40ኛው የህጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እና “ልማታዊው ሲኖዶስ”

“የብጹዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ቦታ አሁንም ክፍት ስለሆነ በቦታው ተጠባባቂ/ምክትል ፓትርያርክ ቢመረጥ መልካም ነው”

 

ታዬ ብርሀኑ

በስደት ላይ የሚገኘው ህጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ 40ኛውን መደበኛ ጉባኤ ከጥቅምት 26-28/2007 ዓ/ም በኮሎምበስ ኦሀዮ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ካቴድራል የተካሄደው ጉባኤ ስኬታማ ነበር። እንደዚህ ዓይነቱ የተሳካ ስብሰባ በኦሀዮ መደረጉ የራሱ የሆነ ታሪካዊ እሴት አለው። ይህም የቅዱስ ሲኖዶስ ድጋፍ ኮሚቴ ብለው የተሰባሰቡ ግለሰቦች በአባቶቻችን መሃል ከሶስት ዓመታት በፊት የጫሩት የመለያየት እሳት ግብዓተ መሬቱ እዛው ቦታ ላይ መፈጸሙ ነው። በእርግጥ አባቶች የነዚህን ስብስቦች አካሄድ ተረድተው ወደ አንድ ገጽ ከመጡ አንድ ዓመት አስቆጥረዋል ሆኖም ከማወጅ በፊት አንድነቱ ይርጋ በሚል ስንጠባበቅ ቆይተን 40ኛው የሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ያንጸባረቀውን መልካም ገጽታ እኛ ምኦመናንን ስላስደሰተ እግዚአብሄርን ለማክበርና ለማመሰገን እንዲሁም ደስታችንን እንገልጽ ዘንድ ለመጻፍ ወደድኩ።

የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በቅዱስ ፓትርያርኩ መልካም ፈቃድ በብጹእ አቡነ መልከጼዴቅ ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊነት ዘመናትን በተሻገረ በጠለቀና በበሳል የአመራር ችሎታ ስብሰባው ተመርቶ ወቅታዊና አበይት በሆኑ ርዕሶች ላይ ተነጋግሮ ጉባኤው በስኬት ተፈጽሟል። ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ ስለ ህገ ቤተክርስቲያን መከበርና ሰለ ስብከተ ወንጌል መስፋፋት በስፋት የተነጋገረበት ሲሆን ይህን አሰመልክቶ ከተለያየ አቅጣጫ የቀረቡት አስተያየቶች በተገቢው መንገድ ሁሉም ተስተናግደው ወደ ውሳኔ ሃሳብ ተደርሷል። ቅዱስ ሲኖዶሱ ከተወያየበት ወቅታዊ ርዕሶች በደማቁ ሊሰመርበት የሚገባው ሀገራችንን ኢትዮጵያ ውስጥ በገዢው ፓርቲ እየተካሄደ ያለውን ከርዕስትና ከጉልት ማፈናቀል፣ የዘር ማጥፋትና ማጽዳት ወንጀል፤ የፍትህ እጦት፤ የሰብዓዊ መብት ጥሰት፤ በሃይማኖት ተቋም ውስጥ የሚያደርግውን ጣልቃ ገብነት አውግዞ በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን የኢትዮጵያን ህዝብን ሰቆቃ የሚያስቆመው ከህዝብ ትግል ጋር እግዚአብሔር በመሆኑ በያዝነው ጾመ ነቢያት ወቅት መላው ኦርቶዶክሳውያን በአጥቢያው በሚገኘው አብያተ ክርስቲያን እየተገኘ የምህላ ጸሎት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርቧል። በመሆኑም ካለፈው እሁድ ጀምሮ በሕጋዊ ቅዱስ ጥላ ጥር በታቀፉ በመላው አለም በሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ዓብያተ ክርስቲያናት ተጀምሯል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የትዉልድ አተላዎች ከመሆን ይሰዉረን -  ናኦሚን በጋሻው

ቅዱስ ሲኖዶስ «እኔስ የመረጥኩት ጾም ይህን አይደለምን የበደልን ሰንሰለት ትፈቱ ዘንድ የቀንበሩን ማነቆ ታላቅቁ ዘንድ የተጨቆኑትን ነጻ ታወጡ ዘንድ ቀንበሩን ሁሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን?» ኢሳ 58፥6 በሚለው አምላካዊ ቃል መሰረት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሰንሰለት ህዝቡ ይ,ፈታ ዘንድ፣የኢፍትሐዊነት ቀንበር በኢትዮጵያ ምድር እንዲሰበርና ዘረኝነት በኢትዮጵያ ምድር እንዲገደብና በጠቅላላው ኢትዮጵያውያን ከጭቆና ነጻ ይወጡ ዘንድ ጌታ የመረጠውን ጾም አውጇል። መንፈስ ቅዱስ የሚመራው ሲኖዶስ ፣ በሐዋርያት ወንበር ላይ የተቀመጡ እውነተኛ አባቶች ስለ ምእመናን ሕይወት ግድ ይላቸዋል በክርስቶስ ደም ዋጋ ተክፍሎባቸዋልና። በስደት ያሉት ብጹዓን አባቶችና ካሕናት ሊቀ ካህናቸው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚከተለው ያስተማራቸውን በቅጡ አስተውለው የጌታ አመትን እየሰበኩ እየገኛሉ። “የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩትም መፈታትን ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፥ የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል” ሉቃስ 4፥18

በአንፃሩ ሀገር ቤት የሚገኙው ህገወጡ ሲኖዶስ ስብሰባቸው ጨርሰው ያወጡትን መገለጫ በዘሀበሻ ድረ ገጽና በሐራ ተዋህዶ ላይ ተለጥፎ እንዳየሁት የመጀመሪያ ጥሪ ለሕብረተሰቡ የቀረበው ልማታዊ ጥሪ ነው በተለይም የአባይን ግድብ አሰመልክቶ። የአባይ ግድብ ጉዳይ መንፈሳዊ አባቶችን ጨምሮ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ቢሆንም መንፈሳዊ አባቶች ማስቀደም ያለባችው የተጠሩበት ሰማያዊ ጉዳይ ነው። አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአገልግሎት የጠራችው የሰው ሕይወት እንዲያድኑ እንጁ ለሕንፃ ልማት አይደለም። ለነገሩ መንበሩን የተቆጣጠሩት በጦር መሳሪያ ሃይል እንጂ በመንፈስ ቅዱስ ሃይል ስላልሆነ ሲጀመርም ቅድስና የሌለው ሲኖዶስ ነው። በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ የሚለው ስያሜ አይገባውም ይልቁንም “ልማታዊ” ሲኖዶስ የሚለውን ስያሜ ይገባችዋል። በጣም የሚያሳዝነው ጉዳይ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረው ወገናቸውን መረገጥ በዓይናችው እያዩ የስላሲዎች ህንጻ የሆነው ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ኢ-ፍትሐዊነት ዓይናቸውን ጨፍነው እያለፉ ክርስቶስ በደሙ የዋጃቸውን የአማራውና አኝዋኩ ሕዝብ ላይ የተፈጸመውን የዘር ማጽዳት ዘመቻ እየሰሙ እንዳልሰሙ አልፈው ያልተጠሩበትን ስለ ግዑዙ አባይ መገደብ ያወጡት መገለጫ ምንም መንፈሳዊ መዓዛ የሌለውና በሞራላዊ መስፈርት ሲመዘን እጅግ የወረደ መግለጫ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን መጥላት ፤ ማጥላለት ኢትዮጵያዊነት ሊሆን አይችል!!!

ተመዝንክ ግን ቀለህ ተገኘህ የሚለው የመጽሃፍ ቅዱስ ቃል ለነዚህ የአባቶች ስብስብ ተገቢ ቃል ነው (ዳንኤል 5፡26) ። ፍትህ እንደዚሁም ሰብዓዊ መብት እኮ በእግዚአብሔር አምሳል ለተፈጠረ ሰው ስማያዊ ስጦታ ነው። ሰለሆነም የዜጎች ሰብዓዊ መብት ሲጣስ እንዲከበር መጮህ፣ ጸልዩ ብላ ማዘዝ እንዲሁም ጸሎት ብቻ ማዘዝ ሳይሆን መብቱንና ነጻነቱን ለማስከበር የበኩሉን እንዲያረግ ማዘዝ የቤተክርስቲያን ተልዕኮ ነው። ሩቅ ሳንሄድ ኢትዮጲያዊውያኑ ብጹዕ አቡነ ጴጥሮስና አቡነ ሚካኤል ለዚህ ምግባር ዓይነተኛ ምሳሌዎች ናቸው። ሀገር እየደማ፣ ሀገር እየቆሰለ ህዝቡ ርስቱን እየቀማ በሀገሩ እየተሰደደ፣ በሀስት ክስ እያታሰረና እየሞተ ልክ በኢያሪኮ በወንጀለኞች ተደብድቦ ወድቆ በሕይወትና በሞት መካከል የነበረውን ሰው የአይሁድ ካህናት (ፈሪሳውያን) እንዳላዩ ገለል ብለው እንዳለፉት (ሉቃ 10፥30-35) እንደዚሁ የሀገር ቤቶች አባቶችም የሕዝቡን ሕማማትና ሞት ችላ ብለው አልፈው አባይ ይገደብ ይሉናል ምናለ በነካ አፋችው የሰብዓዊ መብትም ጥሰት ይገደብ፣ ዘረኝነትና ስደት ይገደብ ቢሉ። የሚገርመው ሉቃ 10፥30-35 እንደሚነገረን ካህን ያልሆነው ሳምራዊው ግለሰብ በነገድ ከማይገናኘው ለወደቀው ሰው አዝኖ መደረግ ያለበት እርዳታ ሁሉ አደረገለት። በዘርና በነገድ ከኛ ምንም ግንኙነት ሳይኖራችው ግን ኢትዮጵያ ውስጥ ስለሚደረገው የሰብዓዊ መብት ጥሰት “Amnesty International” ፣ “Human Rights Watch” እና የዓለም ዓቀፉ የጋዜጠኞች ማህበር የሚጮሁት የሳምራዊውን በጎ ምግባር ሲወጡ የአዲስ አበባው ልማታዊ ሲኖዶስ ደግሞ የፈሪሳውያኑን ስራ አንጸባርቀዋል። የአዲስ አባባው ሲኖዶስ የሃይማኖትን ስም ተላብሶ በምግባር ግን በአቶ (ምዕመን) ደረጃ ካሉት ከአርቲስት ታማኝ ና ከአቶ ኦባንግ ያነሰ የሞራል ስብዕና እያሳዩ ናቸው። ዲ/ን ዳንኤል “የማያለቅስ ልጅ” በሚለው ጽሁፉ ይህንን የአዲስ አበባውን ሲኖዶስ ስብሰባ አሰረ ሐዋርያትን (የሐዋርያት ፈለግ) የተከተለ ብሎ አድንቆታል ለማንኛውም የአንባቢ ህሊና የሐዋርያትን ፈለግ የተከተለው የትኛው ጉባኤ እንደሆነ ይፍረድ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአባይ ግድብ ዙሪያ (ግርማ ካሳ)

ጭራሽ የአዲስ አበባው ሲኖዶስን ጨምሮ ሌሎችም የሃይማኖት ተቋሟት በትግራይ ነጻ አውጪ መንግስት የሰለላ ድርጅት እዝ ስር ተዋቅረው መንጋውን የሚሰልሉና የሚያስጨንቁ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኝና ምንደኛ እረኞች እንደሆኑ ለኢሳት የደረሰውን የገዢው ፓርቲ የስለላው ድርጅትን ሪፖርት የድምጽ መረጃ የሰማ ይገነዘባል። የእግዜሃብሔር ቃል ለእነዚህ የሃይማኖት አባቶች እንዲህ ይላል፥

“እግዚአብሔር ከሕዝቡ ሽማግሌዎችና ከአለቆቻቸው ጋር ይፋረዳል፤የወይኑን ቦታ የጨረሳችሁ እናንተ ናችሁ፤ ከድሆች የበዘበዛችሁት በቤታችሁ አለ፤ሕዝቤንም ለምን ታደቅቁአቸዋላችሁ? የድሆችንስ ፊት ለምን ትፈጫላችሁ? ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር። ኢሳ3፥13

“ስለዚህ፥ እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እነሆ፥ በእረኞች ላይ ነኝ፥ በጎቼንም ከእጃቸው እፈልጋለሁ፥ በጎቼንም ከማሰማራት አስተዋቸዋለሁ። ከዚያም ወዲያ እረኞች ራሳቸውን አያሰማሩም፤ በጎቼንም ከአፋቸው አድናለሁ፥ መብልም አይሆኑላቸውም። ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና። እነሆ፥ እኔ ራሴ በጎቼን እሻለሁ እፈልግማለሁ።እረኛ በተበተኑት በጎች መካከል ባለ ጊዜ መንጋውን እንደሚፈልግ፥ እንዲሁ በጎቼን እፈልጋለሁ፤ በደመናና በጨለማ ቀን ከተበተኑት ስፍራ ሁሉ አድናቸዋለሁ።” ሕዝቅኤል 34፦9-12

በመጨረሻም ህጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚገኝበት ሁኔታ ደስ የሚያሰኝ ነው። በስደት ከሚገኙት የመምህራንና የጋዜጠኞች ማህበር እንደዚሁም ከተለያዩ በስደት ከሚገኙ የኢትዮጲያውያን ተቋሟት የግንኙነት መሰመር ፈጥረው የህዝባችንን ሰቆቃ የሚያጥርበት ጊዜ አብረው ቢመከሩ መልካም ይመስለኛል። የጠቅላይ ቤተክህነቱ አስተዳደሪ ከሰዎች ጋር በበለጠ እየተግባባ እንዲሰሩ ቢመከሩ እንደዚሁም የህዝብ ግንኙነት ክፍል አንደበተ ርቱዕና ነቃ ያሉ አባቶች ቢካተቱበትና የብጹዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ቦታ አሁንም ክፍት ስለሆነ በቦታው ተጠባባቂ/ምክትል ፓትርያርክ ቢመረጥ መልካም ነው።

የአባቶቻችን አምላክ የተመሰገነ ይሁን!
Taye_berhanu@ymail.com

3 Comments

  1. መልካም ብለሃል ታዬ ብርሃኑ እግዚአብሔር ይባርክህ
    በርግጥም ብርሃኑ ይታያል ሔሮድስም ይሞታል እመቤታችንም
    ክልጇ ጋር ትመለሳለች::ሙሴም ውሃውን ከድንጋዩ ይፈልቃልከዚያ ድንጋይም ጠጥተን
    እንረካለን::

    ጊዜው ቀርብዋል
    ቸር ይግጠመን

  2. it is very insightful and spiritually deep commentary. I have also learned from this article that how social justice is supported by the Bible. I would like to comment that various civic organizations in diaspora should work with the synod in exile hand in hand. I believe the Holy Synod in exile has the highest background to unite all opposition parties to free Ethiopian from the TPLF. There should a forum to all civic, religious and political organizations to mobilize the diaspora community. As far as the “devlepmental synod in Ethiopia” all the neutral church who believe that ths synod is in addis should stop and think over and over again. Brother Taye, yes indeed we are seeing the light!

  3. በእርግጥ ሰዎች አቁዋማቸውን ቢያስተካክሉ መልካም ነው::ቀናውንም

    መንገድ ማሳየት ይጠበቅብናል አሻፈረኝ ያለውን መተው ነው

    ጌድዮንም እኮ ያለው የፈራ ይመለስ ነው:: ካልሆነም ቀስ ብለው

    ይቀላቀሉናል:እኛ ያየነውን እንዲያዩ መጸለይ የኛ ድርሻ ነው::ማንንም ጠልተን እንዳንጸልይ አደራዬ ፅኑ ነው

    ግሩም በሆነ ትህትና በበረት የተወለደው ጌታ በሁላችንም ልብ ይወለድ

Comments are closed.

Share