የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራዎች የተጨፈጨፉባቸው በርካታ የጅምላ መቃብሮች መገኘታቸውን የጥናት ቡድኑ ገለጸ

April 3, 2022

የትግራይ ወራሪ ቡድን ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ በርካታ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራዎች ላይ የዘር ፍጅት የፈጸመበት “ሀለዋ ወያነ” በመባል የሚታወቁ የጅምላ እስር እና የጅምላ ቀብር የሚፈጸምባቸው ቦታዎችን ማግኘቱን የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድን አስታውቋል።

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድን “ገሃነም” ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የሚገኙ በርካታ የትህነግ የጉድጓድና የዋሻ ድብቅ እስር ቤቶች ጥናት ሲያደርግ ቆይቶ ከተጠቆሙት የጅምላ መቃብሮች መካከል ለሙከራ አምስቱን አስቆፍሮ ጭካኔ በተሞላበት ግፍ የተረሸኑ ንጹሃንን አፅም አስወጥቷል።

አካባቢውን የጀርመኑ ናዚ 1 ሚሊዮን 4 መቶ ሺ በላይ እስራኤላውያንን ከጨፈጨፈበት “ኦሽዊዝ” የተባለ ማጎሪያ ጋር አነጻጽረው “የኢትዮጵያው ኦሽዊዝ” ሲሉ የገለጹት የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምር ቡድን አባላት “ገሃነም” በተባለው የትህነግ የድብቅ እስር ቤት በርካታ ሺህ ንጹሃን ማለቃቸውን በወቅቱ በእስር ላይ የነበሩና ከሞት የተረፉ የወራሪ ቡድኑ የጥቃት ሰለባዎችን ዋቢ አድርገው ገልጸዋል።

ትህነግ ይህን ድብቅ እስር ቤት የመረጠበት ምክንያት አካባቢው ሰው ከሚኖርበት ርቆ የሚገኝ ዙሪያው በከፍተኛ ሰንሰለታማ ተራራ የተከበበ ከመሆኑም ባሻገር በኃይል ይዟቸው የነበሩትን የወልቃይት፣ ጠገዴና ጠለምት አካባቢዎች አማካኝ ቦታ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ከሁሉም አካባቢዎች ንጹሃንን እያፈነ ወስዶ ለማጎርና ለመጨፍጨፍ ምቹ በመሆኑ ነው ተብሏል።

በዚህ አሰቃቂ እስር ቤት የታሰሩ ንጹሃን በሚደርስባቸው ሰቆቃ ምክንያት ራሳቸውን ማጥፋታቸውን፣ የትህነግ ታጣቂዎች በየቀኑ ታሳሪዎችን እየወሰዱ ይገድሉ እንደነበርና የብዙዎቹ አስከሬን በአካባቢው የሚገኝ ቃሌማ ወንዝ ላይ ይጣል እንደነበር ከሞት የተረፉት አዛውንቶች ለጥናት ቡድኑ ቃላቸውን ሰጥተዋል።

የድብቅ እስር ቤቱ ውስጥ በበሽታና በርሃብ፣ በድብደባ ተሰቃይተው እንዲሁም በትህነግ ታጣቂዎች ለሚገደሉት እስረኞች ቀብር ይቆፍሩ የነበሩት እስረኞች እንደነበሩም ለማወቅ ተችሏል።

ባለቤቷ “ከፋኝ” የተባለ በወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ህዝብና መሬት ላይ የተቃጣውን ወረራ ለመቀልበስ የተቋቋመ ታጣቂ ኃይልን ተቀላቅሎ ትህነግን በመታገሉ የታሰረችው የወልቃይት አማራ እናት ለጥናት ቡድኑ እንዳስረዳችው እስር ቤቱ እጅግ አሰቃቂ ከመሆኑ ባሻገር የትህነግ ታጣቂዎች ይፈፅሙት የነበረው ወንጀል አስከፊ እንደነበር ገልፃለች።

“በላይ ድንጋይ የተረበረበበት ጉድጓድ ዉስጥ ነበር የሚያስሩን፡፡” የምትለው የአይን እሟኛ በአንድ ጉድጓድ ቢያንስ 10 ሰዎች ይታሰሩ እንደነበር ትናገራለች። “ገሃነም” ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በርካታ ጉድጓዶች እና ዋሻዎችም የንጹሃን ማሰሪያ የነበሩ ሲሆን ምግብና ውሃ በ24 ስዓት አንዴ ብቻ ይቀርብ እንደነበር እማኞቹ አስረድተዋል።

የጥናቱ እማኝ ሆና የቀረበችው ሌላ እስረኛም “ሁሌም ማታ ማታ ከመካከላችን ስም ይጠሩና ይዘዋቸዉ ይወጣሉ፣ ከዚያ በኋላ በግምት ግማሽ ሰዓት ገደማ ይቆዩና ብዙ ጥይት ይተኮሳል፡፡ ከእኛ ራቅ አድርገዉ ነዉ የሚረሽኗቸዉ፡፡ በቃ ሁሌም እንደ መልአከ ሞት ማታ ይጠሩሃል፣ ትሄዳለህ ጥይት ይተኮሳል ከወጣህ መመለስ የለም፡፡ በተገደሉት እስረኞች ምትክ አዲስ እስረኛ ይመጣል፡፡” ስትል በገሃነም እስር ቤት የነበረውን ሁኔታ ትገልጸዋለች።

ትህነግ ወልቃይት ጠገዴን ከያዘ በኋላ ለትህነግ እገዛ ሲያደርግ የነበረና በአካባቢው የተፈፀመውን ጭፍጨፋ ቆይቶ መረዳቱን የገለጸው የአካባቢው ተወላጅ ወንጀሉ የትህነግ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ይፈጸም እንደነበር ለጥናት ቡድኑ አስረድቷል።

“ከፋኝ” በሚል ለወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ማንነት ሲታገል የነበረውን ቡድን አመራሮች፣ አባላትና የቀድሞ የኢትዮጵያ ሰራዊት አባላትም በአካባቢው ታስረው በነበረበት ወቅት አቶ ስብሃት ነጋን ጨምሮ ከፍተኛ የትህነግ አመራሮች ትዕዛዝ ይሰጡ እንደነበር ለጥናት ቡድኑ እማኝነቱን ሰጥቷል።

የአካባቢው ተወላጅ በመሆኑ ወደ ድብቅ እስር ቤቶቹ እንደማያስጠጉት የገለጸው ግለሰብ አቶ ስብሃት በራዲዮ መገናኛ ስንት ሰው እንዳለ ጠይቆ ከ59 ሺህ በላይ ታሳሪ መኖሩን እንደተገለጸለትና አቶ ስብሃት ነጋም “ሬሽን የለንም፣ መረጃ ተቀብላችሁ ቶሎ ቶሎ አስወግዷቸው” ማለቱን እንደሚያስታውስ ለጎንደር ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድን ተናግሯል።

በወቅቱ ትህነግን ይደግፍ የነበር ሌላኛው ግለሰብ ሀምሌ 7 ቀን 1982 ዓ.ም. በአካባቢው የተፈፀመውን ጭፍጨፋ ለአብነት በመጥቀስ ለጥናት ቡድኑ እንደሚከተለው አስረድቷል።

“በቅርብ ርቀት በርካታ ጊዜ አውቶማቲክ ጥይት ተተኮሰ፡፡ ጨለማ ስለነበር ለማጣራት ጠጋ ብየ ቁጭ አልኩ፡፡ ባሩድ ይሸታል፣ የሚያወሩት ትግርኛ ነው፡፡ ህወሓቶች መሆናቸውን አረጋገጥኩ፡፡ መጀመሪያ የእርስ በርስ ጠብ መስሎኝ ነበር፡፡ ቀስ ብዬ ስጠጋ የተወሰኑት መሳሪያ ይዘው ቆመው ይታያሉ። ሌሎች ጉድጓድ አፈር ይሞላሉ፣ ፈርስና ባሩድ በጣም ይሸታል፡፡ በመጨረሻ ጉድጓዱን ከመሬቱ ጋር አስተካክለው በአፈር ጠቀጠቁት፡፡ ድንጋይ ስር ቁጭ ብዬ በጨለማ ጆሮየን ተክዬ የተወሰነውን አዳምጣለሁ። በትግርኛ ቋንቋ ‘አስማማው በለጠ 36 ራሱን ተሸኘ’ ሲል ሰማሁት፡፡ አስማማው ደግሞ በጣም ታዋቂ ጀግና እንደነበርና እንደወሰዱት አውቃለሁ፡፡”

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድን ለረዥም ጊዜ መረጃ ከሰበሰበ በኋላ ገሃነም በተባለ አካባቢ በሚገኙ በርካታ እስር ቤቶች ጭፍጨፋ ከተፈጸመባቸው መካከል የተወሰኑት ሃይማኖት አባቶች፣ የአካባቢው ነዋሪዎች፣ የሟች ቤተሰቦችና የአካባቢው ፀጥታ ኃላፊዎች በተገኙበት አፅማቸው እንዲወጣ ተደርጓል።

የጅምላ መቃብሮች በመቆፈር የወጣው የንጹሃን አፅም መጋቢት 21 ቀን 2014 ዓ.ም. አዲስ ዓለም ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተቀበረ ሲሆን በአካባቢው ካሉት በርካታ ድብቅ እስር ቤቶችና የጅምላ መቃብሮች በቀጣይ የበርካታ ንጹሃን አፅምን ለማውጣት እቅድ መያዙም ተገልጿል።

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድን “ገሃነም” በተሰኘው አካባቢ በነበሩት ድብቅ እስር ቤቶች የተፈፀመውን ጨምሮ በወልቃይት ጠገዴና ጠለምት ላይ የተፈፀመውን የዘር ፍጅት ወንጀል የሚያሳይ መረጃ አሰናድቶ ለማቅረብ በመሥራት ላይ መሆኑን ለማወቅ መቻሉን ከአማራ ክልል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

277763071 554950645986557 749060390060048453 n 277735898 554950589319896 5638510038011000627 n 277756566 554950485986573 1228023595519455087 n 277776591 554950385986583 6430084865183308316 n 277802335 554950329319922 9111577312663183746 n 277789138 554950275986594 3896099786546464774 n 277735339 554950229319932 277605160269301507 n 277793215 554950102653278 2483489065068821668 n

====

2 Comments

  1. ይሄን የተመለከተ ትግሬ ተከዜን አልፌ ልምጣ ይላል? አዲስ አበባስ የቀረ ትግሬ ይኖራል?

  2. ልብ እንበል። ወያኔ ማለት ገዳይ፤ ዘራፊ፤ ዘረኛ፤ ቂመኛ ማለት ነው። ለነጻነት ታገልኩ የሚለውን አክ እንትፍ በሉት። የትግራይ በረሃዎች ይመስክሩ ስንቶች በወያኔ እንደ ተረሸኑ። አሁን እንሆ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት ያለፈና የአሁን ግድያ አጽም እየተፈለፈለ መውጣቱ አባይን በጭልፋ እንዲሉ እንጂ ጉድ ብዙ ነው። ሰው የመኖር ጫና እያዳፋው ነገር እየተዘነጋ እንጂ ወያኔ በስልጣን ላይ እያለ በአዲስ አበባ ለመንገድ ሥራ የሚቆፍሩ አስከሬን ያገኛሉ። የተገኘው አስከሬን እጃቸው የታሰረና ለወታደር የታደለ የደብረ ብርሃን ብርድ ልብስ እንደለበሱ ነበር የተገደሉት። ወዲያው የወያኔ ታጣቂዎችና ወታደራዊ መሪዎች በመምጣት ሌላ ቦታ ወስደው እንደጣሏቸው በጊዜው ከፎቶ ግራፍ ጋር በግል ሚዲያዎችም ወጥቶ ነበር። እነዚያ ሟቾች እነማን ነበሩ? ፈልጎ ማመሳከር ነው። ሌላ ልጥቀስ ወያኔ አዲስ አበባ እንደገባ ሰሞን ካርቱምና ገዳሪፍ የነበሩ የድሮ የኢህአፓ አባሎችን በሱዳን ወታደሮች አስለቅሞ ወደ ሃገር በማምጣት እንደረሸናቸው የወያኔ ሰዎች ራሳቸው ነግረውናል። ወያኔ ከመግደልና ሰውን በዘር ከማበላላት በስተቀር ሌላ ቋሚ ሥራ አልነበረውም።
    በወልቃይት፤ በጠለምትና በጠገዴ የሆነው ደግሞ የዘር ማጽዳት ዘመቻ ነበር። ሴቶቻችሁንና መሬቱን እንጂ እናንተን አንፈልጋችሁም እየተባሉ ተለቅመው የተረሸኑ፤ በእስር ቤት ውስጥ በሰቆቃ የረገፉ እልፍ ናቸው። ዛሬ ትግራይ ላይ ጀኖሳይድ ሆነ የሚሉን የፓለቲካ ወስላቶች ጀኖ ሳይድ በወያኔ በትግራይ ህዝብ ላይ እየተፈጸመ እንደሆነ መናገር ይፈራሉ። ጥላቸው ከኢትዮጵያና ከኢትዪጵያዊነት ጋር ነውና። በመቀሌና በሌሎችም የትግራይ ከተሞችና ገጠሮች እንዳይናገር ታፍኖ በወያኔ ለተያዘው ህዝብ የሚያሰሙት ድምጽ የለም። ዛሬም ትላንትም ዘፈናቸውና ወሬአቸው አማራ ቋሚ ጠላታቸው እንደሆነ ነው። ያ ከሆነ ለምን የትግራይ ህዝብ ወደ አማራ ክልል ተሰደደ? ለምን ወደ ኦሮሚያ ክልል ውሰድን አላሉም? የሙት ፓለቲከኞች እውነትን ለማመን የማይችሉ የድባ ቅሎች ናቸው። የእነርሱ መፍረክረክ አይታያቸውም። ሁሌ የሚያጠፋው ሌላው ነው። የሚሞትላቸው የድሃው ልጅ ነው። ፓለቲካቸው የዘርና የጎሳ ብሎም ሃይማኖትን ያስታከከ ነው። ፎከታም ፓለቲካ ሁሌ እንደ ፎከተ ነው የሚኖረው። እልፈት የለውም። አንድ ጋ ሲሽርለት ሌላ ጋ ያመረቅዛል። አሁን ባለችው የሃበሻ ምድር ያለው የፓለቲካ እንዘጥ እንዘጥ ከዘመናት በፊት ሁሉ ከሆነው የከፋ ሰውን በሰውነቱ ሳይሆን በዘሩና በቋንቋው ከልሎ አንድን ከአንድ የሚያባላ ነው። ለዚህም ነው እንደ መራራ ጉዲና፤ እንደ በቀለ ገርባ ያሉት የእድሜ ልክ ፓለቲከኞች በቀራቸው ጊዜ ተመስገን ብሎ እንደመኖር አሁንም የፓለቲካ ፈረስ ላይ ተንቆናጠው በእርጅና ግልቢያውን የቀጠሉበት። ነገርየው ግን ቢታሰሩለት፤ ቢፈቱለት፤ በአደባባይ ቢንጫጩ ተልባ ቢንጫጫ በአንድ ሙቀጫ እንዲሉ ፍሬ አላመጣም። የማንም የፓለቲከኛ እይታ ዓለም አቀፋዊ ካልሆነ አቋሙ የተሽመደመደ፤ እይታው ሸውራራ ነው። ዛሬ በዪክሬን የተደረገውና የሚደረገው ግፍ ነጭ ከነጭ ጋር በመላተሙ አልቃሽ በዝቶለታል። በእውነት ወያኔ በአፋርና በአማራ ራሺያ በዪክሬን ላይ ካደረሰችው ግፍ ያልተናነሰ አልተፈጸመም? ግን የጥቁር ደም ለነጩ ወራጅ ውሃ ነው። ትላንትም ዛሬም ወደፊትም የዜናቸው ማሟያ እንጂ ሃዘኔታንና ድጋፍን አናገኝም። ይህ የማይገባቸውን የሃገራችን የዘር ፓለቲከኞችን በምን ዓይነት ሂሳብ ብናስረዳቸው ከዘር ፓለቲካ ተላቀው ሃገራዊና አህጉራዊ አልፎ ተርፎም አለም አቀፋዊ እይታ ይኖራቸው ይሆን? ዘረኞችን የሚፈውስ የባህልም ሆነ የፋርማሲ መድሃኒት የለም። እንደታመሙ ሌላውንም ለክፈውና አስለክፈው ወደ መቃብር ይወርዳሉ። ያን መኖር ከሆነ ድቢጥም ኑራለች። ትንኝም ታስንቃለች!
    በመዝጊያው ወያኔ በአማራ ህዝብ ላይ ያደረሰው በደል ሰማይ ጠቀስ ነው። ዛሬ ወያኔ በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገድ ዘርፎ ባወጣው የህዝብ ገንዘብ በአውሮፓ፤ በእስያ፤ በሰሜንና ደቡብ አሜሪካ፤ በአፍሪካ የተንጣለለ ቤት ገዝተው የሚኖሩና በንግድ ዓለም ተሳካልን ብለው እኛን እያሞኙ የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው። አሁን የኦሮሞው ማንህ ባለሳምንት ባለወረፋም በሃገር ውስጥ ቁልፍ የሥራ ቦታዎችን በመቆጣጠር ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ አይነት ሌላውን በማግለል ጮቤ እየረገጡ ይገኛሉ። ይህም አይሰምርም። በግፍ የተሰበሰበ ሃብት በላተኛውን ሌላ የተራበ ሲበላው ያከትማል። አይተናል። ታሪክ ሽንቁር ቀዳዳን አስፍቶ የሆነውን ጉድ ሁሉ በጊዜው የሚያሳይበት የራሱ የሆነ ስልት አለው። ግን እስከዛው ስንናኮር፤ ስንጋደል፤ የእኔ አውራ ጣት ከአንተ አውራ ጣት ይበልጣል ስንል ዘመንና ጊዜ ይሮጣል። የሞኝ ፓለቲካ እንደዛ ነው። ማጥ ውስጥ እንደገባ መኪና በተሽከረከሩ ቁጥር መስመጥ። አይጣል። አይ ፓለቲካ ድንቄም። አክ እንትፍ! በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Ertria
Previous Story

ኤርትራ በኢትዮጵያ ያላትን የዲፕሎማሲ ውክልና ከአምባሳደር ወደ ጉዳይ አስፈጻሚ ዝቅ አደረገች

rrerrrrg
Next Story

ጨው ኮርማን ጠለፈው!

Go toTop