ለፖለቲካ ትርፍ መሣሪያ አትሁን – ከገብረ አማኑኤል፤

እልቂታችን የመነጨው ከመብታችን መደፈር ነው፤ለፖለቲካ ትርፍ መሣሪያ አትሁን፤ በህብረት ቆመህ አገርህን አስተዳድር፣ ፈጣሪ በሠጠህ ሃብት በጋራ ተጠቀም፤በአገርህ ላይ ያለህን መብት እወቅ፤ መብትን ማስከበር መብትን ከማወቅ ይጀምራል፣

በአገራችን በመካሄድ ላይ ያለው በህዝብ ስም ሥልጥንን የማቆየት የተረኛ ፖለቲካና በህዝብ ላይ የሚፈጸም ግፍ እጅግ የሚያሳዝን ነው። ከወያኔ ሥርዓት የቀጠለው ህዝብን በህዝብ ላይ የማነሳሳት እኩይ ተግባር በስፋት በመቀጠሉ በቅርቡ ባለፉት ጥቂት ዓመታትና በቅርቡም የደረሰው እልቂት ግልጽ ማስረጃ ነው። ህፃናት፣ እናቶች፣ አዛውንት፣ ወጣቶች፣ ሳይል የንፁሃን ደም አንደጎርፍ እየፈሰሰ ነው። ተረኛው የፖለቲካ አመራር የያዘው ለኢትዮጵያ የማይሰራና የማይበጅ፣ ደረጃው እጅግ ዝቅተኛ የሆነ፣ ከፖለቲካ ተጠቃሚነት በስተቀር፣ በየትኛውም ክልል ላለ ኢትዮጵያዊ ጥቅምን የማያስገኝ የክፋትና የሰውን መብት ፈፅሞ የሚደፍር አሠራርን የተከተለና ከራስ ሥልጣንና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የዘለለ አመራር አለመሆኑን በተግባር ከምናያቸው እውነቶች መረዳት ይቻላል።

በኔ እምነት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ባሁኑ ሰዓት ማድረግ ያለበት መብቱን መነሻ ማድረግ ነው። በቅድሚያ መብቱን ማስተዋል፣ መብቱ የሆነውንና መብቱ ያልሆነን ተረድቶ፣ መብቱን ማስከበር፣ የሌላውን መብትና ጥቅም ማክበር፣ በጋራ በአገር መኖርና ፈጣሪ በሰጠው ሃብት በጋራ በመጠቀም አገርን በአንድነት ማስተዳደር ነው። ይህንንም እውን ለማድረግ፣ ቆሞ የቀረ፣ ያረጀ እኩይ የፖለቲካ አቅጣጫ መታገልና መለወጥ፣ አንዱ የሌላውን መብት ማክበርና ማስጠበቅ፤  ከዚህ አኩይ ሥርዓት ለመላቀቅ የተቀናጀና የተደራጀ ሠላማዊ ትግል፣ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ የሚገኝ የኢትዮጵያ ህዝብ ተቀናጅቶ ማካሄድ ይገባዋል።

የምንታገለው ስለየትኛው መብታችን ነው? የትግሉ ሁሉ መሠረት መብት በመሆኑ ይህንን መመለስ አስፈላጊ ነው።

የሰው ልጅ ከፈጣሪው ከተሰጡት ታላላቅ ነፃነቶች መካከል አንዱ በምድር ላይ በነፃነት መኖር ነው። ፈጣሪ በረቀቀ ጥበቡ ምድርን፣ ውሃን፣ በውስጧም የሚኖሩ፣ አንስሳትና አራዊትን ከፈጠረ በኋላ የሰው ልጅ በዚች ምድር ላይ በሰላም አንዲኖርና በውስጧ ያሉትን ፍጥረታት አንዲገዛ ሥልጣን ሰጥቶታል በሚለው አምናለሁ። ሰዎች በተወለዱበት አገር፣ ህፃናት ቢያንስ መሠረታዊ ፍላጎቶቻቸው ተሟልተው፣ አንደልባቸው ቦርቀውና የሚያስፈልጋቸውን የጤናና የትምህርት አገልግሎት አግኝተው አንዲያድጉ፣ ወጣቶች ተምረው ሠርተው በመረጡት ሙያና ስፍራ ለመኖር እንዲችሉ፣ የእድሜ ባለጸጎችም ከብዙ የድካም ህይወት በኋላ የሚያርፉበት ህይወትና በደህንነት የመኖር፣ ሁሉም ተፈጥሯዊ ነፃነትና መብት አላቸው። ዓለማቀፍ ህጎችና አዋጆችም ይህንኑ ያረጋግጣሉ።

ከላይ በተጠቀሰው የሥልጣንና የኢኮኖሚ ጥቅመኝነት የተነሳ የህዝብ መብቶች ሲጣሱ እንመለከታለን። ሆኖም የመብት ጥሰቶች በህጋዊ ርምጃ እንዲታረሙ መታገል ተገቢ ነው። የሰው ልጅ መብቶች በሃይል ሊገፈፉ አይገባም። የሌሎችን መብት መጣስ የወንጀል ወንጀል መጀመሪያ ነው። ማንም ሰው ከህግ በላይ አይደለም። መብትን የጣሰ በህግ ይፈረድበታል። ይሄ አጠቃላይ ዕውነታ ነው። ወንጀለኛን ወደትክክለኛ ፍርድ ለማምጣት ግን በመጀመሪያ እውነተኛ ሥርዓትን ለማስፈን መታገል አማራጭ የለውም።

እውቀት የተግባር መሠረት ነው የሚል እምነት አለኝ። ታዋቂው የመብት ታጋይ  ጃማይካዊው ማርከስ ጋርቬይ ስለዕውቀት ሲናገሩ ‘’ስለ ታሪኩ፣ ስለ አመጣጡና ስለባህሉ የማያውቅ ህዝብ ሥር አንደሌለው ዛፍ ነው።’’ ይላሉ። በተጨማሪም በርትራንድ ራሴል ‘መልካም ህይወት በፍቅር የሚበረታታና በዕውቀት የሚመራ ነው።” ብለዋል። ስለዚህም ስለመብታችን አንወቅ ምክንያቱም መብታችንን ለመጠየቅ መብታችንን ማወቅና መወያየት ቀዳሚ ነውና። ይህች ጽሁፍ የምትጠቅሰው ከመብቶቻችን ጥቂቱን ነው። ይበልጥ በማንበብና በመጠየቅ በርካታ የሆኑትን መብቶቻችንን ማወቅ ሃላፊነታችን ነው፣ መብትን ማስከበር መብትን ከማወቅ ይጀምራልና።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የተምቤን ስብሰባችን ጉድ አደረገን (አብርሃ ደስታ)

ከፈጣሪ በታች የዓለም መንግስታት ባንድነት ሆነው ስለመብት በየወቅቱ እየመከሩ የሰው ልጆች መብቶችን የሚያረጋግጡ ሰነዶችን አውጥተዋል፣ ተፈራርመዋል። ከነዚህ ሰነዶች አንዱ የሆነው ‘የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት አዋጅ’ ‘Universal Declaration of Human Rights’ የሚባለው ነው። ይህንን አዋጅ አባል አገሮች ተስማምተውበት በከፍተኛ ድምጽ አንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ1948 በፊርማቸው አጽድቀዋል። ይህ አዋጅ የዜግነት መብት፣ ንብረት የማፍራት መብት፣ ስለማሰብና የማመዛዘን መብት፣ የሃይማኖት መብት፣ የማህበራዊ ዋስትና መብት፣ ስለስራ መብት፣ ወዘተ. የሚደነግጉ አንቀጾችን የያዘ  ነው። ባንፃራዊነት ህዝባቸውን በዲሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚመሩ አገሮች ለዘመናት ተጠቅመውብታል።

ይህ አዋጅ በርካታ የሰው ልጆች፣ ሰው በመሆናቸው ብቻ ሊኖራቸው  የሚገቡ መብቶችን ግልጽ በሆነ መንገድ ይዘረዝራል። ከላይ ከተዘረዘሩት በተጨማሪ፣ ማንም ሰው በህግ ፊት በየትም ስፍራ በሰውነቱ እውቅና ያለው ስለመሆኑ፣ ደረጃውን የጠበቀ አኗኗር የመኖር መብት ያለው ስለመሆኑ፣ የትምህርትን መብትና የመሳሰሉትንም የያዘ ነው።

ምንም እንኳን በዚህ ዓለማቀፋዊ አዋጅ ላይ የተካተቱት መብቶች በርካታ ቢሆኑም ለዚህ አጭር ጽሁፍ ግን የምናተኩርባቸው በዜግነት መብትና  የሃይማኖት መብትን ስለማሳወቅ ይሆናል።

የዜግነት መብት

ሰብዓዊ መብት የሰው ልጅ ህይወቱን ሰላማዊ ከሚያደርጉት ጉዳዮች ቀዳሚው ነው። በነጻነት በህይወት መኖሩም ለሰው ልጅ ሲወለድ ጀምሮ አብሮት የሚኖር መብት ነው። በየዘመናቱ ያለው ችግርን የፈጠሩት ሁለት ጉዳዮች ግን 1ኛ የሌላውን መብት መጣስና 2ኛ መብትና ነጻነትን ለማስከበርና ለመጠበቅና ለማስጠበቅ የተሰጠን ስራና ሃላፊነት አለመወጣት ናቸው።

አስቲ ይህ አዋጅ ስለሚደነግጋቸው መብቶች ከወቅታዊ ሁኔታችን ጋር የሚያያዙትን ጥቂቱን አንመልከ።

ከሁሉ አስቀድሞ ይህ ዓለማቀፍ አዋጅ አጽንዖት የሚሰጠው የሰው ልጆች ከልደት ጀምሮ አኩል ስለመሆናቸው ነው። ከመነሻው ኢንደዚህ ይላል።

‘’ማንም ሰው ሌላውን  በቆዳው ቀለም፣ በጀርባ ታሪኩ፣ አንዲሁም በሃይማኖቱ ምክንያት ሰውን የሚጠላ ሆኖ አልተወለደም።  ሰው ሰውን ለመጥላት መጀመሪያ ጥላቻን መማር አለበት። በተመሳሳይ መንገድ ፍቅር አንዲመጣ ፍቅርንም ሊማረው ይችላል ምክንያቱም ሰው በተፈጥሮ ከመጥላት ይልቅ ለመውደድ የቀረበ ነው።’’

በዚህ አዋጅ አንቅጽ 3 የተደነገገው ቁልፍ መብት ደግሞ አንዲህ ይላል።

‘እያንዳንዱ ሰው በህይወት የመኖር፣ የነፃነትና በሰውነቱ በደህንነት (ደህንነቱ ተጠብቆ) የመኖር መብት አለው።

ይህ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት አዋጅ ስለዜግነት የሰጠው ድንጋጌ አንቅጽ 3 ደግሞ ስንመለከት እንዲህ የሚል እናገኛለን።

‘1/ ማንኛውም ሰው የዜግነት መብት አለው።

2/ ማንኛውም ሰው በድንገት የዜግነት መብቱን ሊገፈፍ እንደዚሁም ዜግነትን የመለወጥ መብቱ ሊገፈፍ አይችልም።’

ይህ አንቅጽ ለማንኛውም የዓለም ህዝብ በተለይም ይህን አዋጅ ያጸደቁ እንደኢትዮጵያ ያሉ አገራት ህዝቦች ሊጠቀሙበት የሚገባና ለያንዳንዱ ሃገርና ህዝብ የሚሰራ የዜግነት ክብሩን የሚያስጠብቅ አዋጅ ነው። በዚህ አዋጅ ያሉ መብቶች ስጦታ አይደሉም ለሰው ልጅ የሚገባውና ያለው የራሱ የሆኑ መብቶች ናቸው። ይህ አዋጅ ደግሞ የነዚህ መብቶች ማረጋገጫ ሰነድ ነው። እንግዲህ ይህን ተፈጥሯዊ መብት ነው ፖለቲከኞቻችን መብቶቻችንን ማክበርና ማስከበር ሲገባቸው፣ ለራሳቸው እኩይ አላማና ሥልጣን ሲሉ መሣሪያ ለማድረግ ነጥቀውን ሲያበቁ፣ አንደገና እኛ ሰጠናችሁ ብለው መብትን ሰጪና ከልካይ የሆኑት ህዝብን የሚያንገላቱት።

ይህን አዋጅና አነዚህን አንቀጾች የመረጥኩበት ዋናው ምክንያት አሁን ካለው የአገራችን ሁኔታ ጋር የሚያያዝ ስለሆነ ነው። አንግዲህ አንድ ሰው ዜጋ የመሆን መብት አለው ሲባል አንዲሁ ለመናገር ያህል አይደለም። ይህ ማለት ማንኛውም አንድ ዜጋ በአንዲት አገር አንደዜጋ ሊሰጠው የሚገባውን ጥቅም ሁሉ ዜጎች ሁሉ በእኩልነት አንዲያገኙ የሚያደርገው መብት የዜግነት መብት ነው። ኢትዮጵያዊ ዜጋ እስከሆነ ድረስ የኢትዮጵያ በሆነ ግዛት ሁሉ የሚኖር ሰው ይህን መብት ማንም ሊከለክለው የሚችለው አይደለም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሜዳ ሲቃጠል ተራራ ከሳቀ ያ ተራራ ከሜዳው የበለጠ በእሳት መጎዳቱ አይቀርም - መኮንን ሻውል ልደጊዮርጊስ

ይህን አዋጅ አገሮች ተቀብለው በየህገ መንግስታቸው ውስጥ አካተውታል። የህዝብ አገልጋይና የህዝባቸው ወዳጅ የሆኑ መንግሥታት በተግባር እየተጠቀሙበት ነው። በሌላ በኩል ደግሞ እንደኛ ባሉት ሀገሮች በክህደት የተነጠቀ መብት ሆኖ አንገኘዋለን።

ይህ ድንጋጌ በዓለም አቀፍ ሰነድ ላይ የሰፈረና አገሮችም ህግ አድርገው የሚጠቀሙበት ሲሆን፣ በተጻራሪው የሰዎችን ዜግነት የሚክዱ አንዲሁም አነዚህን መብቶች የማስከበር ሃላፊነት የተሰጣቸው፣ ለዚህም የሚከፈላቸው የመንግሥት አካላት ይህን መብት ባለማስጠበቃቸውና ለጥሰቱ ተባባሪ በመሆናቸው ወንጀለኛነታቸውን አንደሚያረጋግጥ መገንዘብ ይገባል። በመሆኑም፣ ይህንን የዜግነት መብት ከሰዎች ላይ የሚገፉና ሃላፊነታቸውን የማይወጡ ሁሉ ያለጥርጥር በወንጀለኝነታቸው የሚጠየቁ ናቸው።

የዜጎችን በመረጡት የአገራቸው ክፍል የመኖር መብት በአንዳንድ ያገራችን ክልሎች በእጅጉ ተክዷል። መብትን በመካድ ከሚኖሩበት ሥፍራ ማባረር ሳይሆን ገድሎ መቅበር እንደስልት ሲሰራበት ለዘመናት ቢዘልቅም ምንም እንዳልተፈጠረ እያዩ እንዳላዩ በማለፍ የወንጀሉ አካል መሆኑን ያለው የፖለቲካ ሥርዓት እያረጋገጠው በመሆኑ ከተቀናጀ ሠላማዊ ትግል የተሻለ አማራጭ ያለ አይመስለኝም።

የሃይማኖት መብት፣

አለማቀፍ የሰብዐዊ መብት አዋጅ አንቅጽ 18 ስለዕምነት ነጻነት እንዲህ ይላል፣

‘አያንዳንዱ ሰው በነጻነት የማሰብ፣ የማመዛዘንና የሃይማኖት መብት አለው። ይህ መብት ሰዎች የመረጡትን ሃይማኖት ወይም እምነት የመያዝና በግልም ሆነ በማህበር ከሌሎች ጋር፣ በግልም ሆነ በህዝቡ መካከል ስለሃይማኖቱ የመግለጽና የማምለክ፣ ሃይማኖቱን የመተግበርና የማስተማር ነጻነት አለው።’

በዚህ አንጻር የኢትዮጵያን ህገ መንግስት ስንመለከት (የማልስማማባቸውና አንዳንዱ በየትኛውም የዓለም አገራት ህገመንግስታት ፈጽሞ የሌሉ አንቅጾችን የያዘ ቢሆንም)፣ ስለሃይማኖት መብት ከአለማቀፋዊ አዋጅ ጋር አንድ አድርጎ በአንቀጽ 27 ይገልጽና የዜግነት መብትን ደግሞ በአንቀጽ 33 ላይ አንደሚከተለው ይዘረዝረዋል።

አንቀጽ 33 – የዜግነት መብቶች

  1. ማንኛውም ኢትዮጰያዊ/ኢትዮጵያዊት ከፈቃዱ/ከፈቃዷ ውጭ ኢትዮጵያዊ ዜግነቱን/ዜግነትዋን ሊገፈፍ ወይም ልትገፈፍ አይችልም/አትችልም። ኢትዮጰያዊ/ኢትዮጵያዊት ዜጋ ከሌላ ሀገር ዜጋ ጋር የሚፈጽመው/የምትፈጽመው ጋብቻ ኢትዮጰያዊ ዜግነቱን/ዜግነትዋን አያስቀርም፡፡
  2. ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የኢትዮጵያ ዜግነት በሕግ የሚያስገኘውን መብት፣ ጥበቃና ጥቅም የማግኘት መብት አለው፡፡
  3. ማንኛውም ዜጋ ኢትዮጵያዊ ዜግነቱን የመለወጥ መብት አለው፡፡
  4. ኢትዮጵያ ከአጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ጋር በማይቃረን መንገድ በሚወጣ ሕግ እና በሚደነግግ ሥርዓት መሠረት የኢትዮጵያ ዜግነት ለውጭ ሀገር ሰዎች ሊሰጥ ይችላል፡፡

አንግዲህ አነዚህ አለም አቀፋዊና አገራዊ መብቶች ናቸው በሚያሳፍር ሁኔታ ባገራችን ሥርዓት የሌለ በሚመስል መልክ እየተጣሱ ያሉት። ኢትዮጵያዊያን በማንኛውም የአገራቸው ክፍል የዜግነትና የሃይማኖት መብታቸው ወደጎን ተትቶ ከሚኖሩበት አካባቢ እየተመርጡና በሃይማኖታቸው እየተለዩ በመገደልና ንብረታቸው በመውደም ላይ ይገኛል። ይሄ በተለየ ባለፉት ሰላሣ አመታት የተተገበረ ሲሆን አሁን ደግሞ ደረጃው ከፍ ባለ ሁኔታ ዜጎች በግልጽና በማናለብኝነት እየተዘረፉ፣ እየተገደሉና የስነልቡና ጫና አየተደረገባቸው ይገኛል።

አንግዲህ ወንጀለኝነት ህግ መጣስ ከሆነ፣ አነዚህ ከላይ የተጠቀሱትን ህጎች በመጣስ፣ ዜጎችን የገደሉ፣ ያፈናቀሉ፣ ንብረታቸውን ያቃጠሉ፣ የዘረፉና የተባበሩ ሁሉ በወንጀለኝነት የሚጠየቁ ይሆናል። ይህንን ባለን አቅም ሁሉ ድምፃችንን ከፍ አድርገን ልናሰማው ይገባል።

ተጨማሪ ያንብቡ:   ‘ያልታረሙ አንደበቶች ሀገርን ያዘቅጣሉ!’ - ፀጋዝአብ ለምለም ተስፋይ

ዜጎች ደህንነታቸው እንዲጠበቅላቸው ለማድረግ  የሚጠበቅባቸው፣ ታክስ መክፈልና ከመንግስት ጋር መተባበር ነው ብዬ አምናለሁ። መንግስት የህዝብ አገልጋይ ነው እንጂ የህዝብ ገዢ አይደለም። በመብት አክባሪ አገሮች የመንግስት ባለስልጣናት ተሽቆጥቁጠው ህዝብን ያገለግላሉ። መብት በማይከበርባቸው አትዮጵያን በመሰሉ አገራት ደግሞ የመንግስት አካላት በጌትነት ተፈርተው ህዝብን እያሽቆጠቆጡ ህዝብ በሚከፍላቸው ደሞዝና በገዛላቸው መሳሪያ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ያጠቁታል።

የዜጎችን ደህንነት ለመጠበቅ ሃይል እንዲኖረው የተደረገው መንግስት ነው። ይህንንም ሃይል ማለትም ገንዘብ፣ መሣሪያ፣ ወታደር፣ ወዘተ ያገኘው ከህዝብ ነው። የሚተዳደረውም በህዝብ ሃብት ነው። ነገር ግን ይህ ተቋም ዜጎች ጉዳት ሲደርስባቸው ካልተከላከለና ካልጠበቀ ስራውን አልሰራም ማለት ስለሆነ እንደተባባሪ ተቆጥሮ በወጀለኝነት ተርታ ተጠያቂ ይሆናል። ክዚህ ጀርባ የዜጎች መብት አንዲጣስና ዜጎች አደጋ አንዲደርስባቸው ያቀደና ያሰማራው አካልም ከዚሁ ወንጀል ጋራ ይመደባል። ምን ያህል በወንጀል በተመላ ስርዓት ወስጥ አንደምንኖር መመርመርና ማወቅ ይኖርብናል።

ስናውቅ አንጠይቃለን። አለዚያ ፖለቲከኞች ህዝብ በሰጣቸው ሥልጣን፣ የተረጋገጠውንና በተፈጥሮ የተገኘውን የሰው ልጅን መብት፣ አንደለጋሽ መብት ሰጪና መብት ከልካይ ይሆናሉ። ለምሳሌ ዜጎች ተጎድተው መንግስት ይድረስልን ሲሉ ይህንን ማድረግ መንግስት አንደግዴታ ሳይሆን አንደስጦታ የሚቆጥረው ከሆነ ትልቅ ችግር መኖሩን አንድንረዳ ያስፈልጋል። የተጠየቀውን ደግሞ በሃላፊነቱና በህጉ መሠረት ካላደረገ ደግሞ ህግ የጣሰ አካል ይሆናል ማለት ነው። ህግ መጣስ ደግሞ ወጀለኝነት ነው።

ጽለዝህ ማናም አንኳን በልጣብልጥ ፖለቲካ ወሸትና ዓይን ያወጣ ቅጥፈት ስትታለል ብትኖርም አሁንም ከፈጣሪ በታች ባለህ አማርጭ ሁሉ ሁሉም ያገራችን ሰላማዊ ህዝብ ባለው አጋጣሚ ሁሉ ተጠቅሞ በመደራጀት መራራ የሆነውን ሰላማዊ ትግሉን መቀጠል አማርጭ ያለው አይመስለኝም።

በመፈፀም ላይ ያሉት ዘር የማጥፋት እልቂትና የሚፈፀሙ በዓለማችን በዚህ ወቅት የትም የማፈፀሙ ግፎች፤ አንድ ቀን በፍርድ አደባባይ ቀርበው ፍትህ የሚያገኙበት ጊዜ ይመጣል። ኢትዮጵያውያን ሁሉ አሁን ፍትህ ያልተገኘ ቢሆንም ወንጀለኞችን ግን ለይቶ ማውቅ መመዝገብና ማስረጃዎችን ማሰባሰብን ጠንክረን ልንሰራ ይገባል። ወንጀለኞችን ለፍርድ ለማቅረብ ጊዜ ቢወስድም እንኳን፣ በርካታ አገር አቅፍና ዓለም አቀፍ መንገዶች አሉ።

የህግ ባለሙያዎች ከመችውም በበለጠ መዘጋጀትና ህዝቡ መብቱን እንዲያውቅና አንዲጠይቅ መርዳት ይኖርባቸዋል። ህዝብም መብቱን እያስረገጠ መኖር በቃ ማለት አለበት።

ምን ጊዜም ኢትዮጵያዊ ዜግነት በዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት አዋጅም ትርጉም ሆነ በኢትዮጵያ ህግ የተከበረ ነው። ዜግነት ማለት ደግሞ ከሙሉ ክብሩና ጥቅሙ ጋር ነው። ከነዚህ መብቶች አንዱ በማንኛውም የኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ መኖር፣ ሃብት ማፍራት፣ የመረጡትን ሃይማኖት ማራመድና ሌሎች ሁሉን አቀፍ መብቶች የያዘ ነው። ይህን የማያከብሩና የማያስከብሩ ሁሉ ወንጀለኞች በመሆናቸው ውሎ አድሮ በህግ ይጠየቃሉ። እውነት ብትመነምንም ስለማትጠፋ፣ ፍትህ ብትዘገይም ስለምትከበር፣ በፈጣሪ፣ በመብትና በፍትህ ተስፋ አንቆርጥም።  ከጀርመን ናዚዎች መካከል ከግማሽ ምዐተ ዓመት በኋላ ፍርድ ያገኙ እንዳሉ አንዘንጋ።

መብታችንን አንወቅ፣ አውቀንም በሰላማዊ ትግል አናስከብር። ድምፃችን ከፍ ብሎ ይሠማ። ገለልተኛ የፖለቲካ ፓርቲዎች ራሳችሁን መርመራችሁ አቋማችሁን አስተካክሉ፣ ከህዝብ ጋር ትግላችሁን አቀናጁ፤ ፍላጎትና ቁርጠኝነት ካለ መንገድ አለ።

ፈጣሪ ኢትዮጵያን ያድን!

ገብረ አማኑኤል

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share