆች ውጭ ያለው ተራው ወታደር እጅ ለመስጠት የሚዘጋጅና በነሱ ላይ አዙሮ መተኮስ የሚችል ሀይል ነው ያለው:: ስለሆነም የትግሉ መራራነት በአጭር ጊዜ የሚጠናቀቅ ነው የሚሆነው::

ረ. ትግልን ለማካሄድ ምክኒያት ማብዛት ወደ ኋላ ያስቀራል:: ለምሳሌ አርበኞች ግንቦት ሰባት ከጅምሩ ህብራዊ እንደሆነ ብንረዳም መሰረቱ አማርኛ ተናጋሪ የሆነው ህዝብ ነው:: ድርጅቱን ኦሮሞዎችና ነጻነትን የሚሹ ሌሎች አካሎች መሰረቱ በአማርኛ ተናጋሪው በመሆኑ መሸሻ ምክኒያት ማድረግ የለባቸውም:: ከላይ እንደጠቀስኩት ካሁኑ መሳተፍ የራስን ሃሳብ ውጤት እንዲኖረው ለማድረግ ይጠቅማል:: ከዚህ በተጨማሪ አማርኛ ተናጋሪው በሕወሐትና ሆድ አደር አጋር ፓርቲዎች ሲገፋና ፍዳውን ሲያይ እንኳ እልህ ተጋብቶ የራሴ ሳይል ለኢትዮጵያ ብሎ ነው ሲጮህና ሲታገል የኖረው:: ታዲያ ስተት ካለ እንተራረም እንጂ ማለት ኢትዮጵያዬ ማለቱ ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ነው የምቆመው ማለቱ ድጋፍ ያሰጣል፣ አይዞህ ያስብላል እንጂ በጥርጣሬ ያስተያያልን ? የሕወሐትን ከፋፍለህ ግዛ ፖለቲካን መቸም ሁላችንም ጠግበነው አንገሽግሾናል:: እና ለምኑ ብለህ ነው ወገኔ የሚልህን የምትርቅ:: ታሪካዊ ስህተቶችንም እንደምንተራረም መስመር እየዘረጋን ነው:: ያለፈው አልፏል፣ የሆነው ሆኗል ለኢትዮጵያ ህዳሴ፣ ለፍትህ፣ ለዴሞክራሲና ለነጻነት ስንል ዛሬ ከአርበኞች ግንቦት ሰባት ጎን ቆመን ለአገራችን ካንሰር የሆነውን ሕወሐትን እናስወግድ::

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር !!

Previous Story

በሰሜን የአገሪቱ ክፍል የሚታየውን ውጥረት ተከትሎ አየር ሃይል በጠንቀቅ እንዲቆም ታዘዘ

Next Story

Hiber Radio: ፕ/ት ኦባማ ኢህአዴግና አማጽያኑን እንዲሸመግሉ መጠየቁ፣ አምንስቲ እንግሊዝ ለኢትዮጵያው አገዛዝ አፈና መጠንከርን ተጠቃሽ አደረገ፣ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ጦርነት መክፈት የፈጠረው መነቃቃት፣ እስራኤላዊው ትውልደ ኢትዮጵያዊው በሐማስ እጅ መውደቅ የፈጠረው ተቃውሞ፣ የጋዜጠኛ ርዮት ዓለሙ እና ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ቃለ መጠይቅ፣ የመን ሰንዓ ኤምባሲ ፊት ለፊት የወደቁ ኢትዮጵያውያን ያሉበት ስቃይ እና ሎሎችም

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop