September 10, 2022
14 mins read

ኳ!ኳ!ኳ!ኳ ! አጭር  ልቦለድ  ቅምሻ ለአዲሱ ዓመት

ethiopiannewyear

እንኳን ለ2015 ዓ/ም አደረሳችሁ ፤ በከንቱ የሞቱትን ወንድሞቼና እህቶቼን ፈጣሪ በአፀደ ገነት ያኑርልኝ ። ፈጣሪ በቃ ይበለን ። እዝጊኦ ማህረነ ክርስቶስ ።

በመኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

ምዕራፍ 1

ሁላችንም ለማኞች ነን ፡፡ ለማኝና  ተለማኝ በራሱ  በለማኙና  በተለማኙ የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ የገዘፈ ስፍራ አላቸው ፡፡ ይኼ ተለማኝና ለማኝ እናም ተለማማኝ ሰው ሁሉ ፣ ለ21ኛው  ክ/ዘመን ሊበቃ የቻለው ባለው ሥር የሰደደ የአብሮነት ቁርኝት ወይም ማህበራዊ መሥተጋብር ሰበብ ነው ፡፡

የሰው ልጅ በአንድ ወቅት በሆነ  ሥፍራና ቦታ በጊዜው ከሁለቱ አንዱን  ሆኖ መገኘቱ ግድ ነው ፡፡ ለማኝ  ወይም ደግሞ ተለማኝ ፡፡  የልመና መገለጫው ብዙ ነው ፡፡ በመሆኑም   ሁላችንም  በየእለቱ ስንለምን   እንስተዋላለን ፡፡

ሰው “ለማኝ” የሚለውን ስያሜ ለማግኘት የግድ በየአደባባዩና  በየመንደሩ ሲለምን  መታየት የለበትም ፡፡ ማንኛውም ሰው በተለያየ ጊዜ ቦታና ስፍራ በተለያዩ  አስገዳጅ እና  ኢ-አስገዳጅ ሁኔታዎች በአንድ በተወሰነ ጊዜ እና ቦታ አንዱ ለማኝ ሌላው ደግሞ ተለማኝ ሆኖ ይገኛል ፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ለማኙ ተለማኝ እንዲሆን ህይወት ታስገድደዋለች ፡፡

እያንዳንዳችን በህይወት ጎዳና ላይ እየተራመድን ኑሮን እየኖርናት ፤ አኗኗራችንን በወጉ  ብናስተውለው ሁላችንም የምንኖረው የልመና  ህይወት መሆኑን  በቀላሉ እንገነዘባለን ።

ሰው ሆይ ! ኑሮህ እንዲህ እኮ የደመቀው በልመና ጧፍ ብርሃንን እያገኘ ነው ፡፡ አንዱ ከአንዱ አየተበዳደረ ጧፉን ባያበራ ኑሮ ይህቺ የምንኖርባት ምድር  እንዲህ  የደመቀች አትሆንም ነበር ፡፡

ያለ ልመና የምድራችን ህይወት ጣፋጭና መራራነቷን አይታወቅም ፡፡ ያለመለማመን ወይም ያለሰጥቶ መቀበል ጣፋጭና መራራን ማጣጣም ከቶም  አይቻልም ፡፡ የሰው ህይወት እርስ በእርስዋ እየተዘካከረች ለመሰንበት ከቶም አትችልም ፡፡

ሰው ለምኖ  ማግኘት  ያለበትን  ” ለምኘስ ከማገኘው  ለምን ጥነቅር በሎ አይቀርም ፡፡ ”  ብሎ እጅግ አንገብጋቢና አስፈላጊውን ነገር ቢያጣ ህይወቱ በምሬት እና በስቃይ የተሞላች ትሆናለች ፡፡ ያለ ልመና ህይወት ትርጉመ ቢስ  ናት ፡፡

ከእያንዳንዱ ግለሰብ በስተጀርባ በልመና የሚገኝ ሆኖም ግን  ግለሰባዊ  እርካታን የሚያስገኝ ሀብት አለ ፡፡ ይህ  ሀብት በመኖሩ ነው ህይወት ያለልመና  ትረጉመ ቢስ የምትሆነው ፡፡ ዋጋ አልባ ለመሰኘት የምትበቃው፡፡

ከእያንዳንዱ ግለሰብ ጀርባ በልመና የሚገኝ ሆኖም ግን ግለሰባዊ እርካታን  ሊያጎናጽፍ የሚችል  ትልቅ ሀብት አለ ። ይህ  ሀብት  በመኖሩ ነው  ህይወትን ያለልመና ትርጉመቢስ እንድትሆን  ያደረጋት ፡፡ ተለማኙ ሰው ለለማኙ የሚሰጠው ፤ በገንዘብ የማይለካ    የግሉ የሆነ ተፈጥሯዊ  ሀብት አለው ፡፡ ይህንን  ተፈጥሯዊ ሀብት በተለመነ ጊዜ እንዲሁ ይሰጣል ።በነፃ ። ሰጪም በምላሹ ሳይዘገይ  በተራው በደቃዎች  ልዩነት ለምኖ  በነፃ ይቀበላል ። ማንም ሳያንኳኳ አይከፈትለትም ።

እናም  የሰው ልጅ  ለልመና ሁሌም የአምሳያውን በር ሲያንኳኳ የመኖር ግዴታ አለበት ።    በሩ የተንኳኳበትም የተለመነውን ለለማኚ ፣ ይነስም ፣ ይብዛ  መስጠቱ አይቀሬ ነው ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም የሚለው ይህንኑ ነው፡፡

“ለምኑ ይሰጣችሁማል ፡፡ ፈልጉ ታገኙማላችሁ ፡፡ መዝጊያውንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል ፡፡ የሚለምን ሁሉ ይቀበላልና ፡፡ የሚፈልግም ያገኛል ፡፡ መዝጊያውንም ለሚያንኳኳው ይከፈትለታል ፡፡ ”

ሉቃስ 11፡ 9-11

ከመፀሐፍ ቅዱስ ጥቅሱም ሆነ  ከገሃዱ አለም የምንገነዘበው እውነታ ልመና  ከምጽዋት ጋር  ብቻ ከእለት እንጀራ ጋር ብቻ የተገናኘ  ያለመሆኑን ነው ፡፡ ለማኝና ልመና ከድህነት ጋር ብቻ የተቆራኘ አይደለም ።  በዓለም   ላይ  በህይወት  የሚኖር ሰው ሁሉ ከልመና ጋር የተቆራኘ ነው ፡፡ ለምኖ ይቀበላል ፡፡ ተለምኖ ይሰጣል ፡፡ ይኸው ነው፡፡

 

ሁላችንም የህይወት ለማኞች ነን ፡፡ ይህ አጭር ልቦለድም የለማኙ ዓይነ  ስውር  የአቶ ልእልና  የመሪ  ልጃቸው የዝናሽ  ልእልና ቁነጽል ታሪክ ነው፡፡

በታሪኩ ፍሰት  ውስጥ ጎልቶ  የሚታየው የጠጅ ቤት ጫዋታ ነው ፡፡ የሀገራችን  ጠጅ  ቤቶች  ዛሬም ድረስ የተጨበጨበላቸው የወሬ መድረኮች መሆናቸውን  ደግሞ በምስክር ማረጋገጥ አያስፈልግም ፡፡

 

ምዕራፍ 2

ታደሰ

ምጽዋት ናፋቂው ለማኝ እንደብዙዎቻችን የህይወት ለማኞች ገና  ጎህ ሲቀድ ነው ለሥራ የሚነሳው ፡፡ ጉልበት  የወጣበት ነገር ሁሉ ሥራ ነውና ልመናን ሥራ ብንለው አይደልም በሎ ማነው የሚሞግተን ?

ተሞጋቹ ራሱ በማንኛወም ሰዓት በመነሳት ልብሱን ከሚለበስበት ሰዓት አነስቶ በሥራላይ እነደሆነ ይወቀው ፡፡ ማንም ሰው ሆድ አሰካለው ደረስ ለመተኛት ከቶም አይችልም ፡፡ ደግሞስ  ልተኛስ  ቢል “ታደሰ” የተባለ ጠላቱ መች ያስተኛውል፡፡

እናም ለማኙንም “ታደሰ” አያሰተኛውም ፡፡ የ “ታደሰ ” ህልውና   የተመሰረተው በእሱ ልመና ላይ በመሆኑ እና አካሉ   ራሱ ፤ ያል “ታደሰ ” አንፃ ራዊ  እርካታ ፤ ህልውናው  አደጋ ላይ እንደሚወድቅ በመገንዘቡ ዘወትር በለሊት ባንኖ ወፍ ሳይንጫጫ   ለልመና ዝግጁ ይሆናል  ስርክ  አዲስ  የሆነው “ታደሰ”  መቼ ከስጋት ውጪ ያደርገውና  ? በዚህ ዓለም ላይ ሲኖሩ ያለአንዳች ሃሳብ የለሥራ ለጥ ብሎ  እንቅለፍን መላፍ ፤ ብሎ ነገር የለም ፡፡

ሰርክ የሚታደሰው “ታደስ” በራሱ መቼ የስተኛና፡፡በቃኝን የማያውቀው  “ታደሰ ” የለማኞች ሁሉ ስጋት ነው ፡፡ ታደሰን  አስደስተው  ራሳቸውም  ለመደሰት  የግድ በሌሊት ተነስተው  በተለመደው  የምጽዋት መለመኛ መደበኛና  ኢ-መደበኛ ቦታቸው ላይ መገኘት ግዴታቸው ነው ፡፡ ህልውናቸው  ቀጣይ እንዲሆን የግድ መለመን ይኖርባቸዋል ።

ለመሆኑ “ታደሰ” ማነው ? ታደሰ በእያንዳንዳችን ሰውነት ውስጥ የሚገኝ በፊት ለፊታችን ከደረታችን ቀጥሎ በእምብርታችን  ዙሪያ  ልሙጥ ሆኖ  ፤ በሰፊ ቆዳ የተለበጠ   ፤ እንሥራ መሳይ የምግብ ማሣለጫ ጎተራ ነው ።  ሆድ ነው __ ታደሰ፡፡

“ታደስ”  ሆድ ነው ፡፡ ሆሌም አምጡ ፤ አምጡ ፤ ባይ ነው ፡፡ በየሰዓቱ ይታደሳል ፡፡ ካልበላንና ካልጠጣን ይገለናል ፡፤ ታዳሹ ሆድ ፊት ለፊታችን በመሆኑ በጠገብንና በተራብን ጊዜ እያሻሸን አናጽናናዋለን ፡፡ ሆድ ፊትለፊታችን ሆኖ በመፈጠሩ እድለኞች ነን ፡፡ሆድ በጀርባችን  ቢሆን ኖሮ በህይወት የመቆየት አቅማችን ውስን ይሆን ነበር ፡፡ ጎትቶ ሥለሚጥለን መራመድ አንችልማ !!

የማይበላና ካካ የማይል ፣የሞተ ብቻ ነው ፡፡ እሱንም አሥቡት ። ለመኖር መብላት ፣መጠጣት አና ከበለውና ከጠጣው ውሰጥም፣ የማይጠቅመውን ማሰወገድ ግድ እኮ ኘው ደ እና እንዴት ?

“ታደሰ ” ባዶ ከሆነ እንቅልፍ አያሥተኛም  ፡፡ ሁሌ በየሰዓቲ አምጤ ይላል ። ቁርስ ፣ምሳ፣ ራት፣ እንዳለም ያሳስባል ፡፡ በሌሊት ለልመና ፣ ለማኙ እንዲሰናዳ ያስገድዳል ፡፡ “ታደሰ ” እያለ እንኳን በምጽዋት የሚኖር ለማኝ ይቅርና  የህይወት ለማኝ የሆነው ተራ ሟቹ ሰው  ያለ ሃሳብ መተኛት ከቶም አይችልም ፡፡

በተለያየ የስራ መስክ  የተሰማራን ሁሉ፣ እርስ በእርሳችን እየተለማመንን  የምንኖር ነን ፡፡ ሰው ሁላ የታደሰ ቁራኞ ነው፡፡

ለዚህም ነው ምጽዋት ፈላጊው ለማኝ በማለዳ ተነሥቶ  “ታደሰን የምታውቁ አትጨክኑ ብኝ ! ቀን ስለማይሰጠው ስለታደሰ  !?  ጠዋት ጥርግ  አድርጎ በልቶ ፣፣ከሰዓት አላየሁም ፤  ስለሚላችሁ ፤ ሥለ ታደሰ  ?! “  በማለት በመንገዳችሁ ላይ ሲለምን የምታገኙት ።

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Ethiopian new year cards free
Previous Story

በአዲስ ዓመት በዕርቅ የታጀበ የተስፋ ጉዞ!!

pardon
Next Story

ማሩኝ! – በላይነህ አባተ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop