**ድንቄም ምርጫ** – ነብሮ

ፍትሕ በተረገጠበትና የዴሞክራሲታዊ ሥርዓት በኃይል በታፈነበት አገር ሕዝብ መሪውን መምረጥ አይችልም።

              የምርጫ ጉዳይ ሲነሳ ወደ ኋላ ሄደን የዘመነ ኃይለሥላሴን፤የደርግን የምርጫ ሂደቶች ብናስብ ከዚህ በሰለጠነው ዓለም ከሚካሄደው ምርጫ ጋር በምንም ሁኔታ ሊመሳሰል እንደማይችል ሁላችንም ግልጽ የምንሆን ይመስለኛል።አድሎአዊና ሕዝብን ያላሳተፈ የገዥው መደብ የሚፈልጋቸውን እጩዎች መልምሎ በማቅረብ ሕዝቡን አስገድዶ እንዲመርጣቸው ማድረግ አይነተኛ ባሕሪው መሆኑን መጠራጠር አይኖርብንም።

የባሰ አለ እንዲሉ ከአንድ መንደር የተሰባሰቡና በዘረኝነት በሽታ የተመረዙት (ጎሰኞች) የአሁኖቹ ገዥዎቻችን ከ1997 ምርጫ በፊት ከምርጫው በፊትና በምርጫ ወቅት ሲፈጸም የነበረውን ሤራ በሚገባ የማውቀው ሲሆን የተቃዋሚ ኃይሎች(ድርጅቶች)ውስብስቡን የካድሬ መሰናክል አልፈው በፓርላማው ውስጥ ጥቂት አባሎቻቸውን በፓርላማ ውስጥ እንዲገቡ ያደርጉ ነበር።በፓርላማው ውስጥ ሃሳባቸውን የመግለጽና የማራመድ እድላቸው የጠበበ ቢሆንም የፓርላማውን ውሳኔ የሚነቅፍ የተቃውሞ ድምጽና የተአቅቦ ድምጽ ማስቆጠር ችለው ነበር።ከ1997 ምርጫ በኋላ ግን ዘረኝነት መራሹ ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ(ህወሃት)ከኢትዮጵያ ሕዝብ ተነጥሎ እንደቆመ ተንሳፎ የሚገኝ መሆኑን ሕዝብ በምርጫ ካርዱ ፍርዱን ሲሰጥ የበረገገው ገዥ ቡድን ረጅም እጁን የምርጫ ኮሮጆ ዘረፋ ውስጥ አስገባ ያልተመረጠውን ተመርጫለሁ አለ።ሰርቀሃል ድምጻችን መልስ ሲባል ደግሞ ግድያ፤እስራት፤ስብሰባ መከልከል፤ሰላማዊ ሰልፍ የማይደረግ መሆኑን አወጀ በግብርም ውሎ አየነው።ከዚያ በኋላ የዚህን ትውልድ አምክን ዘረኛ አገዛዝ እድሜ ለማስረዘም የደህንነት፤የመከላከያ፤የፖሊስና የልዩ ፖሊስ የክልል ፈጥኖ ደራሽ፤የካድሬው መዋቅር ትኩረት ተሰጥቶ እንዲጠናከር ተደረገ።አፈናው ግድያው ተስፋፍቶ ኢትዮጵያውያን በየጎዳናው ወድቀው የሚገኙበት ሁኔታ ተፈጠረ።

ይህ የምታዩት የህወሃት መለያ ሲሆን ከብጫው ላይ የተቀመጠው ዓርማ የጀርመን ናዚ ልዩ ምልክት የነበረ ሲሆን ዛሬ ኢትዮጵያውያን ህወሃትን ሲያነሱ የጀርመን ናዚን የጀርመን ናዚን ሲያነሱ ህወሃትን የሚያስታውሱበት ምክንያት ህወሃትና የጀርመን ናዚ በቆዳ ቀለም ቢለያዩም በተግባር አንድ ናቸው ብለው ስለሚያምኑ ነው። እኔ የዚህ ጹሑፍ አቅራቢም ህወሃትን ከጣሊያንና ጀርመን ፋሽስቶች ለይቸ አይደለም የምመለከተው።ለዚህ ጹሑፌ መነሻ የሆነኝ የፊታችን ግንቦት ለሚካሄደው ብሔራዊ ምርጫ የህወሃትን ሥርአት በሰላማዊ መንገድ ታግለን በምርጫ አቸንፈን ሥልጣን እንጨብጣለን ብለው በተነሱ ኃይሎች ላይ የህወሃት የምርጫ ቦርድ የፈጸመውን አሳፋሪ ድርጊት ተመልክቸ ሲሆን በምንም አይነት መስፈርያ ይሁን የተቃዋሚ ኃይሎች ለምርጫ ውድድር የሚያቀርቡትን እጩ ራሳቸው ወስነው ያቀርባሉ እንጅ የምርጫ ቦርድ ይህ ይመረጥ ይኸኛው አይመረጥ ብሎ የመወሰን ሞራሉም ሆነ ብቃት የለውም።ለዚያውም በእጣ! የምርጫ ኮሮጆ ገልብጦ ያልተመረጠውንና ሕዝብ አንቅሮ የተፈውን ተመርጠሃል ሕዝብ ይሆነኛል ያለውን በምርጫ ያቸነፈውን አልተመረጥክም ብሎ የሚቀጥፍ የአንድ ሥርአት አገልጋይና ተቋም አምኖ ምን አይነት ምርጫ እንደሚካሄድ ከወዲሁ መተንበዩ ነብይ የሚያሰኝ አይደለም።ለሥርአቱ አስጊ የሆኑ የተቃዋሚ ድርጅቶችን አንድነትና መኢአድን በኃይል አፍርሶ የየድርጅችን ንብረት ዘርፎ በሌሎቹ የተቃዋሚ ኃይሎች ጉያም ለመግባት ረጅሙን ዘራፊ እጁን ለማስገባት እያሴረ ያለው ህወሃትና ጉዳይ አስፈጻሚው የምርጫ ቦርድ ሕገ-መንግሥቱን እየናዱ መሆኑን ሊያጤኑ ይገባቸዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ልብን የሚነካዉ የኢትዮጵያዉያን ጉዞ በሳዑዲ አረቢያ

ህወሃት መሠረታዊ ችግሩ ድህነት ከሆነ በትግራይ ሕዝብም ይህ ችግር እንደ ዋነኛ ተደርጎ ከተወሰደ ሌሎችስ ብሎ ማሰብ የሚችል ተፈጥሮ በህወሃት ቤት እንዳማይኖር ቢታወቅም በትግራይ ለተፈጠረው የኢኮኖሚ መዳከምም ሆነ የንዋይ ጥማት የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚጠየቅበት አንዳችም ምክንያት ሊኖር አይገባውም የህወሃት መራሹ ቡድን በፈጠራ ውሸት የቆጥ የባጡን በመቀባጠር የሕዝብ እልቂት እንዲፈጠር በማድረግ በውንድብድና የካሄደው ዘረፋ፤ዜጎችን በተለይም ምሁሩንና አምራቹን ኃይል ከሀገር መንቀልና የመራሹ ቡድን እንባ ጠባቂዎችና ቤተሰቦች አገሪቱን ተስፋፍተው እንዲይዙና ሌላው ዜጋ በዘመናዊ ባርነት መቀጠል ወይም በሌሎች ላይ የደረሰው ጽዋ ሞልቶ እንዲፈስበት ማድረጉ የሚያስከትለውን መዘዝ መገንዘብ ባለመቻል የተፈፀመ ስለሆነ የዛሬው እዩኝ እዩኝ ነገ ሸሽጉኝ ሸሽጉኝን እንደሚያስከትል በድፍረት መናገር ይቻላል።

በአንድ ወቅት የህወሃቱ ፊታውራሪ ስብሃት ነጋ ከጋዜጠኛ ለቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ፡) እንዲህ ብሎ ነበር-ጋዜጠኛ አቶ ስብሃት ድሮ የሃብታምና የባለሥልጣን ልጅ ነበር ስኮላር ሽፕና የውጭ ትምህርት እድል ያገኝ የነበረው ዛሬ ደግሞ የእናንተ ልጆች የሚማሩት ወደ ውጭ አገር ሄደው ነው ሲባል(፡ አቶ ስብሃት ታዲያ እነሱ ያደረጉትን እኛ ብናደርገው ነውሩ ከምኑ ላይ ነው ብሎ ነበር በአራት ነጥብ የዘጋው።እንግዲህ ህወሃት እንዲህ ያሉትን ውዳቂዎችንና ፀረ-ሕዝቦችን አቅፎ ነው ኢትዮጵያን በኃይል አንበርክከን እንገዛታለን ካልሆነልን ደግሞ እናፈራርሳታልን የሚሉን።ከዚህ ወዲያ እብደት የለም እንዲህ ያሉት እብዶች የተሰባሰቡበት ህወሃት ነው ዛሬ በትረ ሥልጣኑን ጨብጦ እየገዛ ያለው።

አንዱ በአንዱ ላይ እምነት እንዳያሳድርና በጥርጣሬ እንዲተያይ ጦርነት ውስጥ እንዲገባ፤አንተ የዚህ አንተኛው ደግሞ የዚህኛው ዘር ነህ በማለት በዘር በማናከስ የሕዝብ ሰላም እንዲደፈርስ ያደረገው ህወሃት ነው። ሰሞኑን ደግሞ አንድ አስገራሚ ድርጊት ተፈፀመ ይህኸውም(ጥቂት ህወሃት የመለመላቸው የቅማንት  ተወላጆች ) በአማራ ገዥ መደብ እስከ ዛሬ ተገዝተናል አሁን በቃን ጐንደር የቅማንት አገር ስለሆነ ራሳችን በራሳችን ለማስተዳደር እንድንችል የራስ ገዝ አስተዳደር ይገባናል በሚል ሲንቀሳቀሱ ቆይተው አሁን የነአቶ በረከትና አዲሱ ለገሠን ይሁንታ አግኝተው ያልተጻፈ የታሪክ ድሪቶ አንግበው በደምና በስጋ የተቀላቀላቸው ወገናቸው ጋር ደም የሚያፋሥስ መንገድ መጀመራቸው ቀልጥፈው ተግባራቸው እኩይ ተግባር መሆኑን አውቀው እንዲያቆሙት ለማስገንዘብ ነው ይህን ጹሑፍ ያዘጋጀሁት። በዚህ ተግባር ግንባር ቀደም ሆነው የሚያራምዱትን በአካል ስለማውቃቸውም ጭምር ወንድማዊ ምክሬን ሊሰሙ እንደሚችሉ በማመን ነው። ህወሃትና የአማራውን ህዝብ ጋንጃ እየመታ የሚገኘውን ብ.አ.ዴ.ንን አምኖ ወደዚህ አጣብቂኝ ጉዳይ መግባት በፍጹም ስህተት ነው።የቅማንት ተወላጅ ለህወሃት የምርጫ ፍጆታ መዋል የለበትም፦የህወሃት ሥርዓትና የሥርአቱ አራማጆች መቀበሪያቸውን ቆፍረው ከመቃብር አፋፍ ላይ በሚገኙበት ወቅት መልካም ታሪክን ማጉደፍ አይገባም።ይህ ስርዓት ወዳቂ ነው በሀገር ጥፋትና እጁን በደም የነከረ ሁሉ በሰፈረው እንደሚሰፈርም ግልጽ ነው።ነገ የዛሬዎቹ ዳኞችና እኛ ፊት ለፊት እንገናኛለን፤ ነገ እኛና ይህወሃት ካድሬ እንገናኛለን፤ነገ የምርጫ ቦርድና እኛ እንገናኛለን፤ነገ የፌደራል ፖሊስና እኛ እንገናኛለን፤ነገ እኛና ፖሊስ እንገናኛለን፤ነገ የአጋዚ ሠራዊትና እኛ እንገናኛለን፤ነገ እኛና የክልል ፈጥኖ ደራሽ እንገናኛለን፤ለዘመናዊ ባርነት ወደ ዐረብ አገር የተላኩ እምቦቃቅላ ሴትና ወንድ ወጣቶችን መዝግበናል፤አገር ጥለው እንዲወጡ የተገደዱ ሙራንና ጋዜጠኞችን ዝርዝር ይዘናል፤ወህኒ ቤት ወርደው ሌትና ቀን እንደ እባብ እየተቀጠቀጡ የሚገኙትን ወጣት ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ድርጅት አመራሮችን እናውቃቸዋለን፤በመላ ኢትዮጵያ የመኖርና ሠርቶ የመብላት መብት የተነፈገው ዘሩ በመድሃኒት እንዲመክን የተደረገውን የአማራ ነገድ ሕዝብ ጉዳይ በሚገባ ተመዝግቦ እንዲቀመጥ ተደርጓል፤ከወሎና ጎንደር ተነጥቆ ወደ ትግራይ የሄደውን መሬት በሚገባ እናውቀዋለን ይህን ሁሉ ህወሃትና መንገድ መሪዎቹ የሚከፍሉት እዳ እንደሆነ ሊያውቁት ይገባል። በዚህ አጋጣሚ አቶ በየነ አስማረና አበበ ንጋቱን አመስግኘ ማለፍ እወዳለሁ።« በወደቀ ግንድ ምሳር ይበዛበታል እንዲሉ » ጣሊያን ጎንደር ሲገባ የተጠቀመበትን ፕሮፓጋንዳ ያነገበው የህወሃት ቡድን ኢትዮጵያን ለመበታተን ሲል የሚያራምደውን የጎሳ ፖለቲካ የተጋቱ አውቆ አጥፊ የቅማንት ተወላጆችንና ሌሎች የተለያዩ በአማራው ነገድ ህዝብ ክልል የሚኖሩ ጎሳዎችን በማነሳሳት በጎሳ መራሹ ቡድን ጣቱን የቀሰረውን ሕዝብ አስተሳሰብና አመለካከት አቅጣጫውን እንዲስት ለማድረግ የሚጠቀምበትን ሕዝብን በሕዝብ የማናከስ ሤራ እያራመዱ ይገኛሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ 2ኛ ዓመት ቅጽ 2 ቁ 72 - PDF

24 ዓመት በመድፈን ላይ የሚገኘው የህወሃት አገዛዝ በሚያካሂዳቸው ምርጫዎች አንድም ቀን ፍትሃዊነት ያልታየበትና የተጭበረበረ መሆኑ እንዳለ ሆኖ በምርጫ ወቅት ለሕዝብ የሚገባቸውን ቃሎች ከመካዱ አልፎ በተቃራኒው እንደሚተገብራቸው ይታወቃል።የዘንድሮ ደግሞ በጣም የለየለትና አውሬነቱን በግልጽ የሳየበት ሁኔታ ላይ ደርሷል ሁላችንም የምግባባበት አንድ መሠረታዊ ጉዳይ ህወሃት ለአፍታም ቢሆን ሥልጣን ከእጁ ካፈተለከ የሚደርስበትንና የሚከፍለውን ዋጋ ስለሚያውቅ በሰላማዊ መንገድ ሥልጣን ያስረክባል ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው። ዋናው አነጋጋሪ ጉዳይ ሕዝብ ካለፈው ተመክሮ የማያገኘውና አልመርጥም የማይልበት ምክንያት ምንድን ነው የሚለው ይሆናል።የሚያሰድድን፤የሚገድልን፤አስሮ የሚያሰቃይን፤ዘር በማጥፋት ላይ የተሰማራን ነብሰ-ገዳይ ቡድንን መርጦ በሥልጣን ላይ ማስቀመጥ አገርን ከመገደል የከፋ ወንጀል ነው።ስለዚህ ሕዝቡ የዘንድሮውን ምርጫ በእምብይታ ሊያስተናግደው ይገባል።

ነብሮ ነኝ ከሰ/አሜሪካ

Share