ሙስሊሞች በተለያዩ ከተሞች መንግስትን ሲያወግዙ፤ መሪዎቻቸውን ከጎናችሁ ነን ሲሉ ዋሉ

(ዘ-ሐበሻ) መንግስት ጂሃዳዊ ሀረካት የተሰኘውን ፊልም ከለቀቀ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ በተለያዩ ከተሞች የተጠራው የሙስሊሞች የተቃውሞ ጥሪ በአዲስ አበባ እና በተከያዩ ከተሞች ከአርብ ጸሎት በኋላ ተደረገ።

‹‹እኛ አቡበከር አህመድ ነን!›› በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው የዛሬው የአርብ ተቃውሞ በአዲስ አበባ አንዋር መስጂድ እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ መገኘቱን የዘገቡት የዘ-ሐበሻ ምንጮች ተቃውሞው በሰላም መጠናቀቁን አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቴሌቭዥብ ‘ጂሃዳዊ ሃረካት’ በሚል ባስተላለፈው ፊልም መሪዎቻቸውን በሽብርተኝነት በመወንጀሉ በዚህ ቁጣ ገንፍሎ ወጥቷል የተባለለት ሕዝብ የታሰሩት ኮሚቴዎቻቸው አሁንም ህጋዊ ወኪሎቻችን መሆናቸውን በማያሻማ ሁኔታ እናረጋግጣለን ብለዋል፡፡
በአንዋር መስጊድ የተገኘው ህዝብ በመሪዎቻቸው ላይ በደረሰው በደልና ግፍ እጅግ ያዘነና የተቆጣ መሆኑ ያስታውቃል ያሉት የዜና ምንጮቻችን በርካታ ሰዎችም ወደ አላህ ሲያለቅሱ ማስተዋላቸውን አትተዋል፡፡ መንግስት ህዝቡንና ኮሚቴዎችን ለመለያየት በድራማው ያደረገው ጥረት መክሰር ብቻ ሳይሆን በተቃራኒው ህዝቡ ለኮሚቴው ያለውን ፍቅርና ክብር እንዲጨምር ማድረጉን የዛሬውን ተቃውሞ የታደሙት በመቶሺዎች የሚቆጠሩ ሙስሊሞች አረጋግጠዋል ያለው ዘገባው ጨምሮም “አሁንም ለህዝብ ጥያቄ ፍትሃዊ ምላሽ ከመስጠት ውጪ ህዝብን ሊያረጋጋ የሚችል ምንም መፍትሄ እንደሌለ መንግስት ሊረዳ ይገባል” የሚል መል ዕክት ያስተላለፈ ተቃውሞ ነበር ብለዋል።
ሙስሊሞቹ በተቃውሟቸው “እኛ አቡበከር ነን”
” እኛ ካሚል ሸምሱነን”
” እኛ ያሲን ኑሩ ነን”
” እኛ አህመድ ሙስጠፋ ነን”
“እኛ ኑሩ ቱርኪ ነ”
” እኛ ኮሚቴው ነን”
“ኢቲቪ ውሸታም”
“መሪዎቻችን ይፈቱ”
የሚሉ መፈክሮች በሰፊው መደመጡን የዘገቡት የዘሐበሻ ምንጮች በተቃውሞው ላይ የታሰሩት መሪዎቻቸው ፎቶግራፎችንም ይዘው እንደነበር ገልጸዋል። በአዲስ አበባ የተደረገን ተመሳሳይ ተቃውሞ በሌሎችም ከተሞች መደረጉን ጨምሮ የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ተቃውሞው እንደተጠናቀቀ በህዝቡ መሀል ግጭት ለማስነሳትና ባስ ለማሰበር ሶስት የአንበሳ አውቶብሶችን (ማለትም 41፣12፣13 ቁጥር) ባሶችን እንዲገቡ ተደርጎ ከይርጋ ሃይሌ ህንፃ ላይ በቪዲዮ ለመቅረፅ ጥረት ቢደረግም ህዝቡ “አንሰብርም፣አንሰብርም” በማለት ባሶቹን በሰላም አሳልፏል ሲሉ ምንጮቻችን ከስፍራው ዘግበዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  አንዷለም አራጌ እና የቃሊቲው ህይወት
Share