የጠለምት የአማራ ማንነትና የወሰን ጥያቄ በሕዝብ ትግል እዉን ይሆናል – ከ ነጻነትና ፍትህ ለጠለምት አማራ የተሰጠ መግለጫ

ከ ነጻነትና ፍትህ ለጠለምት አማራ(Freedom and Justice For Telemt Amhara) የተሰጠ መግለጫ

የጠለምት ወረዳ  በጎንደር ክ/ሃገር በሰሜን አውራጃ በስተሰሜን ተከዜን ተሻግሮ አዲገብሩ (ትግራይ)፣ በስተምስራቅ አሁንም ተከዜን ተሻግሮ ተምቤን (ትግራይ) በስተምዕራብ ወልቃይትና በስተደቡብ የሰሜን ተራሮች የምትዋሰን ጥንታዊና ታሪካዊ ክልል ነች።

ጠለምት ከግራኝ መሃመድ ወረራ በፊት(ማለትም ከአስራ ስድስተኛው ክ/ዘመን ጀምሮ በአማራ ስር ስትተዳደር የቆየችና ሕዝባም የአማርኛ ተናጋሪና የአማራ ባህልና ወግ ያላት አገር ለመሆና የሚያሳዩ በርካታ ታሪካዊ ሰነዶች ያመላክታሉ። ለምሳሌ በጠለምት ወረዳ አብና በምትባል የገጠር መንደር አብና አቦ የሚባል ገዳም ከግራኝ መሃመድ ወረራ በፊት የነበረና በወረራው ወቅትም ገዳሙን እንዳቃጠለው የሚያሳዩ መረጃዎች በገዳሙ መነኮሳት ይገኛሉ። ይህ ብቻም አይደለም በኢትዮጵያ የታወቀው ከስምንት መቶ ዓመታት በላይ ያስቆጠረዉን ትልቁና ታሪካዊው የዋልድባ ገዳም የሚገኘዉም በዚሁ በጠለምት ወረዳ ነው።

ሆኖም ግን ትህነግ የጠለምትን ምንነትና ማንነት ሳያውቀው ቀርቶ ሳይሆን የመሬቱ ለምነትና አምራችነት ጠንቅቆ የሚያውቀው ስለሆነ በአጠቃላይ ክልሉን ከአማራ ክልል በጉልበትና በማናህሎኝበት በመንጠቅ ወደ ትግራይ እንዲካለል በማድረግ በርካታ የትግራይ ተወላጆ በአከባቢው እንዲሰፍሩ አድርጛል።

የአከባቢው ተወላጆችም በተወለዱበትና እትብታቸው በተቀበረበት ቀዬቸው እንደሁለተኛ ዜጋ እየታዩ መረታቸውና ንብረታቸውን በመቀማት ለችግር፣ ለመከራና ለስደት ተዳርገዋል፣ ማንነታቸውንና ንብረታቸዉን ለጠየቁ የአከባቢዉ ተወላጆችም እጣፈንታቸው ሞት፣ እስራት፣ ደብዛቸው የት እንዳሉ የማይታወቁ በጣም በርካቶች ናቸው። የአከባቢው ታዋቂና እድሜ ጠገብ የሆኑ አዛውንቶችም ታሪክን ለማጥፋት ሲባል ተገድለዋል  ደብዛቸውም ጠፍታል።

ሕዝባችን ከ1972 ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁኑ ሰአት ድረስ ከፋሽቱ የትህነግ ወያኔ ወራሪ ሃይል ጋር በመፋለም ዕርስቱን ላለማስነጠቅና ዘሩን ከፈፅሞ ጥፋት ለማዳን ያልከፈለው የመስዋዕትነት አይነት የለም። ይልቁንም ህዝባችን የትህነግን ፀረ-ኢትዮጵያና ፀረ-አማራ አላማና ተልዕኮ ለማክሸፋ ከጅምሩ ነፍጥ አንስቶ የታገለና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህን ፋሽስት ቡድን በአንድነት ቆሞ እንዲታገለውና ከምደረ-ገፅ እንዲያስወግደው አጥብቆ ያሳሰበና በመረጃና በማስረጃ አስደግፎ ሲያጋልጥ ኖሯል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “የተፈፀሙ ወንጀሎች ነጥረው ስለወጡ፣ እውነታ ስለታወቀና ተፃራሪ ቡድኖች እጅ ለእጅ ስለተጨባበጡ ብቻ እርቅና ሰላም አይመጣም። “

ከሁሉም በላይ፣ የጠለምት ሕዝብ ትግል ምንም እንኳን ከጅምሩ በአያሌ መስዋዕትንቶችና ስቃዮች የታጀበ ቢሆንም የትህነግን አምባገነናዊ ስርዓት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ተነቅሎ ወደ መቀሌ እንዲፈረጥጥና ዛሬ በጣረሞት ውስጥ ሆኖ አይቀሬ ታሪካዊ ሞቱን ይጠባበቅ ዘንድ ያስገደደ የኢትዮጵያውያን ባለውለታ ሕዝባዊ ትግል ነው።

የጠለምት ሕዝብ ከ20 ዓመታት በላይ የትህነግን ፋሽታዊ ተግባራት በይፋ በማጋለጥና በጠለምት፣ በወልቃይትና ጠገዴ፣ ወገኖቻችን ላይ ያካሄደውን የመሬት ወረራና የፈፀመውን የዘር ማፅዳት ወንጀል ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም ማህበረሰብ በማጋለጥ ሲታገልና ሕዝባችንንም ሲያታግል ከመቆየቱ አንፃር የትህነግን ፋሺስታዊ መሪዎች እንቅስቃሴና ሴራ በመረዳትና በመተንተን ከሁሉም የተሻለ አቅም ፈጥሯል ብለን እናምናለን።

ይሁን እንጂ ትህነግ መቀበሪያውንና ወደ መቃበሩ ይዞት የሚወርደው አሟሟች እያዘጋጀ መሆኑን ተረድተናል። ከረጅም አመታት ጀምረን እንዳሳሰብነው ትህነግ ሞቱ ካልቀረለት አጥፋቶ ከመጥፋት እንደማይመለስና ለዚህም እኩይ ፍላጎቱ ጠለምት መጥፋት ካለባቸው አከባቢዎች አንደኛ ኢላማው እንደሆነችና አማሟቾቹም ሰላማዊ የጥልምት ልጆች እንዲሆኑ አበክሮ እየሰራ እንደሆነ የሰሞኑ መፈራገጥ ጥሩ ማሳያ ነው።

አሁን ባለን ተጨባጭ መረጃ መሰረት ትህነግ በርካታ የትግራይ ልዩ ሃይል  ራሱን የትግራይ ክልል ነው ብሎ የሚጠራዉን በማይጠብሪ ከተማ በማስፈር ለከፍተኛ ጦርነት እየተዘጋጀ መሆኑን ደርሰንበታል። የአከባቢው ሕዝብም በአሁን የእርሻ ወቅት እርሻዉን ትቶ የጦር መሳርያ እንዲታጠቁ በማድረግ  በዚህ ጦርነት እንዲሳተፍና ከራሱ ወገን ለሆነው ከአማራው ጋር እርስበራሱ ለማጨራረስ ጫና ከመፍጠራቸውም  ባሻገር በሕብረተሰቡ ዘንድ አመኔታ ባለመኖራቸው የሚጠረጥሩትን ሰው ትጥቅ እያስፈቱ ለእስር እየዳረጉት ይገኛሉ።

ትህነግ የስልጣን እድሜዉን ላማራዘምና በህዝብ ትግል ያጣዉን ቤተመንግስት ከተቻለ መልሶ ለመቆጣጠር ካልቻለም እርሱ የማያስተዳድርታ ኢትዮጵያን ባለው እኩይና አጥፊ ዓላማ የተነሳ የሚነዛው ሃሰተኛ ወሬ መሰረቱ ይሄው ከድርጅቱ ጥንሥስ ጀምሮ የተጠናወተው የአጥፊነትና የዘረኝነት በሽታ ከመተግበሩ በፊት ትህነግን የመቅበር ስራ የፌደራል መንግስቱ ስራ ከመሆኑ አንጻር የአማራ ክልላዊ መንግስት ከሕዝብ ጋር በመተባበርና በማስተባበር ከላይ የአቀረብነው መረጃ ታሳቢ በማድረግ በሕዝባችንና በአገራችን ላይ የከፋና አሰቃቂ እልቂት ከመድረሱ በፊት አስቀድሞ የመከላከል እርምጃ እንዲወስድና ህዝባችንም ከወዲሁ ተገቢ መረጃ እንዲደርሰው እንዲደርገ በሕዝባችን ሕዝብ ስም እንማጸናለን።

በመላው ዓለም ለምትገኙ የጠለምት:-  ወልቃይት፣ ጠገዴና ራያ  ተወላጆች በሙሉ፦ ሁላችንም እንደምናውቀው ከ 1972 ዓ/ም ጀምሮ በሃይል፣ ያለሕዝብ ይሁንታና ፈቃድ ወደትግራይ በመካለላቸው ምክንያት ያለማንነታቸው ማንነት ያለቓንቓቸው ትግርኛ ቓንቓ እንዲናገሩና እንዲማሩ፣ ተወልደው ባደጉበታና በአያት ቅድመ-አያት ሃገራቸው እንደሁለተኛ ዜጋ ትቆጥረው መሬታቸውን ተቀምተው ለትግራይ ሰፋሪዎች በመሰጠታቸው ምክንያት ለድህነትና ለስደት የተዳረጉት የአከባቢው ተወላጆች ቁጥር እጅግ በጣም በርካታ ከመሆናቸዉም ባሻገር በትውልድ ቀያቸው መኖር አይበሉትና በሚኖሩት የአከባቢው ተወላጆች ላይ ይህ ነው የማይባል ግፍ፣ ሰቆቃ፣ ጥላቻና አግላይነት ላለፉት 30 ዓመታት ሲያስተናግዱ መቆየታቸዉን እንኻንና ኢትዮጵያዊ ዜጋ ይቅርና የአለም ማህበረሰብ የሚያውቀው ሃቅ ነው።

ስለሆነም በትህነግ አምባገነናዊ አገዛዝ ምክንያት  ላለፉት 30 ዓመታት በሕዝባችን ላይ የደረሰዉንና እየደረሰ ያለዉን ሰቆቃ፣ ግድያ፣ እስራትና ስደት እየተመለከቱ ማለፍ በሞራልም በታሪክም የሚያስጠይቅ መሆኑን በመገንዘብ እየደረሰበት ያለዉን ግፍና መከራ ለመታደግ ይቻል ዘንድ የጠለምት የማንነትና አስመላሽ ኮሚቴ  በሚል ስያሜ ተደራጅተን ይሄው ላለፉት አራት አመታት አቅማችን በፈቀደ መንገድ በሃገር ቤት በአማራው ክልላዊ መግስት እውቅና አጊንተን እየተንቀሳቀስን ስንሆን በዉጭ ሃገራትም በሰሜን አመሪካ፣ አውሮፓና አውስትራሊያ የድጋፍ ኮሚቴ በማቓቓም የዉጩንና የውስጡን ኮሚቴዎች በመቀናጀትና በመናበብ አመርቂ ስራዎችን እየሰራን እንገኛለን።

በመሆኑም በሃገር ቤትና በዉጭ ሃገር የምትኖሩ የጠለምት አማራ ተወላጅ ደጋፊዎቻችን ወቅታዊዉን የሃገራችን ተጨባጭ ሁኔታ በትኩረትና በአንክሮ በመከታተል ከዚህ ቀደም ስታደርጉት የነበረዉን የንዋይና የሞራል ድጋፍ  እጅግ በጣም እያመሰግን ቀጣይ  ድጋፋችሁን ለወሳኝ መዕራፍ አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉበት ወገናዊ ጥሪያችንን እያቀርብን፣ በሰሜን አመሪካ፣ በአውሮፓና በአውስትራልያ የተቓቓመዉን የድጋፍ አስተባባሪ ኮሚቴ ጎን በመሆን አስፈላጊዉን ድጋፍ እንድታደርጉልን በስቃይና በመከራ ዉስጥ ባለው የጠለምት ሕዝብ ስም ጥሪ እናቀርባለን።

ለትጋራይ ሕዝብ፡-  የአማራ ሕዝብ ለረጅም አመታት ተደጋጋሚ ጥሪዎች ሲያቀርብ ኖራል።  ዛሬ የተፈጠረው ሁሉ እንዳይሆን አስቀድመን አሳስበን ነበር።  ዛሬም እንደትናንቱ ማሳሰብ የምንወደው ነገር ቢኖር በስምህ የሚነግደው ለፋሺስቶች ትህነግ መሪዎች እድሜ ማራዘሚያና መደበቂያ ሲባል ለዘመናት በፍቅር፣ በአብሮነትና በመከባበር አብሮህ ከኖረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሊነጥልህና ሊያዳማህ የሚያደርገዉን ማነኛዉም እንቅስቃሴ በማክሸፍ የታሪክ ሃላፊነትህን እንድትወጣ ወገናዊ ጥሪ እናቀርባለን።

 ነጻነትና ፍትህ ለጠለምት አማራ(Freedom and Justice For Telemt Amhara) የተሰጠ መግለጫ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share