በአማራ ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን መጠነ ሰፊ ግፍ አስመልክቶ ከዓለም አቀፍ አማራ ህብረት የተሰጠ መግለጫ

ሚያዝያ 9 ቀን 2015 ዓ.ም./April 17, 2023

 

ዓለም አቀፍ አማራ ህብረት በአብይ አህመድ፣ ሺመልስ አብዲሳና አዳነች አቤቤ የሚመራው የኦሮሞ ብልፅግና ፓርቲ በአማራ ህዝብ ላይ ያወጀውን ፋሺስታዊ ወረራ፣ ግድያ፣ አፈና፣ መጠነ ሰፊ ቤቶች ማፍረስና እና ማፈናቀል እንዲሁም የአማራ ልዩ ኃይልን ትጥቅ ለማስፈታትና ለማፍረስ ያሳለፈውን ዕብሪት የተጠናወተው አገር አፍራሺ የሆነ የሴራ እርምጃ አጥብቆ ያወግዛል።

የአማራ ህዝብ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከሚደርስበት የማያባራ ግፍ እንዲሁም ከጦርነት እንኳን ገና ሳያገግም በኦሮሞ ብልፅግና የሚዘወረው የብልፅግና ፓርቲ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የአማራን ህዝብ ደህንነት እና ህልውና ሲያስጠብቅ የቆየውን ኃይል ለማፍረስ እና ትጥቅ ለማስፈታት መወሰኑ እና ይህንንም ለማስፈጸም በግልጽ ጦርነት ከህዝቡ ጋር መግባቱ ከአንድ መንግሥት ነኝ ከሚል አካል የሚጠበቅ አይደለም። የአማራ ልዩ ኃይል የተቋቋመው በክልሉ ምክር ቤት ሲሆን በጀት የሚያገኘውም ከክልሉ ነው። የተቋቋመበት ዋነኛ ምክንያትም የውስጥና የውጭ ታጣቂ ኃይሎች በክልሉ ህዝብ ላይ እያደረሱበት የነበረውን የፀጥታ ችግር በመደበኛ ፓሊስ ሊወጣው ባለመቻሉ መሆኑ ይታወቃል። ይህ የአማራ ልዩ ኃይል እስካሁን ድረስ በአጣየ እና ሸዋ ሮቢት ከኦነግ ጦር ጋር በመዋጋት፣ በጎንደር ከቅማንት ታጣቂወች ጋር በመፋለም እንዲሁም በቤንሻንጉል ጉምዝ ከክልል መንግሥት በተደረገለት ጥሪ መሰረት ወደ ክልሉ በመግባት የጉምዝና የኦነግ ታጣቂዎች እያደረሱ ከነበረው ጭፍጨፋ ህዝብን ከከፋ እልቂት ታድጓል። ከዚህም አልፎ ህወሓት በከፈተው ጦርነት ከአገር መከላከያ፣ ከፋኖ ሚሊሻ እና የአፋር ልዩ ኃይል ጋር በመሆን አኩሪ የውጊያ ድሎችን በማስመዝገብ አገርን ከውርደት መንግሥትን ከመፍረስ የታደገ የሃገር ባለዉለታ ነው። ነገር ግን ለዚህ ላደረገው አስተዋጽዖ እና ለከፈለው መስዋእትነት ምላሹ ትጥቅህን ፍታ የሚል መሆኑ ከማስገረምም አልፎ አደገኛ አካሄድ መሆኑን ተገንዝበናል። ለመሆኑ የኦሮሞ ብልፅግና ለምን በአሁኑ ወቅት የአማራ ልዩ ኃይል ትጥቅ እንዲፈታ ወሰነ? በእኛ እምነት በአምስት መሰረታዊ ምክንያቶች ነው ብለን እናምናለን፦

 

  1. በፕሪቶሪያ ድብቅ ስምምነት መሰረት አብይ አህመድ ወልቃይትና ራያን ለትግራይ ለማስረከብ ስለተስማማ እንዲሁም ለአሜሪካኖች ቃል ስለገባ ይህንን ለማስፈፀም ልዩ ኃይሉ እንቅፋት ይሆናል ብሎ በማሰብ ለማፈራረስ ማሰቡ፣ ለዚህ ማረጋገጫ የሚሆነወ የአማራ ልዩ ኃይል ከመከላከያ ጋር በተፈጠረው ግጭት ቦታዎችን መልቀቁን ተከትሎ የህወሓት ጦር ወደ ጠለምትና ራያ እየገባ መሆኑ እየተዘገበ መሆኑ ነው።

 

  1. ፋኖን ትጥቅ ለማስፈታት ያደረገው ሙከራ ስላልተሳካ በቅድሚያ ልዩ ኃይሉን ትጥቅ አስፈትቶ በቀጣይ የፋኖንን፣ የሚሊሻውን እና የህዝቡን የግል ትጥቅ በቀላሉ ለማስፈታት እንዲችል በማቀድ፣

 

  1. በወለጋ በአማራው ላይ የኦነግ ጦር ከኦሮሚያ ልዩ ኃይል ጋር በመጣመር እያካሄዱ ያሉትን የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ፣ በአዲስ አበባ ዙሪያ መጠነ ሰፊ የቤት ማፍረስና አማራውን የማፈናቀል ዘመቻ እንዲሁም አማራወች ወደ አዲስ አበባ አትገቡም የሚለው ክልከላና እንግልት አማራውን እንዲያመር ስላደረገው ለትግል መነሳቱ የማይቀር መሆኑን በመረዳት መሳሪያ አልባ ለማድረግ፣
ተጨማሪ ያንብቡ:  ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

 

  1. የአማራ ብልፅግና አንዳንድ የበላይ አመራሮች በተለይም የዞንና የወረዳ አመራሮች የህዝቡን ብሶት ማንፀባረቅ በመጀመራቸው ክልሉ በራሱ የመወሰን አቅም ሊያመጣ ስለሚችል ለመቅጨትና የስልጣናቸው ተገዳዳሪ ኃይል ሆኖ እንዳይወጣ ለማድረግ፣

 

  1. የኦሮሞ ብልፅግና የኦነግን የዘመናት ጥያቄ በማንገብ ኢትዮጵያን በማፍረስ አዲስ አገር ለመፍጠር ወይም የኦሮሞን የበላይነት የምትቀበልና ኦሮማዊት የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ካለው እቅድ አንፃር ግዛት ማስፋቱ ዋናው አጀንዳ በመሆኑ አዲስ አበባን ከመሰልቀጥ፣ ቤንሻንጉልን ጋምቤላን ከመዋጥ ብሎም በሶማሊያ፣ በሲዳማ በደቡብ ክልል ዙሪያ ያለውን የመስፋፋት እቅዱን ተግባራዊ ከማድረግ የአማራ ልዩ ኃይልና ፋኖ ይገዳደረኛል ብሎ ከማሰብ የተነሳ ነው።

 

በመንግሥት ባለስልጣናት በኩል የሚናገረውና ልዩ ኃይሎችን ወደ መከላከያ ለማዞር የበለጠ አገራዊ ኃይል አቅም ለመፍጠር ነው እንጂ ለማፍረስ አይደለም የሚለው አባባል ፍፁም ውሸት ነው። የታሰበው የአማራ ልዩ ኃይልን ለማፍረስ ነው። ለምን የአማራ ክልል ብቻ የሚል ጥያቄ ሲነሳ ሌሎችንም ያጠቃልላል በሚል ህዝብን ለማሞኘት እየጣሩ ይገኛሉ። ነገር ግን ህዝቡ ስለነቃ ሰሚ አላገኙም። ዋናው እቅዳቸውን በአምባሰደር ተሾመ ቶጋ በኩልና ከአማራ ክልል የፓሊስ ኮሚሺነር በኩል ትጥቅ ፍቱ የሚለው ትዕዛዝ በግልፅ እንዲታወቅ ሆኗል።

 

ለመሆኑ የአማራ ክልል በአሁኑ ሰዓት የህልውና ስጋት የለበትም? በትክክል ከህወሓት፣ ከኦነግና ከኦሮሚያ ልዩ ኃይል እንዲሁም ከሱዳን ወራሪ ጦር ከፍተኛ የህልውና ስጋት አለበት። በአሁኑ ሰዓት ኦነግ በአጣየና አካባቢው ጦርነት በአማራው ላይ ከፍቷል። የኦሮሚያ ልዩ ኃይል በብዙ የአማራ ከተሞች በመከላከያ ስም በመግባት በህዝቡ ላይ ግልፅ ጦርነት እያካሄደ ንፁሀንን እየጨፈጨፈ ይገኛል። ህወሓት በፌደራል መንግስት በመታገዝ ወልቃይትና ራያን በጦርነት አሸንፎ ለመያዝ ሰራዊቱን እያስጠጋ ይገኛል። መንግሥትም ታስረው የነበሩ የትግራይ የጦር መኮንኖችን በመፍታት ወደ ትግራይ እየሸኛቸው ይገኛል። ሱዳን የአማራ ልዩ ኃይል ይዞት የንበረውን ካምፕ መልቀቅ ተከትሎ ጦሯን አስገብታ የኢትዮጵያን መሬት በስፋት እየተቆጣጠረች ትገኛለች። እንግዲህ ይህ ከሁሉም አቅጣጫወች የጦርነት ስጋት ባለበት ሁኔታ ነው አማራው ትጥቁን

 

እንዲፈታ የተወሰነበት። ለምንድን ነው ይህ የሚሆነው ቢባል የተፈለገው አማራው ያሉትን ጥያቄዎች ሁሉ ትቶ በባርነት ታዛዥ ሆኖ እንዲኖር ብሎም የኦነጉ መንግሥት አዲስ አገር የመፍጠሩን ወይም የኦሮሞን የበላይነት ለማረጋገጥ የወጠነውን ፕሮጀክት እውን ለማድረግ እንቅፋት እንዳይፈጥርበት ለማድረግ ነው። ይህን በመረዳት ልዩ ኃይሉም ሆነ ህዝቡ ውሳኔውን እንቃወማለን ብሎ ለሰላማዊ ሰልፍ ሲወጣ ጨፍጫፊ ኃይል ተልኮበታል። በብዙ ሚዲያወች እንደተዘገበው አብዛኛው ወደ አማራ ክልል ለወረራ የገባው የመከላከያ ልብስ የለበሰ የኦሮሞ ልዩ ኃይል መሆኑ ተረጋግጧል። ይህ ወራሪ ኃይል በፍፁም ጭካኔ ህዝቡን በከባድ መሳሪያ እየጨረሰው ይገኛል። ብዙወች ተገድለዋል እንዲሁም ቆስለዋል። ህዝቡ ግን ለህልውናው በመዋደቅ ላይ ይገኛል። መሆንም ያለበት ይኸው ነው። የዓለም አቀፍ የአማራ ሕብረት ከተገፋው የአማራ ህዝብ ጎን መቆሙን ያሳውቃል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አገር አውዳሚውና ከፋፋዩ የኢህአዴግ/ብልፅግና አገዛዝ ሀገሩንና ወገኑን ከጥፋት ከሚታደገው ፋኖ ላይ አይኑንም እጁንም ያንሳ!

 

የአማራ ክልል መንግሥት በዚህ ወሳኝ የትግል ምዕራፍ ወቅት ህዝቡን ክዶ ከወራሪው ኃይል ጋር ወግኖ መቆሙ እጅግ አሳዛኝና አሳፋሪ ተግባር ነው። አሁንም የበለጠ ደም መፋሰስ ሳይፈጠር ከህዝቡ ጎን በመሆን የትግሉ አካል እንዲሆን ጥሪ እናቀርባለን።

 

ኢትዮጵያ አገራችን ከዚህ የበለጠ ትርምስ ውስጥ እንዳትገባ ለመንግሥትና ለሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የሚከተሉትን ጥያቄዎች እናቀርባለን፦

  1. በአማራ ህዝብ ላይ የተደቀነው የህልውና ስጋት እስኪቀረፍና አስተማማኝ ሰላም እስኪገኝ ድረስ ልዩ ኃይሉ በፊት በነበረው ሁኔታ እንዲቀጥል፣
  2. አማራው በወልቃይትና ራያ በከፈለው መስዋዕትነት ያስመለሰው ማንነትና ያስመለሳቸው አፅመ ርስቶቹ ህጋዊ እውቅና በአስቸኳይ ተሰጥቷቸው በአማራ ክልል ስር እንዲተዳደሩ እና የሁለት አመት ውዝፍ በጀት እንዲያገኙ እንዲደረግ፣
  3. ወደ ክልሉ የገባው የመከላከያና የኦሮሚያ ልዩ ኃይል በአስቸኳይ እንዲወጣ፣
  4. በህግ ማስከበር ሰበብ በአማራ ክልል የታሰሩ ፋኖዎች ከነ መሪያቸው አርበኛ ዘመነ ካሴ እንዲሁም ልዩ ኃይሎች በሙሉ እንዲፈቱ፣
  5. በአዲስ አበባና በዙሪያዋ በአማራው ላይ ያነጣጠረ የቤት ማፍረስ ዘመቻ በአስቸኳይ እንዲቆም፣ የፈረሰባቸውም ካሳ አግኝተው በቦታቸው ላይ እንዲሰሩ እንዲፈቀድ፣
  6. በአዲስ አበባ በሺወች የሚቆጠሩ ታፍሰው የታሰሩ አማራወች እንዲሁም ምሁራን ረዳት ፕሮፌሰር ሲሳይ አውግቸው፣ መስከረም አበራ፣ ጋዜጠኞች አባይ ዘውዱ፣ ገነት አስማማው፣ ዳዊት በጋሻው፣ ቴዎድሮስ አስፋው፣ ፓለቲከኞች፣ አንቂወች እንዲሁም ባለሃብቶች በሙሉ በአስቸኳይ እንዲፈቱ እንዲሁም የፍትህ ታጋዩ አቶ ታዲዮስ ታንቱ እንዲፈቱ፣
  7. በወለጋ አማራወች ላይ እየተካሄደ ያለው መንግሥት መር የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ በአስቸኳይ እንዲቆምና ወራሪው የኦሮሚያ ልዩ ኃይልም ከቦታው እንዲወጣ፣
  8. እድሜውን በሙሉ ለአገሩ ሲታገል የኖረው ብርጋዴር ጄኔራል ተፈራ ማሞ ውጭ ወጥቶ ህክምና እንዳያገኝ መከልከሉ ፍፁም ነውር እና ሰባዓዊነት የጎደለው በመሆኑ በአስቸኳይ እንዲፈቀድለት እንጠይቃለን።

 

 

ለመከላከያ ሰራዊት

መከላከያ ሰራዊት ዋናኛ አላማህ ኢትዮጵያን ከጠላት ለመጠበቅ ስለሆነ ከዚህ በወጣ መልኩ በህዝብ ላይ ወረራ ፈፅም የሚል ትእዛዝ ውድቅ ማድረግ ይኖብሃል። ደግሞስ የአማራ ልዩ ኃይልና ፋኖ በችግርህ ወቅት የደረሱልህ በአንድነት በጦር ሜዳወች ተዋድቃችሁ ለድል አልበቃችሁምን? ስለዚህ መከላከያ ከህዝብ ጎን እንድትቆም እንጠይቃለን።

 

ለፓለቲካ ፓርቲዎች

ለፍትህ ዕኩልነትና ዲሞክራሲ የምትታገሉ የፓለቲካ ፓርቲወች በሙሉ ይህ የኦነግ መንግሥት ኢትዮጵያን ለከፍተኛ የህልውና አደጋ ላይ ስለጣላት በጋራ ሆናችሁ እንድታወግዙትና ከያዘው የእብደት ጉዞ እንዲገታ ጫና እንድታደርጉ እንጠይቃለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለዐማራ ሕዝብ፣ ለዐማራ ክልላዊ መንግሥትና፣ ለዐማራ ብልፅግና ፓርቲ የቀረበ የፍትሕ ጥሪ!

 

ለሌሎች ክልሎች መንግሥታትና ህዝብ

የኢትዮጵያ እንደ አገር መቀጠልና ለህዝብ ሰላም የምትጨነቁ የክልል መንግሥታትና ህዝብ መንግሥት እየሄደበት ያለውን የእብሪትና ጉዞ በመቃወም ከተገፋው የአማራ ህዝብ ጋር በመቆም የትግል አጋሩ እንድትሆኑ እንጠይቃለን። በትብብር ይህ እብሪተኛ መንግሥትና ስርዓቱ ካልተለወጡ አገር እየፈረሰ መሆኑ በግልፅ ሊታወቅ ይገባል።

 

ለአዲስ አበባ ህዝብ

የአዲስ አበባ ህዝብ በዚህ የኦነግ መንግሥት እንደደረሰብህ መከራና ግፍ እንዲሁም ውርደት መቸም ደርሶብህ አያውቅም። ነገር ግን ግፉን በሚመጥን መልኩ እየታገልኸው ባለመሆኑ ገና ከዚህ ለባሰ ስቃይ ስለሚዳርግህ በአስቸኳይ በአማራ ክልልና በጉራጌ ዞን የተጀመረውን ህዝባዊ ትግል እንድትቀላቀል ጥሪ እናቀርባለን።

 

ለኦሮሞ ህዝብ

ህወሓት ስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት እየፈፀመ ለነበረው ሰቆቃና ግፍ የትግራይ ህዝብ ተቃውሞ ባለማሰማቱ ከሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር እንዴት የትግራይ ህዝብ እንደተቀያየመ የሚታወስ ጉዳይ ነው። አሁንም የኦሮሞ ብልፅግና ከኦነግ ጋር በመሆን የኦሮሞ መንግሥት ነኝ እያለ በህዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን ግፍና ሰቆቃ እያየህ ነው። ስለዚህ ይህ በስምህ የሚፈፀመውን ግፍ ሳይውል ሳያድር እንድትቃወም ጥሪ እናደርጋለን።

 

ለአማራው ህዝብ

ላለፉት ሃምሳ ዓመታት በተለያዩ የአማራ ጠል መንግሥታት እየደረሰብህ ያለው ሰቆቃ ተነግሮ እንደማያልቅ ለቀባሪው እንደ ማርዳት ነው። ህወሓትና ኦነግ በትብብር ያደረሱብህ መከራ ተዘርዝሮ አያልቅም። በተለይ ግን በዚህ አምስት አመት ውስጥ በአብይ አህመድ የሚመራው የኦነግ መንግሥት እያደረሰብህ ያለው ግፍና ሰቆቃ ግን ፍፁም የተለየ ነው። የወለጋውና መተከል የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ፣ የአጣየ ተደጋጋሚ ውድመት፣ የደራ ሰቆቃ፣፣በአዲስ አብባ ዙሪያ ጅምላ ቤት ፈረሳና መፈናቀል፣ በእምነትህ የደረሰብህ ግፍ፣ ወደ መሰረትሃት ከተማ አዲስ አበባ አትገባም መባል፣ አዲስ አበባ ውስጥ ስራ እንዳትሰራ መከልከል፣ በህወሓት በሴራ እንድትወረርና እንድትወድም መደረግ፣ በድል ጦርነቱን እንዳትደመድም በማድረግ ወደ ድብቅ ስምምነት መድረስ፣ ይህን ተከትሎ በታላቅ መስዋእትነት ያስመለስሃቸውን ወልቃይትንና ራያን ዳግም ለህወሓት ለመስጠት መወሰን፣ እረ ስንቱ ይዘረዘራል አሁን ደግሞ ክልል ብለው በወሰኑልህ ሰፈር የጦር ኃይል በማሰማራት እየወጉህ ይገኛሉ። ለዚህ ወረራ እየሰጠህ ያለኸው ምላሽ የሚያኮራ ነው። በዚሁ አጠናክረህ እንደምትቀጥል እናምናለን። ያለ ስርዓት ለውጥ ከህገ መንግሥት ለውጥ ጀምሮ ሌሎች ያሉህ መሰረታዊ ጥያቄዎችህ መልስ ሊያገኙ ስለማይችሉ ለስርዓት ለውጥ፣ ፍትህና እኩልነት ተግተህ እንድትታገል ጥሪ እያደረግን እኛም ከጎንህ መሆናችንን እናሳውቃለን። አብዛኛው ኢትዮጵያዊም አገርን ከመፍረስ ለማዳን ፍትህና እኩልነት እንዲሰፍን ለምታደርገው ትግል ከጎንህ እንድሚቆም እናምናለን።

 

ፍትህ ለግፉዓን!

የአማራው የህልውና ትግል ኢትዮጵያን ከመፍረስ ይታደጋል!

ዓለም አቀፍ አማራ ህብረት

ዋሽንግተን፣ ዲሲ

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share