የፕሬሥ ነፃነትን፣ ከመናገርና ከመፃፍ ነፃነት ነጥሎ ማየት አይቻልም – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ 

285810622 597941755230417 2241969369239480835 n

“ Freedom of speech is the liberty to speak and write without fear of government restraint. It is closely linked to freedom of the press. “

285810622 597941755230417 2241969369239480835 n

ይድረስ  ፣ ለኢትዮጵያ መንግስት ።

ኢትዮጵያ ጠንካራ መንግሥት ያሥፈልጋታል። ይኽንን አምናለሁ። ይሁን እንጂ በየፈርጁ የተጠናከሩ ተቋማት እሥከሌሉ ድረሥ መንግሥት ጠንካራ ለመሆን እንደማይችልም ይታወቃል። የኢትዮጵያን መንግሥት ጨምሮ  ፤ በዚህ በ21 ኛው ክፍለ ዘመን የነቃውን ህዝብ በወጉ ለመምራት የሚችሉት ዘመኑንን የሚዋጁ ተቋማት ሲኖራቸው  ነው። ከዘመኑ ጋር የሚመጣጠን ፣ የፍትህ ተቋም ፣ የወታደራዊ ተቋም ፣ የደህንነት ተቋም ፣ የጤና ፤ የትምህርት የአስተዳደር ና የአገልግሎት   ተቋም ። ወዘተ። ከሌላቸው በእያንዳንዱ አገር ዜጋ ህይወት ና ኑሮ ላይ ትልልቅ ና ትንንሽ ጠባሣ ማሥከተላቸው አይቀሬ ይሆናል።  መንግሥታት ሁሉ።

ይኽንን ኃቅ በአሜሪካ በጥቂት  በቀወሱ ግለሰቦች የእብድ ድርጊት በየጊዜው ፤ ህዝብ በተሰበሰበበት ሥፍራ ፤ በእምነት ቦታ እና በትምህርት ተቋማት ሣይቀር ፣  የሚፈፀመውን ፣ የጦር መሣሪያ ድንገተኛ ጥቃት አንፃር ተመልክቶ  ማረጋገጥ ይቻላል  ። በየትምህርት ቤቱ ፣ የንፁሀን ዜጎች ና የህፃናቶች ፣  የአዱኑን ፣ ጩኸት በየጊዜው የሚሰማው ፣ የጦር መሣሪያ ሽያጪን በወጉ የሚቆጣጠር ተቋም በአሜሪካ ባለመኖሩ ነው ።

አሜሪካ በፍትህ ፣ በወታደራዊ ፣ እና በሲቪል አሥተዳደራዊ ተቋማት ከፍታ ላይ ብትገኝም ፣ እንደ ከረሜላ የሚሸጠውን የመግደያ መሣሪያ በወጉ የሚቆጣጠር ተቋም ግን የላትም ። እናም የአእምሮ መቃወስ ያለባቸው ዜጎች ሣይቀሩ የጦር መሣሪያ ከሚቸረቸርባቸው ሱቆች እየገዙ  እምቦቃቅላዎችን በትምህርት ገበታቸው ላይ እያሉ እጅግ በሚዘገንን ሁኔታ ሲደፏቸው በእንባ ታጥበን መረጃውን እያየን ነው  ።  በነገራችን ላይ በቻይና የጦር መሣሪያ መሸጫ ሱቅ የለም ። ሁሉም መሣሪያ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ነው ያለው ። በመሆኑም  በግለሰብ  የተከሰተ  እንደ አሜሪካ አይነቱ ፣ የአቶማቲክ መሣሪያ  ግድያ እሥከዛሬ  የለም ። ቆየት ባለ ዘመን በአንድ ትምህርት ቤት በጩቤ አንድ ወጣት ቻይናዊ የተወሰኑ ተማሪዎችን ካቆሰለ በኋላ በቁጥጥር ሥር መዋሉ ግን እርግጥ ነው ። የሞተ ግን አልነበረም ። ይኽንን እውነት ሰሞኑንን ሲኤን ኤን በሐሚዲ ዘካርያን በኩል በአሜሪካን የህፃናቱን ግድያ አሥመልክቶ ያቀረበውን ዘገባ ማየት ይቻላል ።

በአሜሪካ መገናኛ ብዙሃን በኩል ፣  የጦር መሣሪያን ሽያጭና የሚሸጡትንም ቀላል መሣሪያዎች ገደብና አይነት ፣ማን እና በምን ሁኔታ መግዛት እንዳለበት ፤  በሽያጭ ህጉ ውሥጥ ፣ የመቆጣጠሪያ አንቀፆችን  በመካተት ቁጥጥሩን ማጥበቅ  እና የጦር መሣሪያ ሽያጭ ልቅ መሆኑ እንዲቀር  በዜጎች ግፊት እየተደረገ ነው ።የአሜሪካ  መንግሥትም በአራተኛው መንግሥት አማካኝነት ፣ በቅርቡ በአንድ  ወፈፊ  አሜሪካዊ ወጣት በትምህርት ላይ ያሉ ህፃናትና መምህራኖቻቸውን ልክ በጦር ሜዳ እንደተገኙ ጠላቶች እየተኮሰ በመግደሉ የተነሣ ፣ የጠመንጃን ቁጥጥር አልባነት ጦሥ ጥንቡሣሥን  በቅጡ የተገነዘበ ይመሥላል ።

የኢትዮጵያ መንግሥትም በሁለት እግሩ ሁለት ዛፍ መውጣትን አቁሞ አንዱን ዛፍ በወጉ በመውጣት ጫፉ ላይ ከደረሰ ፣ የጠመንጃን ፣ የጦር መሣሪያን በየቦታው መነዛት አደጋ  በቅጡ እንደሚገነዘብ አምናለሁ ።

ይሁን እንጂ ዛሬና አሁን ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ቅድሚያ ሰጥቶ መሥራት ያለበትን ሥራ የዘነጋ ይመሥላል ። የጦር መሣሪያ በአማራ ክልል  የበዛበትና እያንዳንዱ አርሶ አደር በለጠመንጃ የሆነው ፣  የኢህአዴግ የከፋፍለህ ፤ የጎሣ ና የቋንቋ  ሥርዓት ፤ ትልቁን ኢትዮጵያዊነት ሥለ አንኳሰው ነው ።

ኢትዮጵያ ከወያኔ   በኋላ በአዲሱ የለውጥ መንግሥት ከወደቀችበት ብትነሣም ፣ ዛሬ ደግሞ ተመልሣ ወደ ነውጥ የምትገባበት እና የምትወድቅበት መንገድ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ እየተፈፀመ ነው ።

አገር ሠላም አጥታ ፤ ክልሎች እርስ በእርስ ጦርነት ውሥጥ ተዘፍቀው ፣ ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ፣ እልል በቅምጤ እንዳይሉ እና ወደ ቀደመው ኢትዮጵያ የሚለውን ሥያሜ የማጥፋት ተልዕኳቸው ሥኬት በተጠናከረ  ኃይልና በተቀናጀ ኃይል መራመድ እንዳይጀምሩ ፤   ባለማወቅ   ለእነዚህ ፀረ ኢትዮጵያ  ኃይሎች ፣ ተባባሪ የሆኑ የመንግሥት እጆች ፣ ዛሬ ላይ መንቃት ይኖርባቸዋል ። ነቅተውም ከአፍራሽ ድርጊት ተባባሪነት ራሳቸውን ማግለል ይጠበቅባቸዋል ። አለበለዚያ ባለማወቅ መከላከያውን ጭምር ለሁለተኛ ጊዜ ሊያፈርሱት ይችላሉ ። በወያኔ ፈርሶ ነበር ። በብልፅግና መንግሥት ግን መደገም የለበትም ።

መንግሥት በሚያሥመሠግነው  መልኩ  የገነባው የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት ፣ እንዳይፈርሥ ከተፈለገ ፣ መንግሥት በሁለት እግሩ ከወጣበት አንድ ዛፍ ላይ ሆኖ መፃኢውን አደጋ በመገንዘብ የሁሉንም ክልሎች ሠራዊት ወደ አንድ ዕዝ በማምጣት የክልል ልዩ ኃይሎችን በሙሉ “ የፈጥኖ ደራሽ  ሠራዊት “ በማለት እንደገና በማቋቋም እንጂ የመከላከያ ሠራዊት ተገዳዳሪ ጦርን እዛና እዚህ በየክልሉ ጡንቻቸው ሲፈረጥም በማድረግ መሆን የለበትም   ።

የክልል ልዩ ኃይል በሙሉ ፣ “  የፈጥኖ ደራሽ ጦር “ ተብሎ በመከላከያ ሥር እንደገና መዋቀር አለበት ። የትግራይ ልዪ ኃይልን ጨምሮ ።  በአዋጅ ጥሪ ሊደረግለት ይችላል ። ይኽም ለውጥ ፣ በልዩ ኃይሉ ጉያ የተጠለሉትን ቱጃር የወያኔ አባላት እርቃናቸውን እንደሚያሥቀራቸው  አሥባለሁ ።

ይኽንን አደረጃጀት ለመፍጠር የሚያሥችሉ የህግ መአቀፎችን በአሥቸኳይ ማውጣት አገራችንን ከእርሥ በእርሥ ግጭት የሚታደጋት እንደሆነ አምናለሁ ። በፍፁም የየክልል ጦር ወይም ልዩ ኃይል ፤ ብሎ ነገር መኖር የለበትም ። ከህግ አሥከባሪ ፣ ከፍትህ አካላት ጋር የሚሰራ ፖሊሥ እንኳን ቢሆን ሥልጠናውን በፊደራል ደረጃ መውሰድ አለበት ። ብሎ ያምናል ይኽ ፀሐፊ ።

የሁሉንም ክልል ፖሊሶች በማሠልጠን በከተማ እና በገጠር እንደ አግባብነቱ ሊመድባቸውም ይገባል ። ይኽንን ሲያደርግም በሥልጠና ወቅት ፣ ሰዎች በሆኑ ዜጎች መካከል መቀራረብን በመፍጠር ጠባብ አሥተሣሠብን ያስወግዳል ።

ይኽንን ሳያደርግ ፣ እንደወረደ ፣ የኢህአዴግን የጦር አደረጃጀት ተከትሎ ፣ በየክልሉ ፣ የክልል ልዩ ኃይል ና ፖሊሥ የሚል ሥያሜ ሠጥቶ አገርን በሠላም ማሥተዳደር ከቶም የሚቻል አይመሥለኝም ።

የአማራ ፋኖንም ሆነ በፋኖ ሥም የሚንቀሣቀሥ ሥውር ኃይልን ትጥቁን በሠላም ለማሥፈታት እና የጦር መሣሪያን ጦሥ ለማሥቀረት የሚቻለው በአዋጅ የነበረውን የየክልሉን ጦር አደረጃጀት አፍርሶ በፊደራል መንግሥት ሥር በማድረግ ና አገሩን በውትድርና እና በፖሊሥ ለማገልገል የሚፈልገውን እና ብቁ የሆነውን በወጉ ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትና የፖሊሥ ኃይል ጋራ እንዲቀላቀል በማድረግ ነው ። ይኽንን ጠቃሚ እና አገርን የሚታደግ ሃሳብ መከላከያው እንደሚቀበለው አምናለሁ ። የሚኒሥትሮች ምክር ቤትም አገርን ለማዳን ሌላ አማራጭ እንደሌለ የሚገነዘብ ይመሥለኛል ። እናም በአፈ ቅቤዎች በልበ ጩቤዎች ሰበብ  ከእውነታው ውጪ በመሆን ተገቢ አይሆንም ። የቀደመው ሥርዓት በፈጠሰው ድንብርብር ውሥጥ እያለን ፤ ሥለመከላከያ ና ፋኖ እንዲሁም ሥለ አገር ሠላምና ፀጥታ ጉዳይ አንሥተው ፣ መንግሥትን ለምን ተቹ ፤ ለምን ለአገር ጎጂ የሆነ የክልል እና የፊደራሉን መንግሥት ሀፀፅ እና ሥህተት አጋለጡ በማለት ፣ ከብዕር ና ከአንደበት ውጪ ጉልበት የሌላቸውን ጋዜጠኞች ና ማህበራዊ አንቂዎችን ማሠርና ማጎሣቆል ፤  ገዢው ፓርቲ ብልፅግና ኃቁን እያወቀ  ከገባበት አጣብቂኝ የሚያላቅቀው ከቶም አይሆንም    ።

ደግሞም መናገር በተፈጥሮ የተሠጠ የፈጣሪ ሥጦታ መሆኑንን አንዳንድ የፓርቲው  ከፍተኛ አመራሮች በቅጡ ቢገነዘቡ ፣ ያልተገባ ማዋከቡን ረገብ አድርገው ፣ ፓርቲውን ከውድቀት ያድኑታል ብዬ አምናለሁ  ። ሠው በንግግሩ ፣ ብቻ ሊታሠር አይገባም ። እገሌን በለው  እረደው ፣ አቃጥለው ፣ ጣለው  እያለ የሚፎክርና የሚያሥፎክር እሥካልሆነ ድረስ ፣   ጣለው በራሱ ትልቅ ችግር ያሥከትላል ።    ሥነ ቃላችንም ችግሩን አበክሮ ይነግረናል ።

የምን ጣለው ጣለው

የምን በለው ፣  በለው ፣ የምን ጣለው ፣ ጣለው ፣  ይቸግር የለም ወይ ደም መላሽስ ካለው ፣ በማለት ። እናም ለእውነተኛ እና ላልተጭበረበረ ፍትህ መገዛት እና ከህግ በታች መሆን እንጂ ፣ በትዕቢት ፣ በማን አህሎኝነት ፣ በአጋዚ ሠራዊት መተማመን ተገቢ አይሆንም ። ከህዝብ አብራክ በወጣ በመከላከያ ሠራዊት ኃይልም መመካት የኋላ ፣ ኋላ ዋጋ ያሥከፍላል ።  ኢህአዴግም በአጋዚ ተመክቶ ፣ በአፍጢሙ ተደፋ እንጂ ፤ በጉልበት ሥልጣኑንን ማሥቀጠል ከቶም አልቻለም   ። ጉልበተኝነት ሌላ ጉልበተኛ ይወልዳል እንጂ  የተረጋጋ ሠላምን  አያዋልድም ።  ። እናም “ ተበታችሁ “ ፣ ብሎ በጭካኔ ለመውገር ፣ መቀርቀሪያ እና አጣና ማንሣት ፤  ናቃችሁኝ ብሎ አንደበትን መዝጋት በህዝብ ያሥጠላል እንጂ አያሶድድም    ። መንግሥትን የሚያሶድደው በፍትህ ፣ በነፃነት እና በእኩልነት ማመን ነው ። ልክ እንደ አሜሪካን መንግሥት የህግ የበላይነትን ከዳኝነት ነፃነት ጋር ፣ በተጠናከረ ተቋም ማረጋገጥ ነው ። መንግሥት የሚጠበቅበት ። ሥልጣኔው ቢያቅተን መልካም አሥተዳደሩን መኮረጅ እንዴት ያቅተናል ፦

የአሀገሬ መንግሥት ፣  ይህንን ሃቅ ከድሮ የአሜሪካን የህግ ታሪክ መገንዘብ ይችላል ። በአሜሪካ የህግ ታሪክ በመናገር መብት ላይ ትልቅ አሥተዋፆ የነበራቸውን ግለሰቦች እያንዳንዱን ህግ ና የወጣበትን መንሥኤ አንብቦ በመረዳት መረዳት ይቻላል ። …

በቀደመው እና አርጅቶ እንደ ጨርቅ በተጠቀለለው ከኋላችን ተከምሮ በሚታየው ዘመን ፣በአሜሪካ ዴሞክራሲ ውሥጥ የዜጎችን ልብ በደስታ ያሞቀ   ! ዕፁብ ! ድንቅ !  ያሰኘ ፣ ውሳኔ በመናገር የተፈጥሮ ነፃነት ፤ የህግ ጉዳይ ላይ መሠጠቱ  በታሪክ ይታወሳል ። ይኼ ጉዳይ የአሜሪካንን ገፅታ በማበላሸት ላይ የጠነጠነ ፣ እሱን ተከትሎ የመጣ የፖሊሥ ክልከላ ነው ። ነገሩ እንዲህ ነው ፣ አንድ አሜሪካዊ የበዙ ቱሪስቶች ዘወትር በሚጎርፉበት ባቡር ጣቢያ ይለምን ነበር ። የአሜሪካንን ገፅታ ታበላሻለህ ተብሎ ፤ እንዳይለምን በፖሊሥ ተከለከለ ። ይኽንን የሰሙ የሰብዓዊ መብት ተሞጋች ጠበቆች የፖሊሥ ተቋሙን ከሰሱ ። በክርክሩም እረቱ እና ሰውየው መለመኑንን ቀጠለ ።     በክርክሩ ወቅት ጠበቆቹ የረቱበት መከራከሪያ ዋና ጭብጥ  ፤ መንግሥታችን ቆም ብሎ በዕውቀት እና በጥበብ እንዲያሥብ የሚያሥችልው ነው ። እናም የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ጠበቆቹ   የረቱበትን ጭብጥ     ። መንግሥት የሰው ሥብሥብ ፤ አንድ  ግዙፍ ተቋም ነውና ። በራሱ ።

መንግሥት  ከእውነት ጋር ከመጋጨት ከእውነት መማር ይጠቅመዋል ። እናም … ለለማኙ አሜሪካዊ ጥብቅና የቆሙለት ጠበቆች ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡት ጠንካራ  ህገመንግሥታዊ  መከራከሪያን በማሥተዋል ይመልከተው ።  የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾቹ ጠበቆች መከራከሪያ ነጥባቸው ይኽ ነው ። ” ይኽ ሰውዬ በተፈጥሮ የተሰጠውን የመናገር ነፃነት ፣ የማውራት ነፃነት ፣ አንዳች ሃሳቡን አውጥቶ ለሌላው   አምሣያው የመግለፅ ፣ የማሳበቅ ፣ የማሳወቅ ፣ ዝባዝንኬ ሣይቀር ለፍልፎ የማሥጠንቀቅ ነፃነት ። ተፈጥሮውን የመጠቀም መብት ፣ የትም ሥፍራ ማንንም እርዳታ የመጠየቅ ። ወዘተ ። ያልተገደበ መብት አለው ። አይደለም ባቡር ጣብያ ፣ በነጩ ቤተመንግሥት ፊት ለፊትም ተቃውሞውን በሠላማዊ መንገድ ማሣወቅ ይችላልና በገፅታ ማበላሸት ሰበብ የግለሰቡ የተፈጥሮ መብት ማፈን አይገባም ። ” የሚል ነበር ። ፍርድ ቤቱም በዚህ መከራከሪያ ነጥብ እውነተኛነት አምኖ ፣ እንዳይለምን  ገፅታ ያበላሻል የተባለውን ዜጋ  ” መለመን መብትህ ነው ። አንደበትህን ማንም የመዝጋት መብት የለውም ። ቀጥልበት ። ” በማለት አሥደናቂ ፍርዱን ሠጥቷል ።

ከዚህ እውነት ተነሥተን የአገሬ ጋዜጠኞች ፣ በተፈጥሯዊ መብታቸው ሃሳብ ከማዋጣት  የዘለለ ምን የሰሩት ምድራዊ ሐጢያት አለ ? …

ተመስገን ደሣለኝን ጨምሮ ፣ ጋዜጠኞች ከመናገር እና ከመፃፍ ባሻገር ዲሽቃ ይቅርና ምላጭ ይዘው መንግሥትን ለማድማት የተሠለፉ ያለመሆናቸው ይታወቃል ። እና ለምን የተፈጥሮ ነፃነታቸው ተገፎ ይታሰራሉ ?

አብይ መራሹ የብልፅግና መንግሥት መለሥ መራሹ የኢህአዴግ መንግሥት ለአሥራአራት ዓመታት የሠጠውን  የፕሬሥ ነፃነት ያህል እንዴት ገና ከጅምሩ መሥጠት አቃተው ? በበኩሌ ገና ሁለት ዓመት ሳይሞላው ማፈን መጀመሩ እጅግ አሥገርሞኛል ። ለማመንም ከብዶኛል ።

እሥከ 1997ድረሥ በግል መፅሔቶችና ጋዜጦች ምን ሲፃፍ እንደነበር የታወቀ ነው ። በተለይም በጦቢያ መፅሔት የሚቀርቡ ሃሣቦች ዛሬ ላይ ሆኜ ሣያቸው በዛሬው የመንግሥት ፍራቻ ግራ እጋባለሁ ። ከአሁኖቹ መፅሔትና ጋዜጦች እጅግ የበዙ እነ አርያ ተሥፋማርያም በብዕር ሥም የሚሣተፉባቸውም ጋዜጦች ነበሩ ።  በካርቶን ሥዕል ሣይቀር እነመለሥ በአሥቀያሚ መልኩ ፣ እንዴት ይገለፁ እንደነበር ዞር ብሎ መመልከት ይቻላል ።

( እኔም በዛን ወቅት ከአሁኑ ጊዜ ሃሳብ እጅግ የጠነከሩ መንግሥትን የሚሸነቁጡ ሂሶች ፣አሥተያየቶችና አሽሙረኛ ፅሑፎች ይሥተናገዱ ነበር ። እኔም የበኩሌን ሃሳብ በኔሽን  ፣ በሪፖርተር ጋዜጣ እና በአዲሥ ዘመን ጋዜጣ ጭምር በዘመነ መለሥ ሃሳብ  አዋጣ ነበር ። )

ዛሬ እና አሁን ጋዜጠኞች እና የተለያዩ ሰዎች ሃሳባቸውን በተለያየ ሚዲያ ያዋጣሉ እንጂ እንደ ቀደመው ጊዜ የመፀሔት ክምር የለም  ። ይሁን እንጂ በዘመኑ ሚዲያ ፣ የሚያዋጡት ሃሳብ የሚረባም ይሁን የማይረባ ሃሳባቸውን ለተደራሲው ማቅረባቸው ሊወገዝ እና ሊያሣሠራቸው አይገባም ። ሃሳቡ ጥፋትን የሚጭር ፤ የጦርነት ነጋሪትን የሚጎሥም ፣ ጥላቻን የሚሠብክ ፣ ከሙያዊ ሥነምግባር ይልቅ ለሆድ የተገዛ ከሆነ ፤  በለው ፣ ግደለው ፣ ጨርሰው ፣ አጥፋው ወዘተ የሚል ይዘት  ካለው ፣ እና ጥላቻን የሚያራግብ ከሆነ ያ ንግግርና ፅሐፋቸው ተጠቅሶ በግልፅ በአደባባይ ፣ ተጠያቂ ሊሆኑ ይገባቸዋል እንጂ ፣ ሊታፈኑ በድንገት በመሣሪያ ታጅበው እንደሽፍታ ወደ እሥር ቤት ሊወረወሩ አይገባቸውም ። ሀግን ከጣሱ በአግባቡ እንደማንኛውም ህግን እንደጣሠ ግለሰብ  ክስ ሊመሠረትባቸው ና በአንድ ፖሊሥ መጥሪያ ፤ ከአንድ ፖሊሥ ጋራ ፣ ወደ ሀግ ሥፍራ ሊሄዱ ይችላሉ ። በአጀብና በአፈና መልክመ መውሰድ እና ከወሰዱ በኋላ ሰበብ መፍጠር በእውነቱ ፀረ ፍትህ ድርጊት ነው ። ይሄ ኩንን ድርጊትም  በሰው ባያሥጠይቅ በፈጣሪ ያሥጠይቃል ።

በነገራችን ላይ ፣ በዚህ አገር ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ጅግራ ማለት እየተለመደ መጥቷል ። ይኽ የመበላላተ የሤራ ፖለቲካ በፍጥነትና በአሥቸኳይ ሊቆም ብቻ ሣይሆን ሊወገድ ይገባዋል ። ” የተናገሩት እና ወይም የገቡት ቃል ፣ ከሚጠፋ የወለዱት ይጥፋ ። ” ይባላል ። እናም ፤ ክቡር ዶ/ር ጠ/ሚ አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን ሢመጡ የገቡት የሠላም ፣ የዴሞክራሲ ፣ የብልፅግና ቃል ነበረ ። በገቡት አጅግ ተወዳጅና አጓጊ በሆኑት ቃላቸው ቢገኙ ፣ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ መጎልበት መልካም ይመሥለኛል ። ያለፉትንመንግሥታት አሥጠሊ ተግባር መንግሥታቸው እንዳይደግም ልባዊ ፍላጎት ካላቸው ያኔ ገና ወደ ሥለጣን እንደመጡ ከሦሥት ዓመት በፊት ፣ ከጅምሩ ከአርቲሥቶች ፣ ከመላው ምሁራን እና የሙያ ሰዎች ፣ ከዳያስፖራዎች ጋር ያደረጉትን ወይይት ቆም ብለው ያስታውሱ  ። እናም የመናገር ተፈጥሯዊ መብትን አክብረው ያሥከብሩ ። ህግን ማሥከበር እና  ለፍትህ የቆሙ ፣  ንፁሐን እንዳይገላንቱ መጠንቀቅ  በበኩሌ  የሚነጣጠሉ ድርጊቶች   እንዳልሆኑ እረዳለሁ   ። እናም የመናገር እና የመፃፍ ነፃነት ለመንግሥት ጭምር እጅግ ጠቃሚ ነውና  መከበር አለበት እላለሁ ።  … (መንግሥትን ያህል ትልቅ ተቋም በአንድ ግለሰብ ጫንቃ ላይ እንደተቀመጠ ቆጥሮም ፣ በአንድ ሰው ላይ ብቻ እውነትና ሐሰት የተቀላቀለበት ትችት መሰንዘርም አግባብ አይደለም ። ህግ አውጪው ፣ ህግ ተርጓማው ፣ ህግ አሥፈፃሚው   እና አራተኛው መንግሥት “ ፕሬሥ  “ ለአንድ አገር ልማትምሆነ ድህነት ፣ ዴሞክራሲም ሆነ ባርነት ተጠያቂ ናቸው ። ፕሬሱ ፣ አንቂ ፣የሠላ ሂሥ ና ትቺት አቅራቢ ፣ አሥተማሪ ፣ አሣዋቂ ና ህሊናንን የሚያሥደሥቱ ና ትውልድን የሚያንፁ ፕሮግራሞችን ዘወትር አቅራቢ ና አሥተናጋጅካልሆነ ። ህግ አውጪው ለለገር ብልፅግና የሚበጅ ህግ ካላወጣ ፣ ህግ ተርጓሚው ህጉን በሚገባ ተርጉሞ ለተግባራዊነቱ ዘብ ካልቆመ ፣ ህግ አሥፈፃሚው ህጉን ወደተግባር  በእውነት ካልተረጓመ በተዋረድ ያሉት ባለሥልጣናት ሁሉ ተጠያቂ ይሆናሉ ና ያኔ ፤ ቀዳማዊ ኃይለሥላሤ ፤ በቀደም መንግሥቱ ኃይለማርያም ፤ ትላንትና መለሥ ዜናዊ ፤ ዛሬ ደግሞ አብይ አህመድ በማለት ክርስቶስ ይመሥል በአንድ ሰው ላይ ወቀሳውን ማዥጎድጎድ የለብንም ።  ለሁሉም የድርሻውን ከፋፍለን በመሥጠት በወጉ ልንተች ይገባናል ። ጠ/ሚ ተዘግቶ ሥለከረመው ቤት ልናሥታውሣቸው ይገባል ። እውንቤቱን በወጉ አፅደተውታል ወይ ? … በማለት ።  ) እናም ፣ በመጨረሻ “ የምን ጣለው ! ጣለው ! የምን በለው ፣  በለው ፣  ይቸግር የለም ወይ ደም መለሽስ ካለው ? “ በማለት ከዱላ በፊት  በጠረጴዛ ዙሪያ ለመወያየት እንትጋ። በማለት ትሁት ሃሣቤን እንሆ ፣ በማለት ፅሑፌን እቋጫለሁ።

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Abiy Ahymed
Previous Story

እንደእናቴ ሣይሆን እንደሚስቴ አውለኝ! ብሥራት ደረሰ

Ethiopia 1 1
Next Story

ኢትዮጵያን እንዴት ከጥፋት እንታደጋት ? – ንጉሤ አሊ

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop