ሕወሃትና ሕግ ጠበኞች ናቸው – ግርማ ካሳ

የሚከተሉት በቀጥታ ከኢትዮጵያ ሕገ መንግስት የተወሰዱ ናቸው።

አንቀጽ 20፣ ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2

«ማንኛውም ሰው ያለምንም ጣልቃ ገብነት የመሰለዉን አመለካከት ለመያዝ ይችላል።

ማንኛውም ሰው ያለምንም ጣልቃ ገብነት ሐሳቡን የመግለጽ ነጻነት አለው። ይህ ነጻነት በሀገር ዉስጥም ሆነ ከሀገር ዉጭ  ወሰን ሳይደረግበት በቃልም ሆነ በጽሁፍ ወይም በሕትመት፣ በሥነ ጥበብ መልክ ወይም በመረጠው በማናኝዉም የማሰራጫ ዘዴ፣ ማንኛዉንም ዓይነት መረጃና ሐሳብ የመሰብሰብ፣ የመቀበልና የማሰራጨት ነጻነቶችን ያካትታል»

አንቀጽ 38 ንዑስ አንቀጽ ሐ

«ማንኛዉም ኢትዮጵያዉ ዜጋ፣ በቀለም፣ በዘር፣ በብሄር. በብሄረሰብ፣ በጾታ፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ ወይም በሌላ አመለካከት ወይም በሌላ አቋም ላይ የተመሰረተ ልዩነት ሳይደረግበት በማናቸዉም የመንግስት ደረጃ በየጊዜው በሚካሄድ ምርጫ የመምረጥና የመመረጥ»

በርካታ የህወሃት ባለስልጣናትና ካድሬዎች ስለ ሕግ እየደጋገሙ ያወራሉ። ስለ ሕግ፣ ስለ ሕግ መንግስቱ የሚደረገዉን ዉይይት አንፈራም። በአንቀጽ 20 መሰረት፣ «ስለሚያገባን እንጦምራለን»  በድብቅ ሳይሆን በሶሻል ሜዲያው፣ ድብቅ ስም ይዘው ሳይሆን እናት አባቶቻቸው የሰጧቸውን ስም ይዘው፣ ፎቶዋቸውን ለጥፈው በይፋ አስተያየቶችን የሰጡ፣ የጦመሩ፣ ዞን ዘጠኞች ለምን ታሰሩ ? ብእር አንስተው በይፋ የጻፉ እነ ርዮት አለሙ፣ እስክንድር ነጋ፣ ዉብሸት ታዬ፣ ተመስገን ደሳለኝ የመሳሰሉት ለምን ታሰሩ ? አንቀጽ 20 «ማናቸውንም» የሚል ቃላት አካቶ የለም ወይ ? እስቲ ይመለስልን !!!

አንቀጽ 38 ማንኛውም ዜጋ የመምረጥና የመመረጥ መብት አለው። ታዲያ ከ200 በላይ የሰማያዊ ፓርቲ ተወካዮች ተመራጭ እጩ እንዳይሆኑ ለምን ተሰረዙ ? ኦሮምኛ አትናገሩም ፣ የዚያ ደርጅት አባል ነበራችሁ ፣ እጣ አልወጣላችሁም .፣ ወዘተረፈ እየተባለ ዜጎች እንዳይመረጡ መሰረዝ ሕግ መንግስቱን በአፍጢሙ መድፋት አይደለም ወይ ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአባ መላ (ብርሃኑ ዳምጤ) መገለባበጥና ኢሳት

ታዲያ ህወሃት፣  ራሱ የማያከብረዉን ሕግ፣  ሌሎች እንዲያከብሩለት ለምን ይጠበቃል ? ሕግ መንግስቱን በአፍጢሙ ደፍቶት ስለ ሕግ መንግስቱ የማዉራት ምን ሞራል ኦቶሪቲ አለው ?

አገር ዉስጥ ላሉ ድርጅቶች አንዳንድ ሐሳቦች – ናኦሚን በጋሻ

ህወሃት ሕግን የማያከበር አራዊተ ስርዓት ነው።ሕግን ከማያከበር ቡድን ጋር ሕጋዊ ትግል የራሱ ጠቃሚ አስተዋጾ ቢኖረዉም ዘልቆ አይሄድም። ታዲያ አገር ቤት ያሉ ሰላማዊና ሕጋዊ የፖለቲካ ድርጅቶች ምንድን ነው ማድረግ ያለባቸው ? አንዳንድ ሐሳቦችን ላስቀምጥ፡

  1. በአቶ በላይ የሚመራው የአንድነት ፓርቲ ፣ እውቅናውን ለተለጣፊው ቡድን ቢሰጥበትም፣ በብሄራዊ ምክር ቤት አመራር አባላት አዝማችነት፣ አብዛኞቹ የአንድነት አባላት ከሰማያዊ ወንድሞቻቸው ጋር ትግሉን ቀጥለዋል። ይሄ በስፋት ቢቀጥል ጥሩ ነው።
  2. የአንድነት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት የተወሰኑቱ፣ ንብረት ( እንደ ማተሚያ ማሽን የመሳሰሉት) ለማስመለስና በፓርቲው ላይ የተወሰደውን እርምጃ ሕገ ወጥ መሆኑን በመከራከር ወደ ፍርድ ቤት ሄደዋል። ፍርድ ቤቱ ምን ሊወስን እንደሚችል ቢታወቅም፣ እስከ መጨረሻ ተቋማትን በመፈተሽ የበለጣ ማጋለጡ ጠቃሚ ነው።
  3. የማታ ማታ የአንድነት ሕጋዊ እውቃና በፍርድ ቤት ዉሳኔ ተመለሰም አልተመለስም ሰማያዊና አንድነት እሣት በተነሳ ጊዜ በተግባር እንደተዋሃዱት፣ ቀጣዩ ትግላቸውንም ፣ መኢአድና የትብብሩ ሌሎች ድርጅቶችን በማሰባሰብ መቀጠሉ ትልቅ ትኩረት ሊሰጥበት ይገባል። አንድ ጠንካራ ኃይል ይዘው መዉጣት አለባቸው።
  4. ከመድረክ ጋር በጋራ ጉዳዮች አብሮ የሚሰራበት መንገድ መመቻቸት አለበት።
  5. ከጥቂት ወራት በኋላ የሚደረገውን ምርጫ ሰማያዊና መድረክ ቦይኮት እንደሚያደረጉት በመገልጽ ምርጫው እንዲራዘም በጋራ ቢጠየቁ ጥሩ ነው። መኢአድ ምርጫዉን ቦይኮት ሊያደርግ እንደሚችል ይጠበቃል። በነ አቶ በላይ የሚመራው አንድነት፣ መኢአድ ፣ ሰማያዊና መድረክ በምርጫ ቦርድ ሕገ ወጥ የሆኑ እርምጃዎች እንደተወሰዱ የሚያሳዩ ሰነዶችን በማቅረብ ( በጣም ብዙ አሉ) ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ቢወስዱ ጥሩ ነው። ፍርድ ቤቱ ምርጫዉን ማራዘም ይችላል።  ምርጫው እንዲራዘምም የዲፕሎማሲ ግፊት ማድረግ ይኖርባቸዋል።
ተጨማሪ ያንብቡ:  የሕግ የበላይነትን ሊያስከብር ያልቻለ መንግስት በሕዝብ እምነት ሊጣልበት አይችልም

ከዚህ ዉጭ አገር ቤት ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያደርጉት ነገር አይኖርም። ወደ ምርጫው ገብተው ጥቂት የፓርላማ ወንበር ሊያገኙ ይችላሉ። ሆኖም ከዚያ ምንም ሊገኝ እንደማይችል መቼም እነ ዶር መራራ፣ ዶር በየነ በሚገባ ያወቁታል። ምርጫው ካልተራዘመና አዲስ ምርጫ ቦርድ ካልመጣ የሚያመጣው ዉጤት አይኖርም። ምርጫውን ይርሱት !!!! ከዚህ በኋላ ምርጫ ፣ ምርጫ ቢሉ የበለጠ ህዝብ ይታዘባቸዋል። በዚህ ምርጫም ተጨባጭ ነገር ካላስገኙ ይቅርታ አይደረግላቸውም። ያስቡበት እላለሁ።

በመጨረሻ አንድ በጣም ትልቅ ነገር ልናገር። ሕዝቡ በሚያደርጋቸው ሕገ ወጥ ግን ሰላማዊ የእምቢተኝነት ትግል፣ ወይንም አገዛዙ በዉስጡ ባለው ችግር መፈረካከስ ካጋጠመው፣ አገሪቷ ወደ ቀዉስ ልትሄድ ትችላለች።  ጠንካራ አማራጭ የሚሆኑ ድርጅቶች በአገር ቤት ሁልጊዜ መኖር አለባቸው። በመሆኑም ተደራጅቶ መጠበቁ ጥሩ ነው።

 

Share