የሀገርና ወገን አድን ክተት ጥሪ ክፍል ፭ – ቅድመ ምርጫ የኢትዮጵያ መንግስት አዋላጅ ካውንስል ስለመመስረት- ከአባዊርቱ

መንደርደርያ!
መከላከያ የኢትዮጵያ መንግስት  አዋላጅ ቤተሙከራ ስለመሆኑ
በመጀመርያ እዚህ የማቀርበው ከፋፋዮች  በፀሎት የሚጠብቁትን የደቦ ሽግግር መንግስት ሳይሆን በይዘቱም ይሁን አይነቱ ከጥንቱ ደርግ ለየት ያለውን አዲሱን የኢትዮጵያዊነትን አዋላጅ ካውንስል ከራሱ ከመንግስት አብራክ  ስለሆነ  ሳትደነብሩ በፅሞና እንድትከታተሉኝ በትህትና አሳስባለሁ። ይህ መልእክት በተለየ የአገራችሁ ሁኔታ እንቅልፍ ለነሳችሁ ሲሆን በተለየ መንገድ ለ ዶር አቢይ፣ የጦር ጄኔራሎች፣ ክብርት ፕሬዚደንትና ተቃዋሚም ሆናችሁ የኢትዮጵያ ጉዳይ ፖለቲካውን ለግል የስራ እድል የማታዩ ይሁንልኝ ። በበኩሌ ባወጣው ባወርደው የዘንድሮው ምርጫ ምኑም ስላላማረኝ ነውና ታርጋ ሳትለጥፉ ተከታተሉኝማ!
ለምን ከመከላከያ የተዳቀለ የአዋላጅ ካውንስል አስፈለገ?
እንደምታውቁት ኢትዮጵያዊነት ከተቀበረበት ብቅ እያለ ያለው በዚህ ድንቅ አቢይ የሁለት አመት ፕሮጀክት ስለመሆኑ የናቡከደነፆርን የመሰለውን የፅልመት ሰራዊት በ ሶስት ሳምንታት ከመታ በሁዋላ ነው። ይሰመርበት። የጄኔራል ባጫን ግስላነት ያየ፣ የጄኔራል አበባውንና ብርሀኑ ጁላን የቁጭት ፊት ለተመለከተ ጥንት በኮርያና ኮንጎ የኢትዮጵያን መከላከያ ሰራዊት በአለም ፊት ያቀረቡትን ገፅታ በምናብም ቢሆን አለመቃኘት አይቻለንም!
ወገኖች!
ያለንበት በጣም ከባድ ዘመን ነው። የኢትዮጵያ ጠላቶች የውጭዎቹን ድሮም እናውቃለን። በአይምሮም ስንዘጋጅላቸው ኖረናል። አሁን እኮ የመጣብን ጉድ ከባድ ነው። 40 አመታት ከውስጥ እንደ ምስጥ ስንሰረሰር ነው የኖርነው። ህዝቡ በመተከልና በማይካድራ ያለውን እልቂት ነው የሚያየው፣ ኢትዮጵያዊንት ለብዙ አስርተአመታት እንዲህ ተሸርሽሮ እልቂቱ በአራቱም ማእዘን እንደ ሩዋንዳው አለመሆኑ ፈጣሪን በመጀመርያ እናመስግን። የኢትዮጵያዊነት ረመጥ እንዲህ በቀላሉ ፅልመት እንደተመኘልን  የሚከስም ባለመሆኑና ዶር አቢይ በዚች ሁለት አመታት መከላከያውን በኢትዮጵያዊነት ጃኖ ፈጥኖ በማልበሱ ነው። ቀላል ስራ አይመስለኝም ይህ ጉዳይ። ምድረ የ ዩቱብ ቀላዋጭ ነገርዬውን ቢያጣጥለውም ለኔ እጅግ ከባድ የብቃት መገለጫ ነው። ስለሆነም፣
፩) በአስቸኩዋይ የሽግግር ካውንስል የሚከተሉትን ያካተተ ይመስረት
ሀ) የጦር ሹማምንት ጄ ብርሀኑን ያካተተ (ምርጫውን ለዶር አቢይ) – አራቱ እንቁ ጄኔራሎች በቂ ናቸው ፣ አምስት ከኮለኔል አቢይ ጋር እንደኔ።
ለ) የ አስሩም ክልሎች ተጠሪዎች (አሁን ያሉት የክልል መሪዎች ሊሆኑም ላይሆኑም ይችላሉ። ከሆኑ የዖሮምያንና የቤንሻንጉሉን በቴክኖክራቶች መወከል) በንኡስ ካውንስል አካቶ ለዋናው ካውንስል ተጠሪ ማድረግ
የካውንስሉ የበላይ አስተባባሪ ፕሬዚደንቱዋ ይሆናሉ
የካውንስሉ ስልጣንና እቅድ!
በመጀመርያ መቼውንስ ይህን ለማድረግ ፓርላማው war powers act አያጣምና ማንዴቱን ከዚህ ይወስዳል ከሚል ነው። ከሌለውም ይፍጠር አዲስ ህግ ። ይህው ነው። ጦርነት ላይ እኮ ነን። ከወያኔ ርዝራዥ፣ ኮሮና፣ ድህነት፣ ረሀብና ቸነፈር።
ይህ ካውንስል ንኡሳን ካውንስሎች ይኖሩታል። ከነዚህም እንደኔ ምኞት የሚከተሉት አስቸኩዋይ ናቸው።
፩) የዳያስፖራ ሊቃውንት አሰባሳቢ ኮሚቴ።
በአለም ላይ የፈረንጆቹን አገር ኢኮኖሚ በመደጎምም ይሁን መጠገን፣በህክምና ይሁን ሳይንስ ፣ በማህበራዊ ይሁን ሶሻል እጅግ ብቃት ያለው ወገንን ሀርቨስት ማድረጊያው ዘመን አሁን ነው። ከዚህ በላይ ውድቀት፣ ድቀትና ውርደት ከዬት ይምጣ?  የአፍሪካና ካሪቢያንን አገሮች የዲፕለመሲ ሀሁ እንዳላስተማርን ዛሬ እነ ስዩም መስፍን ለ 40 አመታት ምን ሲያቦካሉን እንደኖሩ ገና በምርምር የምንደርስበት ነው። ያንገበግባል። በሰው ሀይልና አይምሮ ታድለን እንደምን እንደዚህ እንዘክረክ? ይህ ምርጫ ሲደላን ይደርሳል። ገና ብዙ የጎደፈውን ማስተካከል ይኖርብናል ። ሲጀመር ምርጫው ለማን ነው? ለፖለቲሻንስ ስራ መቅጠርያ ካልሆነ በቀር ለደሀው ከሆነ በኢትዮጵያ አምላክ አቆዩት። ብዙ ይቀረናልና።ምርጫውን ደግሞ እጅግ ከተፈለገ  ተቃዋሚውን በየሙያው መቅጠር። ለምሳሌ ዶር ብርሀኑ ብቃት ያለው ሰው ነው በኢኮኖሚው መማክርት ጉባኤ ቢሳተፍና ቢያስተባብርልን።  ባለፈው በቪኦኤ እንደሰማሁት በጃንሆፕኪንስ ያሉ ብርቅዬ ዶክተሮች ደግሞ የጤናውን፣ በናሳና መሳሰሉት የሳይንሱና ምርምሩን። እስቲ አስቡት ያሉንን ሊቃውንት ብዛታቸውና ጥራታቸውን። አለመታደል ሆኖ ብንበታተንም በየቤቱ ስለኢትዮጵያ ጉዳይ የማይነዝረው የለም። በተለይ እነዚህ ሙዋርተኞች ሳይመጡ በፊት የወጣው ህዝብ። ከመጡም በሁዋላ ከተወለዱት እጅግ ከፍ ያለ የአገር ፍቅር አለ። መንገድ መሪና ቅን ሮልሞዴሎችን ብቻ ነው የምንፈልገው። ዶር አቢይ እኮ ከነዚሁ  ጉያ ነው የፈለቀው በፈጣሪ ቸርነት።
፪) የውጭ ዲፕለማሲና አባይ ጉዳይ ኮሚቴ
በጡረታም ይሁን በእድሜ ከአገራቸውና ህዝባቸው ርቀው የሚገኙ ብዙ ሊቃውንት አሉን። በምልጃም ይሁን አዋጅ ባስቸኩዋይ መሰብሰብና ማማከር። ብዙ መፍትሄ የሚያፈልቁ ንፁህ ወገኖች አሉን። እነ  ሻለቃ ዳዊት እጅግ አፍሬቦታለሁ። የኢትዮጵያ አምላክ ይፈርዳል። የዛሬ ሁለት አመት ለርሶና ለኮለኔል ጎሹ እባካችሁ ይህን ወጣት አቢይ እርዱልን ብዬ ያልኩበትን በፀፀት አስታወስኩ። አገሩን የሚወድ ቆፍጣና መኮንን አድርጌ ነበር የማዮት። አዝናለሁ። ክህሎት ቅንነትን ካልተላበሰ አለማወቅ ይመረጣል።  እውነት አቢይ አህመድ እርሶ እንደሚያስቡት በኢትዮጵያ ላይ ወይም ወደርሶ ልውረድና በአማራው ላይ መሰሪ ነገር ያስባል? ሳያውቁት የራስዎኑ መሰሪነት ለአለም መሰከሩት። ያሳዝናል። ክህሎቶንና የስራ ልምዶን በዚች ባለቀች ሰአት እንኩዋ ለበጎ ቢያውሉት ታሪክ እንዴት በዘከሮት ነበር ከግል ዝናና አጉል ፉክክር ። ይቅርታ ። ፍሬነገሩ ብዙ ጠበብት አሉን ለማለት ነው። በማስታወቂያ መሰብሰብ ብቻ ነው። የአባይ ጉዳይ የውጭው ገበናችን ዋናው ጉዳይ ነው። የጠላቶቻችን  ብዛትና ጥራት መለክያ ባሮሜትር አባይ ነው። ለካውንስሉ ተጠሪ የሆነ ከባድ በጀት ያለው የንኡሳን ካውንስል ሁሉ አለቃ የሆነ ነው መሆን ያለበት። ወያኔ ስንት የማናውቀውን ገና በለቀማ የማንደርስበትን የውጭ ፈንጅ የቀበረልን በዚሁ የአባይ ቤዚን ጉዳይ መሆኑን ማሰብ ከባድ አይደለም። ይህን ለማወቅ አንድ መሰሪ የፅልመት ሎሌ የውጭ ጉዳይ ተጠሪ ለስንት አመታት የውጭው ገበናችን ሸፋኝ ሆኖ እንደኖረ ብቻ አስቡትና ማይካድራ ይሁን መተከልላይ ከታረዱት ንፁሀን አስተያዩት። እንግዲህ የትህነግ አንጋቾች የማይካድራን እጅግ ደሀ ወገኖች በንድያ አይነት ጭካኔ ከበለቱ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ከውጭ ጠላቶች ተመሳጥረው ለብዙ አስርተአመታት እንዴት ሲበልቱ እንደኖሩ መገመት አይከብድም። እነዚህ ሰዎች የኢትዮጵያን ማህተም በእጃቸው ለ ሰላሳ አመታት አድርገው ብዙ ጉድ ሰርተውናልና ግድ የላችሁም ምርጫው ይቆየን። ኢትዮጵያን በእግሩዋ በትክክል ካቆምን በሁዋላ ይደርሳል።  እስቲ በመጀመርያ የውጭ ተጠሪዎቻችንን ኢትዮጵያን በሚሸቱ ዲፕሎማቶች፣ የግል ካዝናና ዝናን ሳይሆን የኢትዮጵያንና ህዝባችንን ካዝናና ፍላጎት በሚያንፀባርቁ ዲፕሎማቶች እንሙላ። ሁሉ ይደረስበታል።
፫) የ inter-regional affairs ኮሚቴ
ይህ ደግሞ ክልሎችን የሚያቀናጅ ሆኖ ቀስ እያለ ነገ ለምንፈጥረው ሀቀኛው ዴሞክራሲያዊ ፌዴራል አስተዳደር፣ በቁዋንቁዋ ሳይሆን በሪጅን ላይ የተመሰረተ ጥርግያ መንገድ ከፋች ይሆናል። እንደኔ ምርጫ የጥንቱ አስራአራቱ ጠቅላይ ግዛቶች ወይም ክፍለ ሀገሮች በዴሞክራስያዊ ምርጫ ከሆኑ ምንም ጉድለት የለባቸውም። እንደ ድህነታችንም ቢሆን አስር ሺህ ዞንና ቅብጥርሴ ብለን ከመሸንሸን 14 /15 ሪጅን ሆነን በዘርና ጎሳ ሳይሆን በተፈጥሮ አቀማመጥና ጉርብትና ቢሆን እንዴት ባማረ። በንጉሱና ደርግ  ጊዜ የነበሩትን ጠቅላይ ግዛቶች/ ክፍላተሀገሮች ማዘመን ብቻ ነው። እነዚህ ነቀርሳዎች የተከሉብንን የጎጥ ወህኒቤቶች በሂደት ለመቅበር የሚያገለግል ኮሚቴም ይሆናል። ሌላው ዋናው የዚህ ኮሚቴ ስራ የየክልሉን ልዩ ሀይል በአንድ መከላከያ እዝ ስር ማድረግ ይሆናል። ባለፈው ዶር አቢይ ፓርላማው ላይ ከተናገሩትና እስካሁን ሲገርመኝ የሰነበተውና ብዙ ሰው ያላስተዋለው ጉዳይ አለ። መከላከያ ለመቀጠር ያለው ፍላጎት እጅግ አናሳ መሆኑና ባለፉት ሶስት አመታት ከባድ ቻሌንጅ እንደነበረባቸው ነው። እንግዲህ ይህን የሚሉን እልፍ አእላፍ የፌስቡክና ዩቱብ ምፅዋተኛ እምቢ ላገሬ እያለ በሚያቅራራበት ዘመን ነው። እጅግ ልብ ሰባሪና አሳፋሪ ነው። ተጋፍጦ ለኢትዮጵያ መድማትና በአፍ ማድማት ለየቅል መሆናቸውም አይደል? ይህ ሁሉ ሚሊዮን ወጣት በሚርመሰመስበት ሀገር ይህ መሆኑ ከባድ ስራ እንደሚጠብቀን ያመላክታል።
፬) የሲቪክ ማህበራትና ነፃ ጋዜጦች አጎልባች ኮሚቴ
ይህ እጅግ ወሳኝ ነው። ሀላፊነት የሚሰማቸው፣ በአገር ፍቅር የነደዱ ነፃ የሚድያ ሰዎችን፣ የኪነትና  ስነመፅሄት ፈላስፋዎችን ። የመምህራንና ብሎገሮች የመሳሰሉትን መደገፍ፣ ማጎልበትና ሽፋን መስጠት። በዚህ አጋጣሚ አንድ ቆፍጣና ስዩም ተሾመንና ዶር ዳኛቸውን መጥቀስ በቂ ነው። ስዩም ተሾመ የሚፈልገውን latest technology ዳያስፖራው መዋጮ አርጎለት ቢያስታጥቀው እራሱን የቻለ የማይደረመስ ብርጌድ ነው። ሌላው ዶር ዳኛቸው ነው። ቢናገር፣ ቢያስረዳ  ድንቅ ኢንሳይክሎፒድያ ነው። እነዚህን ድንቅ ወገኖች መንከባከብና የፈለጉትን እያቀረቡ ኢትዮጵያችንን መገንባት። ለምን? ቁርጡን ነዋ የሚነግሩን። ለማንም ተጠሪ አይደሉም ለህሊናቸው እንጅ ። ብዙ አሉ እንደነሱ የማናውቃቸው የማያውቁን። ስለኢትዮጵያ ብለን ማጎልበትና ማሳደግ የግድ ነው። መንግስት ከመንገድ ሲወጣ፣ ወይም  ሊቀላምድ ከፈለገና ከመስመር ሊወጣ ሲል ቶሎ ወደ መስመር የሚመልስ ኃይልም ይሆነናል።  ይህ ኮሚቴ በግል አገርወዳዶች የሚደገፍ ይሆናል።
ማጠቃለያ!
የችግራችን መጀመርያ በወያኔ መቃብር ላይ ስለተመሰረተ ይህ አዲስ ስትራክቸር ነገ ለምንፈጥረው ዴሞክራሲ መንገድ ጠራጊ ይሆናል። የኮረናን ጉዳይ ይዘን፣ በየክልሉ እየፈነዳ ያለውን ለ አርባ አመታት ሲቀበር የኖረን ፈንጅ እየለቀምን፣ ትኩስ እሬሳና አፅም ከየክልሉ እየለቀምን፣ በንግድ፣ ትራንስፖርት ፣ ባንኪንግ ፋይናንስና ምግብ አቅርቦት እንዲህ እየታመስን የፖለቲካውን ምርጫ በዚህ አመት ማድረግ ማንን ለማስደሰት ነው? ጥግ ይዘው አድፍጠው ወንጀለኞች ይፈቱልን ብለው ለሚያላዝኑት  ጡረተኞች ? ወይስ  አነጋገርና አለባበስ እያሳመሩ የሚወጣጠሩ ጭራሽ ባለውለታውን፣ ሚስትና ልጆቹን እንደጥገት ቤት አሳስሮ ፈገግ እያለ በመላ ሊያሻግረን ህይወቱን ሁሉ ሊገብር የነበረን ስውዬ በአደባባይ ክዶ ይውረድ የሚለውን?  ወይስ በኑሮ ውድነት የባቄልንና በቆሎን  በጀት እንኩዋ ያልቻለውን ደሀውን ወገናችንን? በኔ በኩል አምናም አልታየኝም፣ ዘንድሮም አይታየኝም። ይህ ምርጫ በትንሹ ለ 2 አመታት ተራዝሞ በጊዜያዊ ካውንስል  አገሪቱዋ በ war powers act decree ብትስተዳደር ከገባንበት ማጥ እንወጣለን ብዬ አስባለሁ።
ድንገት ለ ኢንተርናሽናሉ ኮሙኒቲ ፍጆታ የውስጥ መስመር ማስፈራርያ ካለ የሽግግር መንግስት በኢትዮጵያችን ቅላፄ መስርተናል ማለት ነው።  ከላይ እንዳልኩት በቴክኖክራቶች ብንሞላውና አዲስ ብቃት ያለው ውቅር ብናቀርብ እነሱም አይደፍሩንም። ለምን? ተሰሚነታችን ከፍ ይላላ። አሁን እኮ አንድ አቢይ፣ ደመቀና ሙስጠፌ ብቻ ናቸው እኮ (ከይቅርታ ጋር)። በዚህ አጋጣሚ የሙስጠፌን ብዙ ብያለሁ፣ በአቶ ደመቀ ዝምታ ውስጥ ያለው ረቂቅ ክህሎት ያስደምማል። የሚያሳስበኝ ብቻቸውን ናቸው የሚለው ነው። ይህ አዲስ ስትራክቸር ብቻ እንዳይሆኑ ደጀን የሚሆን መውጫ መንገድ ይመስለኛል።
ልኡል እግዚአብሄር አገራችንና ህዝባችንን በምህረቱ ይጎብኝልን!!
ተጨማሪ ያንብቡ:  የተምቤን ስብሰባችን ጉድ አደረገን (አብርሃ ደስታ)

2 Comments

  1. ወገኔ አባ ዊርቱ፣
    እጅግ በጣም የማከብርህ ፍጹም ኢትዮጵያዊ ነህ። አስተያየትህ እጅግ አርኪ እና ገንቢ ነው።
    እኔም ምርጫን በተመለከተ ያለኝን አቋም ላጋራ።
    አገሮች ያደጉት በ አምባገነን መሪዎች ነው እንጂ በ ምርጫ በመጡ አጭበርባሪ ፖለቲከኞች አይደለም። ቱርክ፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ጀርመኒ እና ሲንጋፖር ሊጠቀሱ ይችላል።
    ኢትዮጵያ አሁንም ወደፊትም በ ምርጫ መንግሥት መመሥረት አለባት ብዬ አላምንም። እኔ በ ኬንያ፣ እንግሊዝ፣ አሜሪካ እና ካናዳ ምርጫ ሲካሄድ አይቻለሁ። ፉክክራቸው በ አብዛኛው ለ ግል ጥቅም እንጂ ለ ዜጎች በ ማሰብ አይደለም። ቢመረጡም ለ አንድ ወገን ብቻ ነው እንጂ ለ መላ ዜጎች አይደለም። ስለዚህ ለ አገር የሚጠቅም መሪ ፍትሃዊ ሊሆን የሚችለው አገር ወዳድ ከሆነ እና ለማንም ተያዝ ካልሆነ ብቻ ነው። ስለዚህ የጠቀስካቸው የ ጦር መኮንኖች የ ኢትዮጵያ መሪ ቢሆኑ በ አገራችን የሰፈነው መገዳደል ሊቆም ይችላል።
    ለ እንደኛ አገር የሚያስፈልገው ያለው መሪ ትክክለኛ ሥራ እንዲሠራ ፖሊሲውን እንዲያስተካክል ተጽዕኖ ማድረግ ነው። ፓርቲዎች ከፋፋዮች እንጂ አገር ገንቢ ስላልሆኑ አያስፈልጉም። በ አላቸው ቀና አቋም የሚከበሩ ሰዎችን ሰይሞ እንዲመሩ ማድረግም አንድ አማራጭ ነው።

  2. ወያኔ የተከለብንን የብሄርተኛ ስርአትን ይዘን የተሻለ ውጤት በምርጫ እናገኛለን ማለት Einstein’ እንዳለው ” Insanity is doing the same thing. Over and over and expecting different results ” ነው የሚሆንብን። ትናንት በትግራይ ያየነው ነገ በኦሮሚያ ወይም በቤኒ ሻንጉል ላለመደገሙ ዋስትና የለም። የምናያቸው ምልክቶችም ወያኔዊዉነትን ለማስቀጠል አለን አለን የሚሉ ከገቢራቸው እያየን ነው። ምርጫው ቢካሃድ ልዝብ ብሄርተኞቹ ወጥተው አክራሪዎቹ ወደ ስልጣን እንደሚመጡ ጥርጥር የለኝም። የሸኔ አባላት፣ የዳውድ ኢብሳ ጀሌዌች፣የጃዋር እና የበቀለ ገርባ ግርፎች፣ የሌሎችም ክልል አክራሪ ብሄርተኞች እንደተባለው በምርጫም ሆነ በጡጫ የመንግስት ስልጣን መጨበጣቸው አይቀሬ ነው። ታዲያ እነኝህ ናቸው እንድሀገር የሚገነቡት ?? ዲሞክራሲያዊ የሆነ፣ ዜጎችን በእኩልነት የሚያስተዳድር ህገ መንግስት የሚያወጡት ? የማይታሰብ ነው። የሚገርመው በየክልሉ ያሉ በብዙ ሚሊዬኖች የሚቆጠሩ ከከሌ ክልል የመጡ ዜጎች ፣እና በተወለዱበት ክልል majority/largest population ሆነው የመ መረጥ መስረታዊ መብታቸው ባልተከበረበት / አማራን በቤኒ ሻንጉል ልብ ይሉአል/ ሁኔታ ምርጫው ምን ፍታዊነት ይኖረዋል የወያኔን ድራማ ከመድገም ውጭ ? ቢያነስ በነኚህ Imperfections. እርምት ሊደረግባቸው በተገባ ነበር። Alas..
    ሀገራችን ባለችበት አሁናዊ ሁኔታ ሀገራችንን ሉአላዊነት እና አንድነቱዋን አስጠብቆ ሊያስኬድ የሚችል ሀይል በፓለቲካው መሪነት ያሉት ሳይሆኑ በአብይ መሪነት የመከላከያ ሀይላችን መሆኑ በተግባር አስመስክሮአል ። የሀገራችን እንድነት ለሰራዊታችን በቀጥታ ከህልውናው ጋር ስለሚያስተሳስረው ነው።
    ስለዚህ ሀገራችን ሳትበተን፣ከፍርስራሽ ቃራሚዎች ሲሳይ ሳትሆን በአንድነቱዋ እንድትቀጥል የምንፈልግ ሁሉ የወያኔን legacies አንድ ባንድ ነቅሰን ነቅለን፣ መፃዊ እንድላችንን በተመለከተ በሚወጣው ትልም/ road map / የመከላከያ ሀይላችን ሙሉ ተሳትፎ እንዲኖረው ማድረግ ይኖርብናል።
    God bless Ethiopia!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share