ኮሎኔል መንግሥቱ ካሳ

ሰዎች ገና ከመፈጠራቸው በፊት እጣቸው በግንባራቸው ጠገግና በእጃቸው አሻራ ላይ በፈጣሪያቸው የታተመ መሆኑን የአንድ አንድ ሰዎችን የሕይወት ፈር ስናጤን የምንቀበለው ሀቅ ሆኖ ይገኛል። እንደ ጠዋት ፀሐይ ጎህና ማለዳን ታግለው ብቅ ይላሉ። በቀትርም ወቅት ከፍተኛ የብርሃን ሀይላቸውን ይናኛሉ። በአመሻሹም እንደ ጀንበር ሁሉ ይጠልቃሉ። ድንገትም ከፍተኛ ደመና ፀሐይን ለአፍታም ቢሆን ሰንጎ በመያዝ ብርሃን ከመፈንጠቅ ያግዳታል። ተፈጥሮ ትክክለኛ ሂደቷን ለጥቂት የታደሉ ብቻ እንጂ ለብዙዎቻችን ሳታዳላ በትክክል እድል አታውቅም።

ለኮሎኔል መንግሥቱ ካሳዬ ሕይወት ከላይ ለፀሐይ የተሰጠ ተምሳሌት ለእርሱም በትክክል ይሠራል። ተወለደ፣ ዳኸ፣ ተራመደ፣ ጎለመሰ፣ በመስከን ለማርጀትና ለመሞት ግን ዕድል አላገኘም። በዚሁ የአጭር ዘመን ዕጣ ፈንታው ግን ብዙ ትእይንት አከናውኗል።

መንግሥቱ ካሳዬ ከአባቱ ከአቶ ካሳ ፋንታዬና ከእናቱ ከወይዘሮ አልጋነሽ በለጠ በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብረ ታቦር ከተማ በ1941 ዓ.ም ተወለደ። ዕድሜው ለትምህርት እንደ ደረሰ ደብረ ታቦር ከተማ በሚገኘው የአጤ ቴዎድሮስ ትምህርት ቤት እስከ ስምንተኛ ክፍል ከተማረ በኋላ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በጎንደር ከተማ ቀ.ኃ.ሥ. ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተምሯል። በዚሁ ትምህርት ቤት እያለ አየር ኃይል ለመቅጠር የሚሰጠውን ፈተና በአመርቂ ውጤት አለፈና የልጅነት ምኞቱ ወደ ነበረው አየር ኃይል ተቀላቀለ።

ደብረ ዘይት (ሐረር ሜዳ) በመምጣት ከሲቪል ወደ ወታደርነት የሚለውጠውን ስልጠና ወሰደ። የበረራ ትምህርቱንም ተያያዘው በበረራ ለመመረቅ ክንፍ ለማግኘት ሥራ ብቻ ሳይሆን እድልንም ይጠይቃል፤ ሁሉም ነገር ጥብቅ ነው፤ በሁሉም ነገር ንቁና ብቁ ሆኖ መገኘት ያስፈልጋል።

ስለ አውሮፕላን በረራ ሞተር ኢንጂን ናቪጌሽን፣ ኢንስትሩሜንት፣ ኤሮዳይናሚክስ፣ ብቻ ሳይሆን በጠባይ፣ በዲሲፒሊን ሁሉ ብልጫ ማሳየት ይጠበቃል። አንድ ሰው በራሪ ከሆነ በኋላ መኮንን ይሆናል፤ መኮንን ሲሆን መሪ ነው የሚሆነው፤ ለዚህም ኃላፊነት የሚሰማው፣ በቀላሉ የማይቆጣ፣ ተስፋ የማይቆርጥ፣ ትእዛዝ መስጠት የሚችል፣ ደፋር፣ አርቆ አስተዋይ፣ ሌሎች የሚተማመኑበት፣ ከፍተኛ ችሎታ ያለው፣ ከሁሉም በላይ ጨዋ መሆን ይገባዋል።

የበረራ ትምህርት ቤት የኤቲክስ ሕግ ከሆኑት ዋንኛው እጩ መኮንን “አይዋሽም” የሚለው ነው። የበረራ አስተማሪዎች ከላይ የተጠቀሱትን ሁሉ ከበረራ ተማሪው ውስጥ ጨምቀው ለማውጣት የተለያየ ዘዴን ይጠቀማሉ። ተማሪው እነዚህን ሁሉ በሚገባ ተቋቁሞ ማለፍ አለበት። ትንሽ ጥፋት ከትምህርት ቤቱ መባረርን ያስከትላል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከታሪክ ማህደር: ፀሐፊ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ (ጠ/ሚኒስቴር)

ከአስራ አራቱም ክፍለ ሀገር ተማሪዎች ወደ አየር ኃይል ከመጡ በኋላ የሚመረቁት ከበዛ አምስት አለበለዚያም ሁለት ወይም ሦስት ናቸው። በአንድ ወቅት ብቻ በ1970 ከገቡ ተማሪዎች ከአስር በላይ የሆኑ በራሪዎች ጨርሰው ክንፍ አግኝተዋል። ጉድ ተባለ፤ በአየር ኃይል የበረራ ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያው ነበርና።

ጀግናው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ብቻውን ተመርቋል፤ ኮሎኔል ክንፈና ተስፋዬ ሁለት እንደ አህያ ጡት በመሆን ጨርሰዋል። ነጥረውና እንደ ወርቅ በእሳት ተፈትነው ነው የሚወጡት ቀላል አይደለም። ከዚህ በኋላም እንደ ትምህርት የመቀበል ችሎታቸው የአእምሮ ፍጥነትና የበረራ ልዩ ክህሎታቸው ጀት አብራሪ፣ መጓጓዣ አብራሪ፣ ሄሊኮፕተር አብራሪ በመሆን ይመደባሉ።

መንግሥቱ ከላይ በተጠቀሱት እርከኖች ውስጥ አልፏል። የጀት አብራሪ ብቻ ሳይሆን ጀት አብራሪዎችን አስተምሯል። ብዙ ተማሪዎችን አሰልጥኗል። የጀት በረራ እውቀቱን አሪዞና ስቴት በሚገኝ ከፍተኛ የበረራ ተቋም ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር በመሆን ተምሮ በመጨረስ በክብር ዲፕሎማውን ተቀብሏል። የአየር ለአየር ውጊያ፣ የተለያዩ አውሮፕላን ላይ የሚጠመዱ መሣሪያዎችን ተጠቅሞ ምሽግ፣ ዋሻ፣ መኪና እና ታንክን የማጥቃት ትምህርት ተምሯል።

የኢትዮጵያ ሕዝብም ሆነ የጦር ክፍል አባሎችን ቅስም ሰባሪ የሆነ የሱማሌ ጦርነት ሲቀሰቀስ መንግሥቱ ካሳ ገና አፍላ ጎረምሳ ነበር። በማስተማር ላይ እያለ ነበር ጦርነቱ የፈነዳው፤ ከራሺያ በቢሊዮን መሣሪያ ያጋበሰችው ሱማሌ ኢትዮጵያን ወረረች፤ ኢትዮጵያ እነ አሜሪካ ገንዘብ የተከፈለበት መሣሪያ ሳይቀር ከለከሏት፤ ከጀግኖች ልጇቻ ጋር በመሆን ያላትን ይዛ ተሰለፈች። አየር ኃይል የመሬቱንም ሆነ የሰማዩን ጥቃት መመከት ግዴታው ሆነ። ለዚህም ቅሌን፣ ጨርቄን ሳይል ቀፎው እንደተነካበት ንብ በያለበት አቆበቆበ። በራሪው፣ ቴክኒሽያኑ፣ አየር መርማሪው፣ የጦር መሣሪያ ገጣሚው፣ የአስተዳደር ሠራተኛው፣ የአውሮፕላን አካል ጠጋኙና በያጅ ሁሉ በአንድነትና በተናጠል ለጦርነቱ ምላሽ ለመስጠት ተዘጋጀ።

አየር ኃይሉም በየስኳድሮኑ ለጦርነቱ ተዘጋጀ። የነበሩት የጦር አውሮፕላኖች ኤፍ 5ኢ፣ ኤፍ 5ኤ፣ ዳኮታ፣ ካምቤራ፣ የተለያዩ ሄሊኮፕተሮች በያሉበት በተጠንቀቅ ሆኑ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አለም አቀፍ የሴቶች ቀን) #March8 በሙያቸው የመጀመሪያ በመሆን በግንባር ቀደምትነት የተመዘገቡ ሴት ኢትጵያውያን

ከኤፍ 5ኢ እስኳዶርን ብርሃኑ ውብነህ፣ በዛብህ ጴጥሮስ፣ መንግሥቱ ካሳዬ፣ ለገሰ ተፈራ፣ ባጫ ሁንዴ፣ አፈወርቅ ኪዳኑ፣ አሸናፊ ገብረጻዲቅ ሆነው ተሰለፉ።

ከኤፍ 5ኤ እስኳድሮን አምኃ ደስታ፣ ተጫኔ መስፍን፣ ብርሃኑ ከበደ፣ ተሻለ ዘውዴ፣ ንጉሴ ዘርጋው፣ ተስፋ ደስታ በመሆን ለጦርነት ተዘጋጁ።

ከካንቤራ ከባድ ቦንብ ጣይ እስኳዶርን መስፍን ኃይሌ፣

አሰፋ መክብብ፣ ብዙወርቅ በቀለ ከሌሎቹ ጋር ለመዝመት ተነሱ።

(አንባብያን እዚህ በወቅቱ የነበረውን ማዕረጋቸውን የመጽሐፉ ጸሐፊ ስላልፃፈው በምንጭነት የተጠቀምኩት መጽሐፍ ላይ ያለውን ነው ያስቀመጥኩት ምክንያቱም ከዚህ ጦርነት በኋላ አብዛኞቹ ባለ ከፍተኛ ማዕረጎች እንደሆኑ ባውቅም በወቅቱ ጸሐፊው ያስቀመጠው ስማቸውን ብቻ መሆኑ ይታወቅልኝ።)

ሱማሌ በምድርም በአየርም ጥቃት ጀመረች።

እነ መንግሥቱ ካሳዬ የኢትዮጵያ ዳኮታ አውሮፕላን ተመቶ ሲወድቅ የመቱትን ወዲያው ተከታትለው እንደ በጋ ዛፍ ቅጠል አረገፉት።

መንግሥቱ ካሳዬ ከብዙዎቹ ጋር አብሮ ቢበርም ከለገሰ ተፈራ ጋርና ከባጫ ሁንዴ ጋር ሲሆን ደስ እንደሚለው የበረራ ጓደኞቹ ይናገራሉ። ሲበዛ ደፋር በመሆኑ በፍጥነት ድንገት ከተፈጠረ ችግር ውስጥ የመውጣት ውሳኔና ችሎታ ስላለው ማንኛውም በራሪ በመንግሥቱ ላይ እምነት አለው። እነዚህ ሦስት ሰዎች አየር ላይ ሲወጡ ሰማይ ይጠባል፣ አውሮፕላኖቹ ወደ ሰንጋ ፈረስነት ይለወጣሉ፤ ሲፈልጋቸው ጉግስ ወይም ደንገላሳ ይጋልባሉ። ሌሎቹም እንደ እነሱ በድፍረት የተሞሉ ናቸው። ሱማሌ ለአስራ ሰባት ዓመት የገነባችውን አየር ኃይል እነ መንግሥቱ በአስራ ሰባት ቀን ከምድርም ሆነ ከአየር አጠፉት። በዚሁ በ9ኛው ስልታዊ ተዋጊ እስኳድሮን ሰማይ ላይ የሱማሌን ራሺያ ሰራሽ 8 ሚግ 21 ፣ 3 ሚግ 17 አውድመዋል። ታንክ፣ መድፍ፣ ስንቅና ትጥቅ ገምቶ ለመናገር የሚያዳግት ነው።

የኢትዮጵያ አየር ኃይል የሱማሌን ጦርነት እጅግ በተፋጠነ መንገድ ከተወጣ በኋላ ይጠቀምባቸው የነበሩትን አውሮፕላኖች በመለዋወጫ እጥረት ምክንያት ትቶ ወደ ራሺያ ሰራሽ አውሮፕላኖች መጋባት ነበረበት። በዚህም ምክንያት ራሺያኖች የተወሰኑ የኩባ በራሪዎችና እጅግ የሰለጠኑ የራሳቸውን የፋብሪካ የሙከራ በራሪዎችን (ቴስት ፓይለትስ) ወደ ኢትዮጵያ ላኩ። መንግሥቱ ካሳዬ በዚህ ወቅት ኤፍ 5ኢ ይበር ነበር። አንድ ቀን መንግሥቱ ወደ አውሮፕላኖች ማስተናገጃ ማማ ወጥቶ ለአንድ ፓይለት መልእክት ሲያስተላልፍ ከራሺያው የሙከራ በራሪ ጋር መተራረብ ይጀምራሉ። የራሻው ፓይለት በንቀት ዓይን

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከታሪክ ማህደር: መምህር ፣አርበኛ፣ ዲፕሎማት እና ታላቅ ደራሲ ክቡር ዶ/ር ሀዲስ ዓለማየሁ

“እኔ ከአንተ ጋር አልበርም፤ ይልቅ እኔ ያሰለጠንኩት የኩባ ተማሪ አለና አንተም ኤፍ 5ኢህን ይዘህ እሱም ሚግ 21 ይዞ ‘ዶግ ፋይት’ አድርጉ፤ ማናችሁ እንደምትመቱ እንይ” ይለዋል። መንግሥቱ “ከአንተ ጋር ነው የምፈልገው” ይላል።

ራሺያው በንቀት “ተማሪዬ ከኔ የበለጠ ነው፤ እሱን ገጠምክ ማለት እኔን ገጠምክ ማለት ነው” አለ። አለቆች ፈቀዱ።

መንግሥቱ ተነሳ፣ የራሺያው ቴስት ፓይለትም ተነሳ፤ ከበረራ ማስተናገጃ ማማው የፍልሚያ ትእዛዝ ተሰጣቸው።

የራሺያው ፓይለት አንዴ መንግሥቱን ዒላማ ሳያስገባው መንግሥቱ ከአስራ ሁለት ጊዜ በላይ ዒላማ እያስገባው አስመዘገበ። የሁለቱን ውርርድ የሰሙ የአየር ኃይል አባሎች የአየር ላይ ትእይንቱን ለማየት ግልብጥ ብለው በካፍቴሪያ፣ በተርሚናል፣ እንዲሁም በማማው አካባቢ ሆነው መመልከት ጀመሩ። ጀግናውና ቀልጣፋው መንግሥቱ ካሳዬ አሸናፊነቱን ለአየር ኃይል አባሎች ለማብሰር በራናዌው አካባቢ ዝቅ ብሎ በመብረር አውሮፕላኑን ሶኒክ ሳውንድ ውስጥ አስገባና በረረው፤ ጠቅላይ መምሪያው፣ የአውሮፕላን ማስተናገጃ ማማው መስታወቶች እንዳሉ በመርገፍ ጨው ሆኑ።

ወዲያው በአጭር ቀናት ውስጥ የነበሩትን የአሜሪካን ስሪት አውሮፕላኖች የኢትዮጵያ መንግሥት ለኢራን በጨረታ ሸጠና ፊቱን ሙሉ በሙሉ ወደ ራሽያ ስሪት አዞረ። መንግሥቱ በጥቂት ቀናት ውስጥ የራሽያን አውሮፕላኖች አቀላጥፎ መብረር ጀመረ፤ ከመብረር አልፎ ማስተማሩን ሁሉ ተያያዘው ራሽዮኖች እንደ ሱማሌ በኢትዮጵያውያኖች ላይ ሊቀልዱ አልቻሉም፤ ሊማሩ ሄደው አስተምረው ተመልሰዋል።

እነ ማሞ ጉደታ ለበረራ የተፈጠሩ ልዩ ጉዶች ናቸው። የራሽያን ሚግ ለመብረር ከአምስት ሰዓት በላይ አይፈልጉም።

በሐረር፣ በጅጅጋ፣ በቀብሪደሃር፣ ፌር ፌር ሰማይና ምድር ላይ ተዋድቀው እፎይ እንላለን ሲሉ እንደገና ጦርነቱ በሰሜን ከራሳቸው ወንድሞች ጋር ሆነ። መንግሥቱም የወንድማማች ጦርነቱን ባይፈልገውም ወታደር ነውና ተዋጋ፤ እንድ ሌሎቹ የአየር ኃይልና የምድር ጦር ወንድሞቹ ያ አንጸባራቂ ኮከብ ከናቅፋ ሰማይ ረገፈ።

ምንጭ…

የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አየር ኃይል (1920-1966 ዓ.ም)

ሻምበል ፍቅሩ ደበበ

#አብዮታዊው_ሰራዊት_ገፅ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share