ለኢትዮጵያ ባለስልጣናትና ፖለቲከኞች ሁሉ ለራሳችሁ ስትሉ ተለመኑ – ሠርፀ ደስታ  

ዛሬ በወያኔ የሆነው ሁሉ እንደሚሆን ጤነኛ አእምሮ ያለው ሊያስበው በተገባ ነበር፡፡ ለወያኔም ሆን አሁን ስልጣን ላይ ላላችሁት አንድ ጥሩ የሚባል እድል የዛሬ ሁለት ዓመት ከግማሽ ለውጥ በተባለ ጊዜ ገጥሟችሁ ነበር፡፡ ወያኔዎች ምን ዓልባት ጥቂት የሚባሉ አባሎቻቸው በፊት በፈጸሙት ወንጀል ቢጠየቁ እንጂ አብዛኞቹ ዛሬ በለውጥ አራማጅነት ሥልጣን ላይ ካሉት የተለየ የሚጠየቁበት ነገር ላይኖር ይችል ነበር፡፡ በእርግጥም ብዙዎቹ የወያኔም አባላት በለወጡ አባልነት ጀምረው ነበር፡፡ ነገሩ ሁሉ ግን ያዳቆነ ሰይጣን ሆነና ይሄው ዛሬ የምናየውን ሆኑ፡፡ በእርግጥም የግፋቸውንና የአረመኔነታችውን መጠን በሰውኛ ፍርድ ቢታለፍ እንኳን እግዚአብሔር ስለሰፈረው ይሄ ዛሬ የሆነው እንዲሆን በራሳቸው ተንቀዠቀዡ፣ እጅግ የከፋው የአረመኔነታቸውን ጥግ አደረጉ፡፡ እግዚአብሔርን (እውነትን) ለማወቅ ባልፈለጉት መጠን ለማይረባ አእምሮ ስለተሰጡ በራሳቸው ፍቃድ ወደሲኦል ወረዱ፡፡ ይሄ አይነተኛ የልዑል እግዚአብሔር ፍርድ ምሳሌ ነው፡፡ እርግጥ ነው ይሄ የምናየውም የምድራዊው ክስተት የእግዚአብሔር ትዕዛዝ ነው፡፡  ያሳዝናል! ይሄ ለሁሉም ዛሬ ባለጊዜ ነን ወይም ወደፊት ስልጣንን የምታስቡ ማስተዋል ብትችሉ በጣም ትልቅ ምልክት ነው፡፡ እርግጥ ነው አለማስተዋል እንጂ ታላላቅ የተባሉት እነሳዳም ሁሴን፣ ጋዳፊ በርካታ የምድራችን ግፍ አድራሾች ምን እንደሆነባቸው አይተናል፡፡ የወያኔ ደግሞ ከሁሉም የከፋ በመሆኑ ለሰሩት ግፍ ሰውኛ ሕጉ ቢተዋቸው እንኳን ከላይ እንደማይቀር ይሄው ዛሬ አየንው፡፡

ዛሬስ ምን እነማራልን፡፡ ባለስልጣኖች ሆይ፣ ፖለቲከኞች ሆይ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ ምን እየሆነ እንደሆነ አስታውሉ፡፡ እርም የሆነውን ነገር ሁሉ ከመካከላችሁ አውጡ፡፡ ወያኔ ብዙ እርም የሆነ ለአገርና ትውልድ እርግማን ሆኖ የሚቀጥል ብዙ ነገር አስቀምጣለች፡፡  አንዱንም ወያኔ ያስቀመጠችልንን እርግማን አልተውንም፡፡ በተለይ ዛሬ ስልጣን ላይ ያላችሁ በእርግጥም ከወያኔ ጋር አብራችሁ የኖራችሁና ብዙ ግፍም አብራችሁ የፈጸማችሁ እንደሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ እያወቀ የሆነውን ሁሉ ትቶ ራሱ ባመጣው ለውጥ የለውጥ ዋና መሪ ሆናችሁ እንደትቀጥሉ እድሉን ቢሰጣችሁም ዛሬም ከአሳደጋችሁ ከወያኔ የተማራችሁትን እንጂ  ዛሬ በወያኔ የሆነው ነግ በእኔ ብላችሁ ለማሰብ የተጋረደባችሁ ይመስለኛል፡፡ ይሄ ነገር እጅግ ያሳስበኛል፡፡ እንግዲህ በአለፉት ወደ 50 ዓመት የተጠጋ እድሜ የሄድንበትን የሲዖል ጉዞ አሁንም ከዚህ ሁሉ መከራ በኋላ እንኳን ባለስልጣኖቻችንና ፖለቲከኞቻችን በሕዝብ ላይ የሆነውን ሁሉ ግፍ እስኪ እርግማን አይሁንብን ይብቃን ለማለት እየቻላችሁ አይመስልም፡፡ እግዚአብሔርን (እውነትነ፣ ፍትህን) ለማወቅ ባልፈለጉት መጠን …. የሚለው የፈላስፋው ትንቢት እየተፈጸመባችሁ እንደሆን ብታስተውሉት ጥሩ ነው፡፡

ዛሬ በተለይ ስልጣን ላይ ያላችሁት ለሁለተኛ ጊዜ እድል ገጥሟችኋል፡፡ ከዚህ በኋላ ላይገጥማችሁ ይችላል፡፡ ዛሬ የብዙ ኢትዮጵያውያንም ከገጠሙት ገጠመኞቹ አንዱ ነው፡፡ ዛሬ ሁሉም በሚባል ደረጃ (ከጥቂት ሊድኑ ከማይችሉት በቀር) በወያኔ አረመኔያዊ ግፍ የተነሳ በአንድነት ለአገራቸው ቆመዋል፡፡ ዛሬ እራሱን መስዋዕት እያደረገ የወያኔን ነቀርሳ ሰንኮፍ እየነቀለ ያለውን ሠራዊታችንን በሙሉ ልብ ሞት ቢመጣ እንኳን አብሮል ሊሰለፍ ፍቃዱ ሆኗል፡፡ በእርግጥም ነው በተለይ የአማራ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ ነቀርሳውን ለመንቀል እያደረገ ካለው ተጋድሎም በላይ በአውሬው ለተከበቡ የመከላከያ ሰራዊታችንም ደርሶለታል፡፡ በአፋር ሕዝብ፣ ታጣቂና አጠቃላይ አመራሩ እያደረገ ያለውን አበርክቶም አይተናል፡፡ አማራና፣ አፋር ወያኔ ቤቴ ከሚላት ትግራይ አዋሳኝ ከመሆናቸውም አንጻር  ቀጥተኛ የዚህ ጦርነት ተሳታፊ ሲሆኑ በሩቅ ያሉት በተለይም የሱማሌው ሕዝብና አመራር ለወያኔ መወደቅ እያሳየ ያለው ድጋፍ የሚደነቅ ነው፡፡ እርግጥ ነው የወያኔ አረመኔያዊ ግፍ ምን አልባትም ከአማራ ቀጥሎ የሆነው በሱማሌ ሕዝብ ነው፡፡  ወያኔ ግን ሁሉንም አድምታለች፣ ልዩነት የለኝም የምትለውን የትግራይን ሕዝብ ሳይቀር፡፡ የግፉን መጠን አስከፊነት ደረጃ ካልሆነ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰላማዊ ሠልፍን እንደ ትግል ስልት - በ ሰለሞን ጎሹ

የሆነው ሁሉ ምን አልባትም በዚህ ሁሉ አስከፊ መከራ እንድንማር ሆኗል፡፡ አሁንስ እንማራልን? ሁሉም እየኖርንበት ያለው ነገር ወያኔ በሰራችልን ሆኖ እውን ሠላም እንኖራለን? እኔ የሚከተለውን ከምንም በፊት አመክራለሁ፡፡ ለጊዜው ምርጫውም ምኑም ምንም ይቅርብን፡፡ መጀመሪያ ከወያኔ መርዝ የፀዳ መሠረት ያስፈልጋል፡፡ ምርጫ ተደረገ አልተደረገ አሁን ባለው ሁኔታ ያው የተለመደ ችግ ካልሆነ ሠላምም ሊመጣ የሚችል አይመስለኝም፡፡ ከዚህ ሁሉ በፊት ሥልጣን ላይ ያላችሁም ሌሎች ፖለቲከኞችም ሁሉም የወያኔን መርዝ ከአገሪቱ ያጽዳ፡፡ ምርጫ ምናም ኮረና እንኳ አዘግይቶታል፡፡ ለመሠረታዊ ደህንነታችን ወሳኝ የሆነ ሕግጋትን ሳናወጣ በዚሁ ወያኔ በሰራችው የአገርና ትውልድ አጥፊ ሥርዓት ወደ ምርጫ መሄድ ከምንም በላይ አደገኛና አሁን ያገኘንውን አጋጣሚም ተመልሰን ላናገኘው የምንችልበት ነው፡፡  ፖለቲከኞች የሚከተሉት የጥቂት ጽንፈኞች ጮኸት እንጂ የብዙሀኑን ደህንነት አደለም፡፡ ይሄ አይነቱ ቁማር ብዙ ዋጋ እያስከፈለን ነው፡፡ በመሆኑም ከምንም በፊት ወያኔ ያመጣችብንን ሁሉ አስወግደን፣ ቆጭ ብለን ተነጋግረን የኢትዮጵያውያንን ሥርዓትን ሕግ መሠረት እንጣል፡፡

  1. ሕገ-መንግስት፡- አሁን ባለው ሕገ መንግስት ምክነያት በግልጽ አገር አደጋ ላይ እየሆነች ደጋግመን እያየን አሁን ተጨማሪ ጊዜ በዚሁ ሕገ-መንግስት በተባለ አደገኛ ሕግ መቀጠል ማሰብ እጅግ አደገኛ የሆነ የአገርን የማፍረስ ተግባርን ማስቀጥል ነው፡፡ በመሆኑም ከምንም በፊት ሁሉም ተሰባስቦ (ስልጣን ላይ ያሉትም ሌሎችም፣ ሕዝብም የሚሳተፍበት) ሕገ መንግስት ይርቀቅና ይውጣ፡፡ ከምርጫ በፊት፡፡ ግድ የለም ምርጫውን ቀስ ብለን እናደርገዋልን፡፡ ሥልጣን ለመያዝ የቸኮላችሁ ካላችሁ ከነጭርሱም ልትወገዱ እንጂ ለሥልጣን ስትሉ አገር የማፍረስ እድል ሊሰጣችሁ አይገባም፡፡
  2. የኢትዮጵያ ሰንደቅዓላማ፡- ከአረንጓዴ ቢጫና ቀዩ ቀለሞች ውጭ በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ላይ ምልክት ያደረገው የእርግማኑ ቡድን ወያኔ እንጂ የቀደሙ አባቶቻችን የሞቱላት ሰንደቅ ዓላማ ሶስት ቀለማት ብቻ የሆነች ምንም ሌላ ምልክት የሌለባት ነች፡፡ እነዚህ ቀለሞች ለኢትዮጵያውያን ብቻም ሳይሆን ለብዙ አፍሪካ አገራትም የነጻነት ምልክት ናቸው፡፡ ለእኛ ኢትዮጵያውያን ደግሞ ብዙ ነገር ማለት ናችው፡፡ የወያኔን ምልክት እያውለበለቡ ከወያኔ ከወያኔ የጸዳ ሥርዓት ሊኖር አይችልም፡፡ የወያኔ የሆኑ ምልክቶች ሁሉ መጥፋት አለባቸው፡፡ ናዚ ምልክቶቹ ሁሉ እንደታገዱ፡፡ የወያኔ ደጋፊዎች አይቀበሉትም በሚል ኢትዮጵያውያን ሰንደቅ ዓላማቸውን ከልክሎ የኢትዮጵያ መሪ ለመሆን አይቻልም፡፡ አውቃለሁ ብዙ ኦሮሞ ዛሬ አባቶቹ የሞቱላት የአረንጓዴ ብጫ ቀዩ ሰንደቅ ጭራሽ እያስደነበረችው ነች፡፡ ከወያኔም ብዙ ይበረግጋል፡፡ ወያኔ ከትግራይ ክልል ከእነጭርሱም ምልክት ያለውንም አረንጓዴ ቢጫ ቀዩን ትታ የሕዝቡን ልብስ ሳይቀር በራሷ ባንዲራ ቀይራለች፡፡
  3. የብሔር ፓርቲና ፖለቲካ፡- ብሔርን መሠረት ያደረጉ የፖለቲካ ፓርቲ በሕግ መታገድ አለበት፡፡ ከምርጫ በፊት የፖለቲካ ፓርቲ እሆናለሁ ብሎ የሚያስብ ከምንም በፊት ብሔርን መሠረት ያላደረገ ቢቻ እንሆን የሚያስችል ሕግ እንዲወጣና የፖለቲካ ፓርቲዎች ከብሔር፣ ሀይማኖትና ማንነትን የሚገልጽ ሌላ ሥብስብን መሠረት ያላደረገ አደረጃጀት ፈጥረው እንዲዘጋጁ ጊዜ ሊሰጥ ይገባል፡፡ ይህ ምርጫ መቅደም ያለበት ነው፡፡ ማንም እየተነሳ ዘር ውስጥ እየተወተፈ አገርንና ሕዝብን ሲያምስ አይኖርም፡፡ የዘር ፖለቲካ በየትኛውም አገር የተከለከለ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን የማንም ዘረኛ መሞከሪያ መሆን የለብንም፡፡ የዘር ፖለቲከኛ በምን መስፈርት ነው የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስቴር ወይም ሌላ የአገሪቱ ባለስልጣን የሚሆነው፡፡ ይሄ ይታሰብበት፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ዘርንና ሌላ ማንነትን ለፖለቲካ መጠቀምም በሕግ መታገድ አለበት፡፡
  4. ክልል፡- ዛሬ ክልል ብላ ወያኔ የሰየመቻቸው በዘር የተሸነሸኑ እንጂ በዜክነት ኢትዮጵያውያን የሚኖሩባቸው እንዳልሆኑ የየክልሉን ሕገ-መንግስ የሚሉትን ማየት በቂ ነው፡፡ በእነዚህ ወያኔ በሠራቸው መዋቅር አገር ለማፈረስ ሌላ እድል መስጠት አሁን አደገኛ ነው፡፡ ይሄም ከምርጫ በፈት በተለይም ደግሞ አሁን የተፈጠረውን እድል በመጠቀም አዲስ አገራዊ አስተዳደር መዋቅር ሊዘረጋ ይገባል፡፡
  5. መከላከያ፣ የፍትህና የደህነት ተቋማት፡- እነዚህ ተቋማት በአዲስ መልክ ከስልጣን መጠቀሚያነት ነጻ እንዲሆን ግድ ነው ለሀሉም ሕግና ሥርዓት፡፡ ምን ዓልባት አሁን በምናየው መከላከያው ትንሽ ፈር የያዘ ይመስላል፡፡ ሆኖም እሱም ይቀረዋል፡፡ የፍትሁና የሕግ አስከባሪ ፖሊሱ ነገር እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ እንግዲህ እነዚህ ተቋማት ነጻ ባልሆኑበት ዲሞክራሲ በሉት ሌላ ማንኛውም ፍትህን መጠበቅ ሞኝነት ነው፡፡ እነዚህ ተቋማት በግልት ሥልጣን ላይ ያለ ቡድንና ግለሰቦች አገልጋይ ሆነዋል፡፡ አገር በሕግና ሥርዓት እንጂ በየትኛውም መስፈርት አትመራም፡፡ የፖለቲካ መሪ ባይኖር እነዚህ ተቋማት እስካሉና በትክክል እስከሰሩ ድረስ አገርና ሕዝብ ደህንነታቸው አደጋ ላይ አይወድቅም፡፡ ብዙ የአውሮፓ አገራት ፓርላማቸው ለወራት አንዳንዴም ከዓመት በላይ (ለምሳሌ ቤልጅየም) ፈርሶ እነዚህ ሦስት ተቋማት ከፖለቲካ በጻ ስለሆኑ ያለምም ችግ የመንግስት አሰራር ይቀጥላል፡፡ መንግሰት ማለት እነዚህ ሶስት ተቋማት ናቸው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ አደለም፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ እንጂ መንግስት አደለም፡፡ ብዙዎች ምንግስትና ፓርቲ ስለሚምታታባቸው ሥልጣን ላይ ሲወጡ ሁሉም ነገር እኛ ካልነው ውጭ እንዳይሆን ይላሉ፡፡ መጀመሪያ የመንግስታዊ ሕላዌን ምንነት ሳይረዱ የመንግሰት ስልጣን እየያዙ ነው ችግሩ
ተጨማሪ ያንብቡ:  የጃዋር ቃለምልልስ በፓልቷክ

እነዚህ ጉዳዮች ሁሉም ሕገ-መንግስቱ በአዲስ መልክ ሲረቅ አብረው ሊካተቱ የሚገቡ ሆነው ትግበራቸውም ከምርጫ በፊት እንዲሆን አበክሬ እጠይቃለሁ፡፡ ወደ 50 ዓመት በጥፋት ኖረናል፡፡ ከዲሞክራሲ ምናምን በፊት ፍትህና ሕግ ይስተካከል፡፡ ሲጀምር ዲሞክራሲ ሕግና ሥርዓት ካለ ብቻ ነው ጥቀሙ፡፡

በተረፈ አንዳንድ ነገሮችን ልጠቁምና ላብቃ፡፡ በአማራ ክልል ምን አዚም እንደሆነ ባይገባኝም የአማራ ባለስልጣናት ወያኔ ከፈጠረችላቸው አሰራር ውጭ እንዳያስቡ የተደረጉ ነው የሚመስለው፡፡ አማራን አስተዳድራለሁ የሚለው ብአዴን (ብሔረ አማራ ዴሞክራሳዊ ንቅናቀ) ሥሙ ራሱ አማርኛ ሳይሆን ወያኔ የሰየመችለት የትግሪኛ ቃል ነው፡፡ አሁን በአዴን ብሏል ራሱን፡፡ የሚያውለብልበው ባንዲራ ደግሞ የወያኔ ኮፒ ቢባል ይሻላል፡፡ አዝናለሁ፡፡ ይሄ ሁሉ ግፍ የተፈጸመበትን አማራ እየመሩ የገዳዮቹን ምልክት ይዞ መገኘት፡፡ የባሕርዳር ኤርፖርት እስካሁንም ሥም የተቀየረለት አልመሰለኝም፡፡ ግንቦት 20 ነው፡፡ ግንቦት 20 የሚል ትምህርት ቤትም የሆነ ቦታ ዓማራ ክልል ውስጥ ሰምቼ ነበር፡፡ አስቡት ለአማራው የሞቱ ያሕል የምትታሰበውን ግንቦት 20ን በየቦታው ሰይመውለት፡፡ የሚገርመው የባህርዳር ኤርፖረት በፊት በላይ ዘለቀ ነበር የሚባለው፡፡  እንግዲህ የአማራ ባለስልጣናት ዛሬ ወያኔን እየቀበረ ካለው የአማራ ሕዝብ ጋር እንዴት መቀጠል እነዳለባቸው ማሰብ ካልቻሉ ወርድ ከራሴ፡፡ እነዚህን እርግማኖች ቢያንስ ግን ለሕዝብ መጠቆም እፈልጋለሁ

በኦሮሚያ አሁንም ብዙ ያልተፈቱ ነገሮች አሉ፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ብዙ ባለስልጣናቱ፣ ፖለቲከኞቹና ምሁራኑ ከወያኔ ያልተናነሰ አረመኔያዊ ምልከታቸውና እያራመዱት ያለው አቋም  አሳዛኝ ነው፡፡ ዛሬም አስታውሳለሁ፡፡ እንግዲህ ሁሉም ያስብበት ከላይ ያልኩትን ዘርን መሠረት ያደረገን ፖለቲካ በሕግ ቢታገድ ዋነኛ ፈተናውም ከዚህ ክልልና ጥቂት ሌሎች  እንደሚሆን እናውቃለን፡፡ ሌላው ኢትዮጵያዊ ሰልችቶታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  መራር እውነቶች። ወያንያዊ ነው። - ዳዊት ዳባ።

በአገር አቀፍ ደረጃ ያው ወያኔ ያመጣቸው የተቋማት ስያሜ ሌላው አስገራሚ ነገር ነው፡፡ የተቋማቱ ሥም በየትኛውም አገራዊ ቋንቋ አለመሆኑ ብቻም ሳይሆን ከውጭ ሆነው ለሚታዘቡንም አሳፋሪ ነው፡፡ አንድ አገር እንዲህ ባለ ግድ የለሽ ሁኔታ ተቋማቶቿን ሰይማ ነጻና በራሱ የሚተማመን ተውልድ ልታፈራ አትችልም፡፡ ይሄ የብዙ አገሮች መርሆ ነው፡፡ የተቋማቱ ሥም በኢንግሊዘኛም በአማርኛም ተመሳሳይ በሚባል ሁኔታ ነው የምናየው፡፡ በክልል በተባሉት አካባቢ የተሻለ ነው፡፡ ለነገሮ የፖለቲካ መሪዎቻችን ራሱ ለሕዝብ ሲናገሩ መቼ ታሳቢ ያደርጉና ሕዝቡን፡፡ ምሁር የሆኑ እየመሰላቸው ይመስላል አንዴ የአገሬ ገበሬ በአስተርጓሚ ካልሆን ሊረዳቸው እስከማይችል እያወሩለት መሪህ ነን ይሉታል አንዳንዶች፡፡ የቋንቋ አጠቃቀም ጥራት ይታሰብበት፡፡ በነገራችን ላይ ጉራማይሌ አጠቃቀም ለቋንቋ ችሎታ ማሳደግም ችግር አለው፡፡ ኢንግሊዘኛን በጉራማይሌ የለመደ ሊናገር አይችልም፡፡ ሌላው እንደ አማራው ክልል አይነት እኔን ሁሌ የሚገርመን የሆለታ ገነት ጦር ትመህርት ቤት ሥያሜ ነው፡፡ ወያኔ ጀነራል ኃይሎም አርዓያ ብላ ሰይማው እስካሁንም እንደዛው ነው የሚል ነገር ሰምቻለሁ፡፡ ያሳዝናል፡፡ እኔ በግሉ ኃያሎም አርዓያ የተባለውን ሰው ከሰማሁለት ታሪኩ አንጻር ከሌሎቹ ወያኔዎች የተሻለ ስብዕናና ጀግንነትም ስላለው ከሚያከብሩት ነኝ፡፡ ሆኖም ለኢትዮጵያ ሳይሆን ለራሱ ቡድን የተዋጋ ሊያውም ለኢትዮጵያ ነቀርሳ ለሆነ ቡድን ተሰልፎ የተዋጋን ሰው ነው፡፡ የአገር መከላከያ ሠራዊቱ ልዩ ታሪካዊ ምልክቱ ሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤትን በወያኔ ጀነራል ሥም ሠይሞ ኢትዮጵያዊነትን የተላበሰ ሰራዊት አፈራበታለሁ ማለት ስድብ ጭምር ሆኖ ተሰምቶኛል፡፡ በተለይ ደግሞ አሁን ላለው የሰራዊት አባል፡፡ በነገራችን ላይ አሁን ያለውን ጦርነት የመሩት ጀነራሎች አብዛኞቹ የቀድሞ ሠራዊት አባል እንደሆኑ ምን ያህሎቻችን እናውቃለን፡፡ ጀነራል ብርሀኑ ጁላን ጨምሮ፣ ጀነራል ባጫ ደበሌ፣ ጀነራል አለም እሸት ደግፌ ሌሎችም የቀድሞ ሠራዊት ዓባል ነበሩ፡፡ ጀነራል ዓበባው የቀድሞ ሰራዊት አባል ባይሆንም በመከላከያው ውስጥ ባለው ኢትዮጵያዊነት መንፈስ ስላልተወደደ ከጀነራል ባጫ ጋር የተገለለ ሰው ነው፡፡ ለማንኛውም አሁን የምናየው ወያኔ እየተበቀለ ያለው የቀድሞው ሠራዊት አባል የሆኑ የሚመሩት ሠራዊትና የአማራ ልዩ ኃይልና ሚኒሻ መሆናቸው ትልቅ ትምህርት ነው ለሁሉም፡፡ አማራ በማንነቱ፣ የቀድሞ ሠራዊት ደግሞ የደርግ በሚል ስንት መከራ ያየ እስካሁንም ተበትኖ የሚኖር ነው፡፡ ለአገር ደህንነት ግን ብዙ ገድልን የሰራ ነበር፡፡

እንግዲህ ማውተዋሉን ቅዱስ እግዚአብሔር ሰጥቶን እርም የሆነውን ሁሉ ከመካከላችን አውጥተን ኢትዮጵያን የእኛ ብቻ ሳትሆን እንደቀድሞው ሌሎች የተገፉም ማረፊያ የሰላም አገር ለማድረግ ያብቃን፤፡

ቅዱስና ኃያሉ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይጠበቅ ይባርክ! አሜን!

ሠርፀ ደስታ

2 Comments

  1. ምክርህ መጥፎ ነው አይባልም፤፡ እስከዛሬ ከጻፍካቸው “ጥሩ” የሚባል ነው፤፤ ነገር ግን “ሁሉን አዋቂ ነኝ” በሚል መንፈስ ዘሃበሻን ስታጣብብ ከርመህ ቁርጡ ሲመጣና ሰለ “ህግ የማስከበሩ” ትልቅ ጉዳይ ቃል ሳትትነፍስ አሁን የህይል ሚዛን አይተህ ብቅ ስትል የሰዉ ቢቀር ህሊናህ አይታዘብህም? ትንሽ ጊዜ እንኳ ብትጠብቅ አይሻልም ነበር?

  2. ሰርጸ ደስታ እንደማንኛዉም ጊዜ ስለ ሀገርህ የሰጠኸዉ ምልከታ ይሄ ቀረዉ የሚባል አይደለም ጠ/ሚኒስትሩ ሰዉ ሲነግራቸዉ እልህ ይይዛሉ ዛሬ ባጋጣሚ ያለንበት ሁኔታ መልካም ነዉ እኝህ ሰዉ 3 እድል አስምልጠዋል በዚህኛዉ ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ ማድረግ ካልቻሉ ከስብሀት ነጋ በባሰ ሁኔታ ተዋርደዉ መጨረሻቸዉ የሚያምር አይመስለኝም። ኦሮምያ ተብሎ በተከለለዉ በረት ነገሩ ሁሉ መላ ቅጡን ያጣ የጁዋርን አድናቂዎች መስመር ካልያስያዙዋቸዉ ከማንም በላይ ኦሮምያ የሚባለዉ ክልል ከድጡ ወደ ማጡ እንደሚወርድ ጥርጥር አይኖርም።
    ወንጀለኞች በሲስተሙ ዉስጥ አሁንም በብዛት አሉ ካንሰር የያዘዉ የሰዉነት ክፍል ተቆርጦ ካልተሰናበተ ሌላዉን ስለሚመርዝ ጠቅላዩ ማስተወሻ መያዝ ይገባቸዋል።
    ምርጫ የተባለዉን መተዳደሪያዉን ፖለቲካ በመቸርቸር የተጠመደዉ ስራ ፈት በመሆኑ ምርጫዉ እንዳልከዉ አገር መልክ እስክትይዝ መቆየቱ መልካም ነዉ። አባ ዊርቱ ምነዉ ጠፉ ከአንድነት ሀይሉ መላተሙ በዛባቸዉ መስል?

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share