“ ፕሮ ፖ ጋ ንዳ “ ስትነዳ እንዳትገለበጥ ፤ በ2015 እንኳን  ተጠንቀቅ – ሲና ዘ ሙሴ

+ፕሮ ፓ ጋንዳ ። ፕሮፖ ጋንዳ ። ፕሮ ፓጋን ዳ ። ፕሮፖ ጋን ዳ ። ፕሮ ፖ ጋ ንዳ ። ፕሮ … ወዘተ ።  ፕሮ ብቻውን እግር ኮስ ተጫዎች ነው ። ፕሮ ጎረምሳም ነው ። ፕሮ በአንድ  ሙያ የዘለቀ እውቀት ያለው ሰው መጠሪያ ነው ። pro (   Noun pro (plural pros) . A prostitute ሸርሙጣ ማለት ነው ።  እናም ደግሞ ፤   በፀሐፊው  ፣አገርኛ  ትርጉም ፣ ፕሮፖጋንዳ ማለት ፤ ፕሮ ፖጋ ንዳ ማለት ነው ። በትዕዛዝ ፖጋ መንዳት ። እንግዲህ ፖጋ መንዳት ማለት በወጉ ወይም ያለወጉ መበጥረቅ ማለት ነው ። መበጥረቅ ለጌቾ ምላሱ እና ለእንትና እና ለሥ ነው ። ለCNN እና ለመሳሰሉት ደግሞ በሴራ  የሚነዳ  ነው ።

እንግዲህ ፕሮ ማለት ሸርሙጣ ማለት ከሆነ  ። የሚነዳውም በቢዝነስ ነው ማለት ነው ።  አንድ ሰው ለጥቅሙ ሲል ፕሮ ሆኖ ፓ ን ለማጥፋት አቅሙን ሁሉ በመጠቀም ሲያጠቃ ፣ ወይም ወደ ፖ ሲነዳ የሚያሳብቅ ድርጊትም ነው ። በመላሱ ጉልበት እና በሐሰተኛ መረጃዎች ወይም ራሱ በፈበረካቸው ሰቆቃዎች ጠላቴ ያለውን ያለርህራሄ ለመጨፍለቅ ሲንቀሳቀስ ከየነው የ ፕሮ _ ፖ_ጋ _ ንዳ  ትርጉሙ ይገባናል   ።

በጥቂት ሰዎች በሚዘወር የፖለቲካ ፖርቲ ፣ በፈላጭ ቆራጭ ባለሥልጣን ፣ ( በመንግሥት ፣ በቡድን ፣ በግለሰብ ) ፕሮ ፖጋ ንዳ ሲጦጦፍ በየቀኑ ይስተዋላል  ። በአምሥቷ ቀን የ2014  ጳጉሜ እንኳን ፖጋ ሲነዳ አይተናል ። እናም በየቀኑ ” ፖጋ ይነዳል  ! ”

የሚገርመው ግን ፣ ርካሽ ተወዳጅነትን ለማግኘት   ከሚሊዮን በላይ በረንዳ አዳሪ  ( በወደቀ ቤት ፤ በየአሥፓልቱ ጥግ ፤ በአሥፖልት ማቋረጫ ፤ በየመሥጊዱና በየቤተክርስቲያኑ ዙሪያ ) በእርዛት እየኖረ በጣት ለሚቆጠሩ ቤት ተሠራ ተብሎ ፤ በግብዝነት ከበሮ ይደለቃል ። የመላዕክት ሥም ለግለሰቦች ይሰጣል ። የመንግሥተ ሠማይ አጋፋሪ መሆን አለባቸው ይባልልናል    ። ያሳፍራል ። መንግሥት ሥራውን ሥለሰራ ለምን ከበሮ ይመታለታል ። ለምን ፖጋ ንዱ ይባላሉ ። የመንግሥት ጋዜጠኞች ። ቴሌቪዢኖች እንደኢየሱስ የማያስበውን እንደ ፈሪሳውያን ሁሉ የከበሬታ ሥፍራ የሚፈልገውን ሰው ድርጊት እንደ ፅድቅ ድርጊት ያሥጮኻሉ ። የዛሬው መንግሥት በህዝብ ገንዘብ ጥቂት ምንዱባንን እና ባለፀጎችን በብዛት  ሰብስቦ ያበላል ። ይበላል ። የድሮ ነገሥታት ደግሞ አዲስ አበቤን  በግድ እየገረፉ ግብር ያበሉ ነበር ። ፍቅር እሥከመቃብር መፅሐፍ ላይ እውነቱ በደራሲው በሐዲስ ዓለማየሁ ተገልፆለሰ ። የንጉሥን ግብር መብላት ግዴታ ነበር ። ይኽንን እውነት የእኛ ጋዜጠኞች አያወሩም ። ሁሌም መሪን እግዜር አድርገው መሣል ግዴታቸው ሆኗላ ። ለዚህም ነው   “ አይ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችንም ወልዳለች ። “ ሲል በዓሉ ግርማ  በታላቅ ምፀት የተናገረው ። በኦሮማይ መፅሐፉ ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የዐብይ አህመድ ሰለስቱ ማንነቶች  (ዐብይ ሰባኪው ፤ ዐብይ ተዋኒው እና ዐብይ አጼ በጉልበቱ) 

ለመሆኑ በዛሬው ሥልጡን ዘመን ፣ አንድ መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት መሆኑንን ተረድቶ አቅም ያለውን ዜጋ በማሥተባበር    ለመላው በረንዳ አዳሪ ያውም ለበዛው ወጣት ዘላቂ ብልፅግና ከልቡ ካልሰራ መንግሥትነቱ ምን ላይ ነው    ? የመንግሥት አጀንዳ ሰው መሆን የለበትም እንዴ ? ድንቡሎ ሣያወጣ ፣  ኪሱ ሣይጎድል ፣  ምድረ ባለሥልጣን በመንግሥት ሀብት  እየተዘባነነ ፤ በሚሊዮን የሚቆጠር ዜጋ በቀን አንዴ እየቀመሰ ኑሮን እየገፋ ፤ ጥቂት የማይባለው ከተሜ ነጋ ጠባ ድንች በዳቦ እና የበቀሎ ቂጣ ፣ በቀን አንዴ እየበላ እያደረ ፤ በግብዝነት በየቴሌቪዥኑ ፅድቅ ያልሆነ ተግባርን በማሣየት በየቤቱ ያለውን ደሃ ማሥገምጀት ተገቢ ነው እንዴ ? የምን አትርሱን ነው ?   መቼ ይሆን  ከዚህ የግብዝነት ገብያ የምንላቀቀው !? መቼ ይሆን ፕሮ ፖ ጋ ንዳውን ሉጋም የምናሥገባለት ?

ድሮ “ በቄላ አሮብናል ። “ ይባል ነበር ። ዘንድሮ ደግሞ በቆሎ በአቅሙ ለደሃ አሮበታል ። ሸምቶ መብላት አልቻለም ። …

ጠ/ሚሩ በአዲስ አበባ ለጥቂት ግለሰቦች ያማረ ቤት ሥለሰሩላቸው የኢትዮጵያ ህዝብ እንደ ህዝብ ምን ተጠቀመ ። እርሳቸው እኮ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒሥቴር እንጂ የአዲስ አበባ ከንቲባ አይደሉም ።   ለብዙሃኑ ምሥኪን ህዝብ  ፤ ለጠቅላላው ዜጋ ማሰብ እና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማድረግ መንግሥታዊ ኃላፊነታቸው ነው ። ወጥ እያወጡ ማሥተናገድ ለፅድቅ ያበቃኛል ብለው ካሰቡ ተሣሥተዋል ። ሥንትና ሥንት ጨላፊ በዚች አገር ላይ እንዳለም በቅጡ ይረዱት ። ይኽቺ አገር የጨላፊ ችግር የለባትም ። ዋናው መደገሱ ላይ እንጂ እጅን ታጥቦ ለመጨለፍማ ማን ያንሳል ????

በጣት የሚቆጠሩ አዲስ አበቤዎች ፣ አጋጣሚው እረድቷቸው ፣ ከወደቀ ቤት ወደ ቪላ ቤት መሸጋገራቸውሥ የኢትዮጵያን መንግሥት የሚያሥሞግሰው ነው እንዴ  ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሁለቱ ስምምነቶች ወግ - ኤፍሬም ማዴቦ

ጠቅላዩ ፣ በግል ያደረጉት መልካም ሥራ ከሆነ ፤ ያ ይጠቀስ እና ይሞገሱ ። ከኪሳቸው እንጂ ከመንግሥት ካዝና ( ከከተማ መሥተዳድሩ ወይም ከአካባቢው ካለ ባለሀብት ) ድንቡሎ ሳይቀበሉ የገነቡት እና ለድሆች በግል ሠርተው የሰጡ ከሆነ በእውነቱ ሊመሰገኑ ይገባቸዋል ። ከዚህ ውጪ ከሆነ እና የሌሎች ተሳትፎ በዚህ ጉዳይ ከለበት ግን ቢያንስ እነዚህ ግለሰቦችን መጥቀስ ተገቢ ነው   ። አለበለዚያ ይሄ “ ፕሮ ፖጋ ንዳ “ እንጂ ሌላ ትርጉም አይሰጠውም   ። …

የሚገርመው ፤ በመንግሥት  ሚዲያዎች ዓመት በዓል በመጣ ቁጥር ደግነት ይሰበካል ። ሰው አንድ ቀን በልቶ ይሞት ይመሥል ፣ ለአንድ ቀን ደስታ ለዋለ ገንዘብ ፣ “ በተነ ሠጠ ፅድቅም ሆኖ ተቆጠረለት ። “ ይባልለታል ። 365 ቀናትን በችጋር ና በችግር የሚኖረውን በሚሊዮን የሚቆጠር ኢትዮጵያዊውን ህይወት በዘላቂነት ለመቀየር በፕሮግራም ፣ በተፃፈ ዕቅድ ፣ ዓላማ እና ራዕይ የሚንቀሳቀስ ፣ በፊደራል ደረጃ የሚመራ አንድ ማዕከል ያለው  በህዝብ የሚደገፍ ተቋም መመሥረትን ግን ማንም አያስበውም ። …

በየዓመቱ ጳጉሜን በሥብከት ማሳለፍ ፣ “ በፕሮ ፖጋ ንዳ “ መንከውከው እንጂ ለደሃው ብዙሃን ጠብ ያደረጉለት ነገር የለም ።

የሠላም ቀን ብሎ በሰላማዊ ሠልፍ ፍለጠው ቁረጠው ሲሉ መዋል ። መንገድ በመዝጋት ዜጎችን ማበሳጨት ፣ ሠላማቸውን ማደፍረስ እንጂ ፤ በወጉ በአዳራሽ ተቀምጦ ሥለ ሠላም መወያየት ፤ ሃሳብ መለዋወጥ የለም ።

በበኩሌ ፤“ዛሬም  በደርግ የግዳጅ  የሰልፍ መንገድ ቀበሌዎች መጓዛቸው ያርፋል ወይ ? “ ብሎ ይኽ ፀሓፊ ይጠይቃል ። “ አያርፍም ። “ እንደህነ መልሱ ያውቃል   ። ብልፅግና በዚህ የግዳጅ ሠልፍ እንደ ኢህአዴግ እና እንደ ደርግ የሚቀጥል ከሆነ ገና አምሥት ዓመት ሳይሞላው ጀዘበ እንዴ ?!  ያሰኛል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ባዲሱ ዘመን ለሰው ልጅ ህይወት ክብር እንስጥ

ይህ ፀሐፊ በጥገናዊ ለውጥም ሆነ ለጥቂቶች ሎቶሪ መሠል ዕድል በመሥጠት በአገር ለውጥ ለሚጣ ከቶም እንደማይችል ይገነዘባል ። ለውጥ የሚመጣው “ በተደራጀ ተቋም ፣ በተፃፈ ፕሮግራም ፤ በሚመለከታቸው ምሁራን በወጣ እቅድ እና እቅዱን ለመፈፀም በሚከናወን ተከታታይነት ባለው ተጨባጭ ሥራ ነው  ። “ ብሎም ይመክራል ። ዜጎች ከድህነት ሊወጡ የሚችሉት “ በፕሮ ፖ ጋ ንዳ “ አይደለም ። እናም ሁሉንም ዜጋ ፣ ላብአደሩን ፣ የመንግሥት ሠራተኛውን ፣ ገበሬውን ነጋዴውን ፣ መከላከያውን ፣ ፖርቲዎችን ፤ ወዘተ ። በማሥተባበር የድሃ፣ደሃ ፣ ደሃ የሆኑትን እና በየከተሞቻችን  በየአሥፓልቱ  ማሥታሽ በመሳብ ፣ እየጦዙ ያሉትን ፣ በተጨባጭ በመርዳት ነው ታላቅ አገራዊ ለውጥ ለማምጣት የሚቻለው ። እናም ብልፅግናዎች በ 2015 ዓ/ም በአዲሱ ዓመት ህዝቡን ለማበልፀግ ከልብ መነሳሳት ይጠበቅባችኋል  ። አንዳንዶቻችሁም የራሳችሁ ሥግብግብነት ሊያሳፍራችሁ ይገባል ። ሌብነት ይብቃችሁ ። በህዝብ ፣ በደሃው ሥም ከቀበሌ ጀምሮ ሣንቲም እየሰበሰባችሁ ከፊሉን ኪሳችሁ በመጨመር መብልፀጉ ያሳፍራችሁ ።  ሼም ይግባችሁ ። ባካችሁ አርፉ ። አራዳ ሁኑ ። ከተኛችሁበት ንቁ ። የመንግሥት ባለሥልጣን ያውም ህዝብን ለማገልገል የተመረጠ ባለአደራ  ሆኖ መሥረቅ ፣ በዛሬው ዘመናዊ ጊዜ በቁም መሞት ነው ። እናም በአዲሱ ዓመት “ ፕሮ _ ፖ_ጋ _ ንዳ “  ውን ፤ ቀነሥ  አድርጉና  ወደ ገደለው ግቡ ። ለታይታ ፣ ለሾ ፣ ለፖ ጋ መንዳት ፣ የራሳችሁን መልክ በቴሌቪዢን ለማየት አትጣደፉ ። ካለፉት መንግሥታት ያለማሥተዋል በጊዜ ተማሩ ። የኢትዮጵያን ህዝብ የልብ ኩራት ከእናንተ ይልቅ ነጮች አሣምረው እንደሚያውቁትም ተረዱ ።

1 Comment

  1. ፕሮፓጋንዳ ነድቶ የተገለበጠ የለም ፕሮፓጋንዲስቶች አገርም ህዝብም ይገለብጣሉ እንጅ፡፡ ደመቀ መኮንን እንዲህ መቀለጃ ከሚሆን በቃኝ ተከብሬ ልኑር ብሎ ቢጠይቅ ምናለበት? ነው ወይስ የድሮዋን ካርድ እየመዘዙ እያሳቀቁት ነው? የሰውን ችግር የሚያውቅ እራሱ ነው፡፡ ባለፈው ምርጫ ምናልባት የእሱ ቁጥር በልጦ ተገዳዳሪ ይሆናል በማለት ተመስገን ጥሩነህን ምርጫው ላይ አስገቡት መራጩ እንዲከፈል ይህ በሌሎች ጎሳዎች አልተደረገም አስተዋጽዎው ከግምት ሳይገባ ከአብይ በፊት ያድረገኝ ብሎ አብይን የሸፈነበት ተረስቶ ዛሬ ተሳቅቆ ይኖራል፡፡ ከዚህ አብይ ከዚያ ሽመልስ ከዚያ አዳነች አቤቤ መከራውን ያበሉታል ያሳዝናል ይችም ኑሮ ሁና ይሄ ሁሉ ውርደት፡፡ቆረጥ አድርጎ በቃኝ ብሎ እያረሰ ቢኖር ይሻለው ነበር ከዚህ ሁሉ ውርደት፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share