June 26, 2011
23 mins read

ቅድስት:- በሚኒሶታ ብቸኛዋ የታክሲ ሾፌር

Dr yakob

ሕይወት ሽንኩርት ናት:: ስትላጥ ብታስለቅስም ስትበስል ግን ትጣፍጣለች:: ከሕይወት ስንክሳሮች መካከል ደግሞ አንዱ ስደት ነው:: የሰው ልጅ የተሻለ ኑሮን ወይንም በአስቸጋሪ ሁኔታ ሲሰደድ እንደሽንኩርቷ በችግር ሲላጥ አልቅሶ; የተፈተነበት ውጤት ሲያልፍ ደስተኛ ይሆናል:: የዛሬዋ እንግዳችን በሚኒሶታ ብቸኛዋ የታክሲ ሹፌር የሆነችው ኢትዮጵያዊቷ ቅድስትም በሕይወት ስንክሳር ብዙ ተፈትና ዛሬ እዚህ ደርሳለች:: የዚህችን ሴት ታሪክ ሰማንና የጋዜጣችን እንግዳ ለማድረግ ወደ ስልኳ በተደጋጋሚ ደወልን:: ከስልኳ የምናገኘው you have reached the voicemail of…. የሚለውን አናዳጅ ምላሽ ነበር:: ሆኖም ግን በነዚህ ቃላት መካከል “ኪኪ” የሚል ድምጽ ስናገኝ ስልኳ የእርሷ መሆኑን አረጋግጠን ድወላችንን ቀጠልን:: ምላሽ ስናጣም የድምጽ መልዕክት አስቀመጥን; ቅድስት ወይም ኪኪ ወዲያውኑ ስልካችንን መለሰች:: ከዛም የሚከተለውን እዛው የምትሠራበት ፖስት ሮድ ተቀጣጥረን የታክሲዋን መስኮት ከፍተን አወራን::
ዘ-ሐበሻ:- ተጀመረ!
ቅድስት:- ምኑ?
ዘ-ሐበሻ:- ቃለ ምልልሱ!
ቅድስት:- (ሳቅ…)
ዘ-ሐበሻ:- ምነው? አልተዘጋጀሽበትም እንዴ?
ቅድስት:- ኸረ እንደውም!
ዘ-ሐበሻ:- የፈራሽ ትመስያለሽ?…
ቅድስት:- እንዴ እኔ ለኢንተርቪው አዲስ አይደለሁም እኮ!… ድሮ እኔም ራሴው ኢንተርቪው አደርግ ነበር::
ዘ-ሐበሻ:- ኦው! ጥሩ:: ታዲያ ራስሽም ቃለ-ምልልስ ታደርጊ ከነበረ; እንዲሁም ብዙ ሰው ቃለ-ምልልስ ሲደረግለት አይተሻልና ጋዜጠኞች ብዙ ጊዜ አስቀድመው የሚጠይቁት ነገር ስለምንድን ነው?
ቅድስት:- ስለማንነት!…. ከራሳቸው ላይፍ ስታይል.. ከስማቸው ያሉበትን የመጡበትን….
ዘ-ሐበሻ:- ታዲያ እኛም ከእርሱ እንጀምር?…
ቅድስት:- እንደፈለክ!
ዘ-ሐበሻ:- ይሄንን በቅድሚያ ብጠየቅ የምትይው ነገር ካለ?
ቅድስት:- ይሄን ብጠየቅ?
ዘ-ሐበሻ:- አዎ!
ቅድስት:- (ሳቅ!..) የሥራ ሁኔታ እንዴት ነው? አንቺ ሴት ሆነሽ እንዴት እዚህ ቦታ እንዴት መጣሽ? ብቻሽን ነሽና እንዴት ልትመጪ ቻልሽ ምናምን…. ነው መስለኝ ጥያቄው የሚመስለኝ… (ሳቅ) እና ተደሰቺበታለሽ ወይ በሥራው? ይመስለኛል…
ዘ-ሐበሻ:- እሺ ቅድስት ማናት ብለን እንጀምር!…
ቅድስት:- ቅድስት ታዬ::
ዘ-ሐበሻ:- ይህን ጋዜጣ ለሚያነቡ ሰዎች ራስሽን አስተዋውቂ ብትባይ እንዴት ራስሽን ትገልጪዋለሽ?
ቅድስት:- የመጣሁት ከኢትዮጵያ ነው:: ተወልጄ ያደግኩትም ጅማ ውስጥ ነው:: ኢትዮጵያ ውስጥ ከተማርኩና ከሰራሁ በሗላ ወደ አውሮፓ ሄድኩኝ:: ከአውሮፓ ወደ እዚህ መጣሁ:: ወደዚህ ሙቭ (ሀገር የቀየርኩት) ያደረግኩት በ1998 ነው::
ዘ-ሐበሻ:- አውሮፓ የት ነበርሽ?
ቅድስት:- ስዊድን ነበርኩ!…
ዘ-ሐበሻ:- እንዴት ነበር ወደ አሜሪካ የመጣሽው?
ቅድስት:- መጀመሪያ ያው በደርግ ጊዜ ነው ከሀገር የወጣሁት:: ስዊድን ሀገር ሄጄ ከዛ በሗላ 10 years ቆየሁ:: እዛ እያለሁ; እኔ እንኳን አልሞላሁም ጓደኞቼ ዲቪ ሞልተው ላኩልኝና መልሱ ሲመጣ በእኔ አድራሻ መጣ::
ዘ-ሐበሻ:- ስዊድን ሆነሽ ማለት ነው?
ቅድስት:- አዎ!
ዘ-ሐበሻ:- ኢትዮጵያ ውስጥ ምንድን ነበር ሞያሽ? ምንድን ነበር የምትሰሪው? እዛም እንደዚሁ ታክሲ ትነጂ ነበር?
ቅድስት:- ሙያ የሚባል ነገር ያው just ሀይስኩል ከጨረስኩ በሗላ ባንክ ትንሽ ሰርቻለሁ::
ዘ-ሐበሻ:- ቅድም የጋዜጠኝነት ሙያው አለኝ; በራዲዮ ሰርቼ ነበር ስትይኝ ነበር?
ቅድስት:- ጋዜጠኝነት እንኳን ሳይሆን በራዲዮ ነው:: የራዲዮ ፕሮግራም እናዘጋጅ ነበር – በቤተ ክርስቲያን ውስጥ:: በኢቫንጀሊካል ቤተክርስቲያን ፕሮግራም እያዘጋጀን ስዊድን ሀገር ለ5 አመታት ሰርቼበታለው::
ዘ-ሐበሻ:- አሜሪካ ከመጣሽ በሗላ የታክሲ ሹፌርነቱ ሥራ የመጀመሪያ ሥራሽ ነው?
ቅድስት:- አይደለም:: መጀመሪያ ኤርፖርት ውስጥ እሠራ ነበር:: ለ2 ወራት በኤርፖርት ሥራዬ ሴክዩሪቲ ሆኜ ነበር የሠራሁት:: ከዛ በሗላ ደግሞ የአፍሪካ ሕጻናት እና ሴቶች እንክብካቤ ቡድን ውስጥ ሰርቻለሁ:: በዚህ መሥሪያ ቤት ውስጥ በሰዎች “አብዩዝ” የተደረጉ ልጆችን እና ሴቶችን መርዳት ነበር ሥራችን:: ከ6 እስከ 8 ወር ለሚሆን ጊዜ ሰርቻለሁ::
ዘ-ሐበሻ:- በሀገር ቤትም; በስዊድን ቆይታሽም የታክሲ ሾፌር ካልነበርሽ እንዴት አሜሪካ መጥተሽ ይህንን የሥራ ክፍል ልትመርጪው ቻልሽ?
ቅድስት:- ባንክ ሰርቼ ነበር:: በዌልስ ፋርጎ (wells Fargo) ባንክ ውስጥ እየሰራሁ አብሬያቸው ቸርች የምሄዳቸው ልጆች እነርሱ ታክሲ ይነዳሉ:: እና ብዙ ጊዜ አንዳንድ ቦታ ለመሄድ አንድ ነገር ለማድረግ; በሕብረት የሆነ ነገር ለማድረግ እነርሱ ፍሪ (ጊዜ አላቸው) ናቸው:: እኔ ማስፈቀድ ምናምን ስላለብኝ አይመቸኝም:: ከዛም ለምን እኔም እንደነርሱ አልሰራም ብዬ አስብ ነበር:: ይህ ሀሳብ በአእምሮዬ ውስጥ እንዳለ አንድ ቀን መንገድ ላይ ስሄድ አንዲት ሶማሌ የባሏን ታክሲ ይዛ ነው መሰለኝ ስትነዳ አየሗትና እንዴት የሱማሌ ሴት ታክሲ የነዳች እኔን ያቅተኛል ብዬ ካልጀመርኩኝ ሞቼ እገኛለሁ አልኩ::
ዘ-ሐበሻ:- ከዛስ?
ቅድስት:- ከዛማ አብረውኝ ቸርች የሚሄዱትን የታክሲ ሹፌሮች አነጋግሬያቸው ታክሲ ሥራ ለመጀመር እንዴት እንደማደርግ ፕሮሰሱን ነገሩኝ እና ጀመርኩት::
ዘ-ሐበሻ:- አንዴ ኢንተርቪውን ላቋርጠው… ጉንፋን ይዞኛልና አፍንጫዬን ማጸዳዳት ይኖርብኛል::
ቅድስት:- ሶፍት ልስጥህ?
ዘ-ሐበሻ:- አይ ተይው!… ግን ጉንፋኔን እንዳላጋብብሽ?
ቅድስት:- I know!… (ሳቅ…)
ዘ-ሐበሻ:- (ከጥቂት ቆይታ በሗላ) እሺ አሁን መቀጠል እንችላለን::… እና ያቺ ሱማሌ ነች መነሻ የሆነችሽ ማለት ነዋ!
ቅድስት:- አዎ ሱማሌዋ ናት መጀመሪያ አእምሮዬ ውስጥ የነበረውን ሀሳብ በደንብ አጠናክሬ እዚህ ሥራ ውስጥ ያደረገችኝ ማለት ይቻላል:: በጣም ሞራል ሰጠችኝ:: የሶማሌ ሴት የነዳች እንዴት ያቅተኛል ብዬ ገባሁበት::
ዘ-ሐበሻ:- የታክሲ ሾፌር ከሆንሽ በሗላ ሥራውን እንዴት አገኘሽው?
ቅድስት:- በጣም easy (ቀላል) ሥራ ሆኖ ነው ያገኘሁት:: ስለእውነት ለመናገርም የሚከብድ ሥራ አይደለም:: ደግሞ ከእኔ በፊትም የሚገርምህ ሁለት ኢትዮጵያውያን ሴት የታክሲ ሾፌሮች ነበሩ:: ሆኖም ጥቂት ጊዜ ሰርተው ጥለው ወጡ ወዲያው::
ዘ-ሐበሻ:- አሁን ግን እዚህ የኤርፖርት ታክሲ ላይ አንቺ ብቻ ነሽ ሴት?
ቅድስት:- ያው ከሀበሻ እኔ ብቻ ነኝ:: ከነጮች ግን አንድ ሴት አለች:: almost 5 Years ይሆናል ብቸኛዋ ሴት የሀበሻ የታክሲ ሾፌር እኔ ነኝ ያለሁት::
ዘ-ሐበሻ:- ከብዙ የታክሲ ሾፌሮች እንደምሰማው ሥራውን የምትሰሪው ትንሽ ሀላፊነት ወስደሽ ነው:: ወንጀለኛ ሊያጋጥም ይችላል:: ሰካራምና በአደንዛዥ እጽ የደነዘዘ ሰው መጫን አለ:: አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ሰው ጭነሽ መንገድ የመጥፋት ነገር አለ:: እና አንቺ በዚህ ሥራ ውስጥ ያጋጠመሽ ነገር ምንድን ነው?
ቅድስት:- ጥሩ ጥያቄ ነው:: ወንጀለኛ እንኳን አጋጥሞኝ አያውቅም:: በጣም የሚያጋጥመኝ ያው መንገድ መጥፋት ነው:: በታክሲ ስራ ውስጥ መንገድ መጥፋት So normal ነው ይሄ:: እ.. እ… (እንደማሰብ አለችና) አንድ ጊዜ እንደውም ምን አጋጠመኝ መስለህ? አንዱን ደንበኛዬን ሆቴል እየወሰድኩት እያለ ሰውዬውም እኔም ሆቴሉ ያለበትን ቦታ አናውቀውም:: እየነዳሁ ሆቴሉ ጋር ስልክ ደውለን አድራሻውን ጠየቅኳቸው:: በየት በየት እንደምሄድ የነገሩኝ በትክክል አልገባኝም.. በቃ ሰውዬውን ይዤው ጠፋሁ:: ይገርምሀል ሰውዬው ምንም ነገር አይናገርም:: ዝም ብሎ ብቻ ነገሩን ይከታተላል:: ከተማውን ዞሬ ዞሬ እንደገና ሆቴሉ ጋር ስደውል የሚነግሩኝ መንገድ አይገባኝም:: ቢቸግረኝ ስልኩን ለተሳፋሪው ሰጠሁት:: ከዛ በሗላ በይ ከዚህ በኩል ተመለሺ ብሎኝ በተሳፋሪዬ እየተመራሁ ሆቴሉ አደረሰኩት:: ካሁን ካሁን ጮኸብኝ ብዬ ስፈራ እሱ እንደውም ቲፕ አድርጎ ሲከፍለኝ እኔ ‘ይሄን ያህል ገንዘብ አይመጣም; እንደውም ጊዜህን ሁሉ ስላጠፋሁብህ አላስከፍልህም’ ስለው እርሱ ጥሩ ሰው ስለነበር ከነቲፑ ሰጥቶኛል:: ሆኖም ግን ወንጀል ምናምንም አጋጥሞኝ አያውቅም::
ዘ-ሐበሻ:- አንቺ የታክሲ ስራ አስከፊ ጎን የምትይው ምንድን ነው?
ቅድስት:- መቼም በእኔ አስከፊ አድርጌ የምወስደው መንገድ መጥፋትን ነው:: ሰው ይዞ መጥፋት በጣም በጣም የሚያስፈራ ነው:: ሌላው ደግሞ ማታ መሥራት ትንሽ አደገኛ ሊሆን ይችላል:: አንዳንድ ጊዜ የሰከረ ሰው ሊያጋጥም ይችላል:: ማታ መሥራት ጥሩ አይደለም:: በተለይ ወደ ኖርዝ ሚኒያፖሊስ ማታ ከሆነ ሰው ይዞ መሄድ ብዙም ጥሩ አይደለም::
ዘ-ሐበሻ:- አንቺ ማታ ማታ አትነጂም ማለት ነው?
ቅድስት:- ማታ በጣም አላመሽም::
ዘ-ሐበሻ:- በሴትነትሽ ተሳፋሪ ሆኖ የሚተናኮልሽ የለም?
ቅድስት:- ማለት የኤርፖርት ታክሲ ስለሆነ የምሰራው ብዙም እንደዚህ ያለው ነገር አያጋጥምም:: ብዙ ጊዜ ከኤርፖርት ራሳቸውን ችለው; የኤርፖርት ትኬት ገዝተው የሚሄዱ ሰዎች ወደ ቤታቸው ወይም ወደ ሆቴል አንዳንዴም ወደ ሥራቸው ስለሆነ ብዙም እንደዚህ አይነት ሰዎች የሉም:: የሲቲ ታክሲ ስለማልሰራ ብዙም አልጨነቅም:: የሲቲ ታክሲ ግን ብዙ ጊዜ እንደዚህ ያለው ነገር ሊከሰት ይችላል::
ዘ-ሐበሻ:- በሚኒሶታ በሲቲ ታክሲ ውስጥ ሴት ሹፌር አለች እንዴ?
ቅድስት:- No! የለችም::
ዘ-ሐበሻ:- እዚህ ሚኒያፖሊስ-ሴንትፖል ኤርፖርት ታክሲ ሥራ ላይ የተሰማሩ ስንት ኢትዮጵያውያን አሉ?
ቅድስት:- I think እስከ 150 የምንሆን ይመስለኛል::
ዘ-ሐበሻ:- እንግዲህ ከነዚህ ሁሉ መካከል አንዷ ብቸኛ ሴት አንቺ ነሽና ውሎሽ ከወንዶች ጋር ነው ማለት ይቻላል::
ቅድስት:- በሚገባ!..
ዘ-ሐበሻ:- ታዲያ ከወንዶች ጋር እንደመዋልሽ ወንዶችን ምን ታዘብሻቸው?
ቅድስት:- (ረዥም ሳቅ…) እኔ ከሕጻንነቴ ጀምሮ ወንዶችን ናቸው ጓደኞቼ:: ከሴቶች በላይ ከወንዶች ጋር ነው የምውለው:: አንዳንድ ጊዜ ሴት መሆኔንም የሚረሱበት አጋጣሚ አለ:: እነርሱ ብዙ ነገር ነው የሚያወሩት:: (ሳቅ…) በጣም ደስ ብሎኝ ነው ከወንዶች ጋር የምውለው:: ምንም ያየሁባቸው የታዘብኳቸው ነገር የለም:: ደግሞ እንደየአካባቢያችን እና እንደምንግባባቸው ሰዎች ነው የምንቆመው:: አብረውኝ የሚቆሙት (ተራ እስኪደርስ ለመጠበቅ ማለቷ ነው) ያሉት “ኩል” የሆኑ ናቸው::
ዘ-ሐበሻ:- ብዙ ጊዜ ወንዶች ስለምንድን ነው የሚያወሩት?
ቅድስት:- (ሳቅ..) እሱ ጠፍቶህ ነው እኔን የምታደርቀኝ? (ሳቅ…) ብዙ ጊዜ ሴት ያወራሉ:: ስለማህበራዊ ጉዳይ ያወራሉ:: ግን አብዛኛውን ጊዜ ስለሀገር ጉዳይ በማውራት ነው የሚያሳልፉት:: ስለሀይማኖት ጉዳይም ያወራሉ:: ግን ብዙ ትኩረት የሚሰጡት በሀገር ፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ነው::
ዘ-ሐበሻ:- አላማሽ ምንድን ነው?
ቅድስት:- አላማዬ መማር ነው:: ከዚህ ቀደምም ተምሬ አቋርጬው ነው:: አሁን እሱን ከተማርኩ በሗላ ወደ ሀገሬ መግባትና ከሕጻናት ጋር የተያያዙ ሥራዎችን መስራት እፈልጋለሁ:: ሕጻናትን በጣም ስለምወድ እነርሱን ማስተማር ደስ ይለኛል:: የወሰድኩትም ትምህርት ከዚሁ ጋር የተያያዘ ስለሆነ በዚህ ዙሪያ መሥራት እፈልጋለሁ::
ዘ-ሐበሻ:- ብዙ ኢትዮጵያውያን ሀገሬ መግባት እፈልጋለሁ ይላሉ ልክ እንዳንቺ; ግን ሲገቡ አይታዩም:: ለምን ይመስልሻል?
ቅድስት:- መቼም ሁሉም ኢትዮጵያዊ እዚህ ይኑር እንጂ ልቡ ያለው ሀገር ቤት ነው:: ስለሀገሩ የማያስብና የማይናፍቅ የለም:: ያለመሙላት ጉዳይ ነው እንጂ ሁሉም ቢገባ ደስ ይለዋል:: እኔም ከወጣሁ ቆይቻለው:: ሰውን ወደ ሀገሩ እንዳይሄድ የሚያደርገው የገንዘብ ጉዳይ ነው:: እዛ ሄዶ ከዚህ ዝቅ ብሎ መኖር ስለማይፈልግና ኢትዮጵያ ሄጄ ከዚህ ያነሰ ልኖር? እያለ ስለሚፈራ; እሄዳለሁ እንዳለ ሳይሳካለት እዚሁ ይቀራል:: እኔም የምፎክረው ገንዘብ ቢኖረኝ ዛሬ እሄዳለሁ እያልኩ ነው::
ዘ-ሐበሻ:- ወደ ሥራሽ እንመለስና; ከመኪና ጋር አብሮ መዋል ብዙ አደጋ አለው:: ችግርም ያጋጥማል:: ለመሆኑ መንገድ ላይ እየሄድሽ ጎማ ቢፈነዳብሽ ራስሽ ነሽ የምትቀይሪው?
ቅድስት:-(ሳቅ..) ኸረ እኔ አልችልም:: ጎማ ቢፈነዳብኝም ቢበላሽብኝም መኪናዬን አስገፍቼም (ቶው አስደርጌ) ይዤ ወደ መካኒክ ነው የምሮጠው::
ዘ-ሐበሻ:- የሚኒሶታ አየር ትንሽ ይከብዳል:: በተለይ በክረምቱ ጊዜ ያለው በረዶ ጠንከር ያለ ነው:: አንቺ እንዴት ነው ይህንን አስቸጋሪ የክረምት ወራት ካለ አደጋ በረዶ ላይ በመንዳትና; በረዶ ላይ ቆሞ ወረፋ በመጠበቅ የምትሰሪው?
ቅድስት:- ይገርምሀል እኔ የሚኒሶታ ክረምት አይከብደኝም:: እንደውም ተስማምቶኝ ነው የምሰራው:: ለምን መስለህ ስዊድን ሀገር ከዚህ የባሰ በረዶ (ስኖው) አለ:: እናም ተስማምቶኝ ነው የምሰራው:: በደንብ ከለበስክ ከሚኒሶታ በጋ ክረምቱን እመርጣለሁ:: መንዳቱም ቢሆን ተጠንቅቀህ ከነዳህ መንሸራተትም አደጋም የለም:: ለታክሲ ስራ ገበያ የሚኖረው የክረምቱ ጊዜ እንደሆነም አትርሳ:: (ሳቅ) ስለዚህ ክረምቱን እወደዋለሁ::
ዘ-ሐበሻ:- ኢትዮጵያውያን ወንዶች በቤት ስራ ደካሞች ናችሁ እንባላለንና አንቺም ከእነርሱ ጋር እንደመዋልሽ ሙያውም ጠፍቶብሽ ይሆን?
ቅድስት:- (ሳቅ…) አልክድም:: እንደ ሴት መንጎዳጎድ አይሆንልኝም:: እንደውም እዚህ ያሉት በጣም ይፈታተኑኛል… (ሳቅ) ሙያሽን እንቅመሰው እስኪ አገልግል ፈትፍተሽ አምጪ ይሉኛል; ግን አይሆንልኝም:: እኔም ሴትነቱ ጠፍቶኛል መሰለኝ አላበላም ብዬ ቁጭ ብያለሁ:: አልሞከርኩትም እንጂ ሳይጠፋኝ አይቀርም:: ለራሴም ቀባ ቀባ አድርጌ ነው የምበላው: እንደወንዶቹ ቀለል ያሉ የፈረንጅ ምግብ; ሩዝ ወይም ፓስታ እያበሰልኩ ነው የምመገበው:: ወጣ ወጡን ነገር ሳልረሳው አልቀርም::
ዘ-ሐበሻ:- አግብተሻል?
ቅድስት:- አላገባሁም::
ዘ-ሐበሻ:- ለምን አላገባሽም ብዬ አልጠይቅሽም:: ግን ብዙ ጊዜ ከወንዶች ጋር ስለምትውይ ተጽእኖ አሳድሮብሽ ይሆን?
ቅድስት:- ኖ! ላሳደረብኝም:: Just የራሴ የሆነ ፐርሰናል ጉዳይ ያለማግባት ጉዳይ ነው::
ዘ-ሐበሻ:- እሺ እንተወው:: የሕይ ወት ፍልስፍናሽ ምንድን ነው?
ቅድስት:- እኔ በእግዚአብሄር የማምን ሰው ነኝ:: የቤተክርስቲያን ሰው ነኝ:: ያደግኩትም ከእግዚአብሄር ቃል ጋር ነው:: በሕይወቴ የሚያጋጥሙኝ ነገሮችና የሚፈጠሩት ሁኔታዎች ሁሉ በእግዚአብሄር ፈቃድ ብዬ ነው የማምነው:: ከዛ በተረፈ እኔ ማድረግ ያለብኝን ነገር ሁሉ አደርጋለሁ ቀጥሎ ያለው በእግዚአብሔር የሚሆን ነው::
ዘ-ሐበሻ:- በመጨረሻም ምን ትያለሽ?
ቅድስት:- ማለት የምፈልገው? ብዙ ጊዜ ለሀበሾች ታክሲ ነው የምነዳው ስል አንዳንዱ ይደነግጣል; አንዳንዱ ይገረማል; አንዳንዱ አብረታቶኝ ያልፋል:: አብዛኛው ሴት ሆኜ የታክሲ ሥራ ላይ ሲያየኝ ‘ጉድ’ ይላል:: እኔ የምለው ግን በተለይ ሴቶች የታክሲ ሥራ አያስፈራም; ቀላል ነው; ኑና ሞክሩት ነው የምለው:: ብዙ ጊዜ የእኛ ሴቶች ፈሪዎች ነን:: መንገድ እንፈራለን… አይናፋር ነን… ግን ኑ የታክሲ ሥራ ቀላልና የሰነፍ ሥራ ነው የምለው:: ሴቶች መጥተው ቢሞክሩት ደስ ይለኛል::
ዘ-ሐበሻ:- እናመሰግናለን ቅድስት::
ቅድስት:- እኔም አመሰግናለሁ:: ®

Previous Story

ይህች ኮሜዲያን እንደ ርዕዮት ዓለሙ ወይም እንደቴዲ አፍሮ?

Next Story

የእግር ኳስ አጥቂ አበበ ቢቂላ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop