ዱሩ ቤቴ !! ( አሥራደው ከካናዳ )

እገባለሁ ጫካ – እገባለሁ ዱር፤
የበደልን ገፈት – ስጋት ከምኖር፤
አትገባም ወይ ጫካ – አትገባም ወይ ዱር፤
ተቀጥላ ዜጋ – ሆነህ ከመኖር ::

ትናንትም ተበዳይ – ዛሬም ጦም አዳሪ፤
የበይ ተመልካች – የጅቦች ገባሪ፤

የሃብቱ ተመጽዋች – ያገሩ ባይተዋር፤
የመብት ተነፋጊ – የባንዳዎች ገባር
ሁለተኛ ዜጋ – ሆኜ ከመኖር፤
እገባለሁ ጫካ – እገባለሁ ዱር ::

ባዕድ አምላኪዎች – ታሪክ ከላሾችን፤
ዘረኛ ጎሠኛ – አንድነት አፍራሽን፤
የ ’ድገት እንቅፋቶች – የኋሊት ጎታችን፤

አትፋለምም ወይ – አትገባም ወይ ከዱር፤
አንገት እየደፋህ – ዘወትር ከመኖር ::

አትሰማም ወይ ጥሪ – አትሰማም ወይ ጩኸት፤
ደሙ ሲተነፍግ – ሲንቀጫቀጭ አጥንት
በደም ተለውሶ – ባጥንት ያጠሩትን፤
አሳልፈህ ስትሰጥ – የጦቢያ መሬትን ::

ያ’ገሬ ቁልቁለት – ያ’ገሬ ተራራ፤
ጥንትም ያልተበገርክ – ለጠላት ወረራ፤

ለወገንህ ኩራት – መመኪያ ስለሆንክ፤
አብረኸኝ ተሰለፍ – ጠላት ለማንበርከክ ::

ዱሩ ቤቴ ብዬ – በቃ ወጥቻለሁ፤
በደልን በዓርነት – ፍቄ እመለሳለሁ ::

ወንዙ ጥም ቆራጬ – ደኑ ብርድልብሴ፤
አሸዋው ምንጣፌ – ድንጋዩ ትራሴ፤

ቅጠል ፍራፍሬ – ስራስር በልቼ፤
ሰንደቅ አበቅላለሁ – ነፃነት ዘርቼ ::

የዱር አራዊቶች – ሳትቀሩ ተነሱ፤
እምዬ ኢትዮጵያ ! – እያላችሁ አግሱ፤

ነብርና አንበሳ – አብሩ ባንድላይ፤
ከጣሊያን የባሰ – መቷል አገር ገዳይ ::

ጀግናው ጫካ ገባ – እሰይ በይ ምድሪቱ፤
እጅግ ቢበዛበት – የበደል ገፈቱ

ጉብል ከዱር ገባች – ዕልል በይ መሬት፤
ትግልን አርግዛ – ለመውለድ ነፃነት፤
በ’ኩልነት ጸንቶ – እንዲሰምር አንድነት ::

ተጨማሪ ያንብቡ:  አንተ ምንጭ ሆይ ፍለቅ!

 

ጎበዝ ! « ጅቡ ከሚበላህ ጅቡን በልተህ ተቀደስ !! »

 

ለሥር ነቀል ለውጥ፤ በአንድነት በመነሳት፤ ነፃ ሕዝብ እንሁን !!

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!

ነፃነት፤ እኩልነትና ወንድማማችነት ይለምልም !!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይባርክ !!

የካቲት 27 ቀን 2016 ዓ.ም ( 06/03/2024 ) እኤአ

ለአድዋ ድል በዓል መታሰቢያ ተዘጋጅቶ ሳይላክ የዘገየ ::

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share