የእስክንድር ውዱ የልደት ቀን ስጦታ!

ከጌታቸው ሽፈራው

በጠዋት ቂሊንጦ (ሁለት ቦታ ተከፍለን) እነ ኃብታሙን፣ የሽዋስን፣ አብርሃን፣ በፍቄን፣ አጥናፍንና ሌሎችንም ከጠየቅን በኋላ ለ30 ደቂቃ ብቻ እንዲጠየቁ ‹‹የተፈቀደላቸውን›› እነ እስክንድር፣ አንዱ ዓለምና መላኩ ተፈራ (የአንድነት አባል የነበሩ) ለመጠየቅ ወደ ቃቲ አቅንተን ነበር፡፡ በተለይ እስክንድር ወደዚች አለም የመጣባት ቀን ስለሆነች ከእሱ ጋር ትንሽም ጊዜም ቢሆም ማሳለፍ ፈልገን ነው ወደቃሊቲ ያቀናነው፡፡

እስክንድር የተወለደበትን ቀን አስታውሰን ወደ ቃሊቲ መሄዳችንን አመስግኖ ሌላ ቦታ ላይ በእስር ስለሚገኙት፣ ውጭ ስላለው ጉዳይ በአጠቃላይም በአገራዊ ጉዳይ ላይ አስተያየት ወደ መስጠት ገባ፡፡ ከቆይታ በኋላ በአንድ የአፍሪካ ጉዳይ ላይ መረጃ መስማት አለመስማቱን ጠየቅነው፡፡ ዋናው ደግሞ የቡርኪናፋሶ ጉዳይ ነው፡፡
‹‹ቡርኪናፋሶዎች አምባገነናቸውን አስወገዱ፡፡›› ስለው በጣም በደስታ ‹‹እውነት!›› አለኝ፡፡

አዎ! ‹‹ኮምፓወሬን በአንድ ቀን ተቃውሞ ከስልጣን አስወገዱት፡፡ ስለው አላስጨረሰኝም፡፡

‹‹ኮምፓዎሬን?!›› እስክንድር አላመነም!

ወደቃሊቲ ስናቀና እስክንድር ሁሌም የሚቀበለን በፈገግታ ነው፡፡ የሚሸኘንም እንዲሁ በፈገግታ! እኛን ለማበረታታት ሲጥር እሱ የታሰረ አይመስልም፡፡ እሱ ሁሌም ደስተኛ ነው፡፡ የዛሬው ደስታው ግን በእጅጉ ይለያል፡፡

‹‹ኮምፓዎሬን?!››

‹‹ብራቮ! ብራቮ! ብራቮ! ብራቮ!….›› ሁለቱንም እጆቹን ጨብጦ ወደ ላይ ዘለለ፡፡ የእስክንድር ነጋ ደስታ እኔንም፣ ከጎኑ ቆሞ የምንለው የሚያዳምጠውን ፖሊስ እስክንድርን በአድናቆት ከማየት ውጭ ምንም ማለት አልቻልንም፡፡

እስክንድርን በልደቱ ቀን ለትንሽ ጊዜም ቢሆን አብረን ከመቆየት ውጭ ምንም አላደረግንለትም፡፡ እሱ ግን ትልቅ ስጦታ ሰጥታችሁኛል አለ፡፡ የኮምፓዎሬን ውድቀት ስላሰማነው፡፡

‹‹በእውነት ይህ ለእኔ ውድ የልደት ቀን ስጦታዬ ነው፡፡ በጣም ትልቁ የልደት ቀን ስጦታዬ!›› እስክንድር ያች አጭር ጊዜ አለቀች ተብሎ ሲመለስም ሁላችንን ያመሰገነው ስላበረከትንለት ትልቁ የልደት ቀን ስጦታው ነው፡፡ ስለ ቡርኪናፋሶው አምባገነን ውድቀት፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:   የኢትዮጲያ ፖለቲካ ሓይሎች አስላለፍ ና ውጤቱ - ሙሉቀን ገበየው

1 Comment

Comments are closed.

Share