ብልጽግናና ባሕል

በዳንኤልክብረት

መንገድ አቋርጣለሁ፡፡ በእግሬ፡፡ ሁለት ጎልማሶች በመንገዱ ማቋረጫ ላይ ተገናኙ፡፡ ከሁለት አንዳቸው ቀድመው ወይም ተከትለው ማለፍ አለባቸው፡፡ ሁለቱም ቆሙ፡፡ ከዚያም አንዱ ሌላኛው ቀድሞ ያልፍ ዘንድ ጋበዘ፤ የተጋበዘውም ጋባዡ እንዲያልፍ ለመነ፡፡ ግብዣው ጥቂት ደቂቃዎች ፈጀ፡፡ እኛም ከኋላ ያለነው ትኅትናቸውን አድንቀን በትዕግሥት ቆምን፡፡ በመጨረሻ አንደኛው እያመሰገነ አለፈ፡፡ ሌላኛውም ‹ምን አይደል›› እያለ አሳልፎ አለፈ፡፡

ደግሞ ሄድኩኝ፤ እነሆም በአንድ መስቀለኛ የአስፋልት መንገድ ላይ ደረስኩ፡፡ መኪኖቹ ከአራቱም አቅጣጫ ይመጣሉ፡፡ ሁሉም ወደ መስቀለኛው መጋጠሚያ ይገባሉ፡፡ አራቱም በአንድ ጊዜ ለማለፍ ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን አይችሉምና የመኪኖቹ አፍንጫዎቻቸው ተፋጥጠው ይቆማሉ፡፡ ለማለፍ እንጂ ለማሳለፍ የሚጥር አላይም፡፡ አራቱም በመስኮት ብቅ ብለው ‹ወደ ኋላ በልልኝ ልለፍ› ይላሉ፡፡ እነርሱ ሲከራከሩ ሌሎች ባለመኪኖችም ይመጣሉ፡፡ እንደ ዘንዶ ተጣጥፈው በአራቱ መኪኖች መካከል ለማለፍ ይሞክራሉ፡፡ እነዚያ ቀድመው የመጡትም ይናደዱና ወደ ፊት ገፍተው መንገዱን ያጠባሉ፡፡ በዚህ የተነሣም እነዚያም ከኋላ የመጡት በተራቸው ይቆማሉ፡፡ ሁሉም ቀድሞ ለማለፍ በሚያደርገው ፍትጊያ ሁሉም ይቆማሉ፡፡ እለፍ፣ እለፍ ተባብሎ መገባበዝ የለም፡፡

እየገረመኝ አልፋለሁ፡፡
አልፌም አንድ ያረጀ የዕድር ድንኳን የተጣለበት ጋ እደርሳለሁ፡፡ ድንኳኑ ለሁሉም አይበቃምና ከድንኳኑ ውጭ አግዳሚ ወንበር ላይ ሰዎች ተቀምጠዋል፡፡ ሌሎች ልቅሶ ደራሾ ሲመጡ ቀድመው ተቀምጠው የነበሩት ግር ብለው ይነሡና ወንበር ይለቃሉ፡፡ ‹ይቀመጡ አልቀመጥም› የግብዣ ግብግብ ይፈጠራል፡፡ በመካከል ገላጋይ ገብቶ እንግዳ ይቀመጣል፡፡ ‹ኖር› መባባል መልቶ ሰፍቶ ይከናወናል፡፡ ሰውን በአግዳሚዎቹ መካከል ለማሳለፍ ሁሉም እግሩን ያነሣል፣ ወይ ራሱ ይነሣል፡፡

እያደነቅኩ አለፍኩ፡፡
የማልፍበት መንገድ በግራ በቀኝ ቤት ሠሪዎች አሸዋና ጠጠር፣ ድንጋይና ብረት አውርደውበታል፡፡ እዚህም እዚያም ተጀምረው ያላለቁ፣ አልቀው ደግሞ ሰው የገባባቸው ቤቶች አሉ፡፡ አሸዋውና ድንጋዩ፣ ጠጠሩና ብረቱ መሐል መንገድ ላይ ይቆለላል፡፡ ሰው በምን ይተላለፋል? መኪና በምን ያልፋል? ብሎ ነገር የለም፡፡ ሁሉም በቤቱ ፊት ለፊት ይደፋል፡፡ ሲብሰው ደግሞ መሐል መንገድ ላይ ሲሚንቶ ያቦካል፣ ድንጋይ ይፈልጣል፡፡ እዚያ ድንኳን ውስጥ የነበረው ‹ኖር› መባባል፣ በአግዳሚዎች መካከል ሰው ለማሳለፍ መከራ መቀበል፣ እንግዳ ሲመጣ ከመቀመጫ ተነሥቶ ክብር መስጠት በቤት ሠሪዎቹ ዘንድ የለም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ተሂዶበት ከሚፈለገው ቦታ ባላደረሰ መንገድ ተመላልሶ መጓዝ ችግሩ የመንገዱ ሣይሆን የተጓዡ ነው

ይህንንም አለፍኩት፡፡
እነሆም በኑሮ ደከም ያሉ ሰዎች ወደሚኖሩበት መንደር ደረስኩ፤ የቆርቆሮ ጣራና የቆርቆሮ ግድግዳ ወደሚበዛባቸው፡፡ አቡኪዎቻቸው በእድሜ ገፍተው በሞቱ የጭቃ ግድግዳዎች ወደተሠሩ፤ ተቃቅፈው እንደሚሄዱ የሦስተኛ ክፍል ተማሪዎች ትከሻ ለትከሻ የተደጋገፉ ግድግዳዎች ወዳሏቸው ቤቶች መንደር፡፡ በዚያም ሳቋርጥ ‹‹ወ/ሮ እንትና ደኅና አደሩ፤ ምነው ሰሞኑን አላየሁዎትም› የሚል የጎረቤት ድምጽ ሰማሁ፡፡ ወ/ሮ እንትናም አብራሩ፡፡ እልፍ ስል ደግሞ ‹‹እ-ን-ት-ና፣ ቡ-ና-ው ፈ-ል-ቷ-ል› የሚል ዘለግ ያለ የግብዣ ጥሪ አዳመጥኩ፡፡ ደግሞ ልጆቹም ሰብሰብ ብለው በመንደሩ መካከል ከምትገኘው የእጣቢ መድፊያ መስክ ላይ አፈር ልሰው አፈር መስለው ይጫወታሉ፡፡ ውሾም ከልጆቹ ጋ ይዘላሉ፡፡
እነሆ ያንንም መንደር አለፍኩትና ከመንገዱ ማዶ ተሻገርኩ፡፡
ይኼ ደግሞ የባዕለ ጸጎች ሠፈር ነው፡፡ እያንዳንዱ ግን በአጥር ተከልሏል፡፡ ወደዚያ መንደር ለማለፍም እንደ መንግሥት መሥሪያ ቤት መታወቂያ ይጠየቃል፤ ወደ ውስጥ ስትዘልቁ እንደ ሙታን መንደር ጭር ያለ ነው፡፡ መስክ ላይ ተሰባስበው የሚጫወቱ ልጆች አታዩም፤ ሁሉም ወይ ጌም ላይ ናቸው ወይም ቲቪ እያዩ ነው፡፡ አለያም ግቢያቸው ውስጥ ናቸው፡፡ ወላጆቻቸውም ግቢ ግቢያቸውን ዘግተው አይጠያየቁም፡፡ እንዲያውም ጎረቤታቸው ማን እንደሆነ የማያውቁም አሉ፤ ከግቢያቸው ሲወጡ ‹‹ወ/ሮ እገሊት ደኅና አደሩ፤ ምነው ሰሞኑን አይታዩምሳ›› ብለው አይጠይቁም፡፡

በዚህም ተገረምኩ፤ አለፍኩም፡፡
እነሆም ሰዎች ታክሲ ለመሣፈር ወረፋ የያዙበት ቦታ ደረስኩ፡፡ ረዥም ሰልፍ፡፡ ልጆች፣ ወጣቶች፣ አረጋውያን፣ በከዘራ የሚሄዱ፣ ጎንበስ ብለው መሬት መሬት የሚያዩ፣ ጥላ የያዙ፣ በወረቀት ፀሐይን የሚከልሉ፣ ሁሉም ተሰልፈው የታክሲውን መምጣት ይጠባበቃሉ፡፡ ቆምኩና አየኋቸው፡፡ ታክሲዎቹ በመጡ ቁጥር የቻሉትን ሰው ይጭናሉ፡፡ በዚያ ፀሐይ ጨዋነታቸው ይነበባል፡፡ ራሳቸው ተራ አስከባሪዎች ከሚፈጥሩት ግርግር በቀር ግርግር ለመፍጠር የሚቻኮል ያንን ያህል ሰው የለም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ይድረስ ለወዳጄ....

ይህንንም አይቼ አለፍኩ፡፡
አለፍኩና ወደ አንድ ማደያ ዘንድ ደረስኩ፡፡ የነዳጅ ወረፋው የመንገዱን ጥግ የመኪና መሸጫ አስመስሎታል፡፡ ወደ ማደያው አካባቢ ሸውደው ለማለፍ የሚሞክሩ፤ አልፈው የሚሄዱ መስለው በሰው ሰልፍ የሚገቡ፣ ያንን ረዥም ሰልፍ እያዩ ሌላ ሰልፍ የሚፈጥሩ፣ መኪናቸውን አቁመው ጓደኛቸውን የሚያስገቡ ባለመኪኖች ይታያሉ፡፡ ከመኪኖቻቸው ውስጥ የብልግና ስድቦች ይወጣሉ፤ ይወራረፋሉ፤ ታክሲ እንደሚጠብቁት ሰዎች ፀሐይና አቧራ አያገኛቸውም፤ ከታክሲ ጠባቂዎቹ በላይ ግን ትዕግሥት የለሾች ናቸው፡፡ በመካከል ነዳጅ አልቋል ሊባል እንደሚችል ያውቃሉ፤ ነገር ግን ከኋላቸው የተሰለፉት ሰዎች ድካም ምንም ሳይመስላቸው ከነዳጅ ታንከራቸው በተጨማሪ በጀሪካቻኖቸው ይሞላሉ፡፡

እነሆ ይህንንም ታዝቤ አለፍኩ፡፡
አሁን ግን ዝም ብዬ አላለፍኩም፤ ያሳስበኝ ጀመር፡፡ እንዴው የኛ በጎ በጎ ባሕላችን በድህነት ላይ ነው እንዴ የተመሠረተው? አልኩ፡፡ በድሃው ማኅበረሰብ አካባቢ የምናያቸው የመከባበር፣ የመተባበር፣ የመጠያየቅ፣ የመረዳዳት፣ የመተሳሰብ ባሕሎች የተሻለ ገቢ ያለው ማኅበረሰባችን ላይ ሲታዩ ወይ ጠፍተዋል ወይም ቀንሰዋል፡፡ የዘመዶቻቸውን ልጆች እንደራሳቸው አድርገው የሚያሳድጉ ክቡራን ወላጆችን በብዛት የምናየው ድሃው ወገናችን ዘንድ ነው፡፡ የአንድ ሰው ጉዳይ አሳስቦት የት ነበርክ? ብሎ የሚየጠይቀው፣ ያለውን ተካፍሎ ለመብላት የሚተጋው፣ ጉርብትናው የሚያምረው፣ መከባበሩ ሞልቶ የሚፈሰው እዚህ ደሃው ወገናችን ላይ ነው፡፡

የተሻለ ኑሮና ዕውቀት ያለው ጋ ስትሄዱ ግለሰባዊነት፣ ብቸኛነትና ድንበርተኛነት ሠፍኖ ታዩታላችሁ፡፡ የማይለብሳቸው ብዙ ልብሶች አሉት፣ ግን አይሰጥም፤ የማይመገበው ትርፍ ምግብ አለው ግን፤ ግን አይመጸውተውም፡፡ ታላላቅ ግቢ አለ፤ ነገር ግን ተረት የሚያወሩ፣ ባሕል የሚያስተምሩ አክስቶች፣ አጎቶችና አያቶች አይኖሩበትም፡፡

እነዚያን የመንደር ሐኪሞች፣ እነዚያን እጆቻችንን አሽተው ያዳኑን ወጌሾች፣ እነዚያን ሐረግሬሳ በጥሰው፣ ስሚዛ ጨምቀው ያዳኑንን የመንደር እናቶችን አስቡና የአሁኑን የሕክምና ሥነ ምግባር አስቡት፡፡ ጠዋት ከዕንቅልፍ ብንቀሰቅሳቸው፣ በምሳ ሰዓት ብንሄድባቸው፣ በእኩለ ሌሊት ብንጠራቸው ለመንደሩ ሰዎች የነበራቸው ትጋት፤ ዛሬ ከዘመናዊ የሕክምና ተቋማት ለምን ተወሰደ? ይበልጥ ባወቅንና ይበልጥ ባገኘን ቁጥር ይበልጥ ጨዋነት ይጠፋብናል ማለት ነው? ከጉልት ሻጮች ይልቅ በሱፐር ማርኬቶች፣ ከመንደር ሱቆች ይልቅ በገበያ አዳራሾች ለምን ማጭበርበሩ በዛ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከወያኔ በከፋ የኦሮሞ ኦነግ/አፒዲ አደገኞች ናቸው ብዬ ነበር - ሰርፀ ደስታ

ከተለያየ ጎሳና ነገድ ይበልጥ ተዋሕዶ፣ ተጋብቶና ተዛምዶ የምናገኘው የትኛውን ኅብረተሰብ ነው? ከውስኪ ቤትና ከጠጅ ቤት ኢትዮጵያን የሚያሳየን የትኛው ነው? በሀገር ቤት ከሚኖረውና በውጭ ከሚኖረው የትኛው ነው ጠባቡ? በአውቶቡስ ከሚሄድና በአውሮፕላን ከሚሄደው የትኛው ነው የሚገባበዘው? የትኛውስ ነው የሚጨዋወተው?

ባደግንና በተለወጥን ቁጥር፣ ዕውቀትና ሀብትም ባፈራን ቁጥር፣ የኑሮ መደባችንም በተቀየረ ቁጥር እነዚያን የኛ ናቸው የምንላቸውን ወጎች፣ ልማዶች፣ ሥነ ምግባሮችና ባሕሎች እየተውናቸው እንሄዳለን ማለት ነው? ሥልጣኔና ብልጽግና የበጎ ባሕል ማጥፊያ ናቸው እንዴ? ኢትዮጵያዊ የምላቸው ባሕሎች፣ ወጎችና ልማዶች ካልተማረው ይልቅ በተማረው፣ ከሀብታሙ ይልቅ በደሃው ማኅረሰብ ዘንድ ይበልጥ የሚከበሩትና የሚጠበቁት ለምንድን ነው? ይበልጥ በበለጸግን ቁጥር፣ ይበልጥስ በተማርን ቁጥር ይበልጥ ኢትዮጵያዊነታችንን እንለቃለን ወይስ?

5 Comments

  1. Deyaqon Daniel

    fiyel wedeya qizemzem wedeh !!!
    este sele Betehrestyan bandoch awran yeleq !!!!!
    mengaw tebetno ,, tebaqe aten yele ende ?
    este sele weyane cadre abatochachin awgan ? ketomerk ayqer !!!!
    selefersew bete kiresteyan awgan

    sele Fiteh ,,badebabay selemechfechew wegenachin !!
    be Ethiopia selemefesew inbana dem!! toner este !!!!!!

  2. DANILE ANTE YE BETKERSTYAN AGELGAYE MSELKEGENE ESITY EZA AKBABI MESQLE YEZEW MIYAWNBDU QESAWESETEN TMLKETELEN MEN YAZORHALE MNDER LMDER? LOL

Comments are closed.

Share