አገርን የማያጸና ህገ መንግስት – ገብረ አማኑኤል

ህገመንግስት የህጎች የበላይ ነው። ይህን የምንልበት ምክንያት የኣንድ ኣገር ዝርዝር ህጎች የሚመነጩት ከህገ መንግስት በመሆኑ ነው ማለት ይቻላል። ህጎች በመሰረቱ የኣንድን ኣገር ሰላምና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና የዜጎችን መብቶች ለማስከበር የሚቀረጹ መሳሪያዎች ናቸው። የኣገሮች ህገ መንግስታትን  በንጽጽር ለማየት ይህ ኣጭር ጽሁፍ በቂ ስላልሆነ ጥቂት የዓላማነት ይዘት ያላቸውን ኣንቅጾች ብቻ ቀንጭበን ኣንመለከታለን።

የአሜሪካ ህገመንግስት ዓላማዎቹን በሚያሳየው በዋናው መግቢያ ርዕሱ ላይ ኣንደዚህ ይላል።

“እኛ የዩናይትድ ስቴትስ ህዝብ (`We the people of the United States`)፣ የተሻለ ፍጹም ኣንድነትን ለመመስረት ፣ ህግን መሰረት ለማስያዝ፣ ኣገራዊ መረጋጋትን ለማረጋገጥ፣ የጋራ መከላከያን ለማጠናከር፣ ኣጠቃላይ ጥቅምን/ደህንነትን ለማሳደግና፣ የኛንና የመጪውን ትውልድ  የነጻነት በረከቶቻችንን ለመጠበቅ፣ ይህንን የተባበረውን የኣሜሪካ ግዛቶች  ህገ መንግስት በኣዋጅ መስርተናል።“ የአንግሊዘኛውን ሓረግ ከላይ የተጨመረው የኣገራችን ህገ መንግስት ጋር ለማነጻጸር ኣንዲረዳ ነው።

ከዚህ የኣሜሪካ ህገ መንግስት ዋና መንደርደሪያ  የምንገነዘበው፣ ዋናው የህጎች መሰረት የህዝቦች ኣንድነትን፣ መረጋጋትን ኣገር መጠበቅን፣ የህዝብን ሰላማዊ ኑሮና ለትውልድ የሚሻገር ነጻነትን ማስጠበቅን ዋና ዋና የህገ መንግስቱ ዓላማዎች ኣድርጎ የሚመለከት መሆኑን ነው።

በኣህጉራችን የምትገኘው የደቡብ ኣፍሪካ ህገ መንግስት መንደርደሪያ ደግሞ ኣንዲህ ይላል።

“አኛ የደቡብ ኣፍሪካ ህዝብ፣ (`We, the people of South Africa`) ያለፈውን ታሪካችንን ኢፍትሃዊነት አንገነዘባለን፣ በምድራችን ላይ ለፍትህና ለነጻነት ለተሰቃዩ ክብር አንሰጣለን፣ ኣገራችንን ለመገንባትና ለማሳደግ የተሰሩትን ሁሉ ኣናከብራለን፣ ኣንዲሁም ደቡብ ኣፍሪካ የሁሉም ዜጎቿ መሆኗንና በልዩነታቸው መካከል ባንድነት የሚኖሩ ዜጎቿ ኣገር መሆኗን አናምናለን።“ ይላል።

ይህም ህገ መንግስት የዜጎችን የኣገር ባለቤትነት ኣንዲሁም ለቀደሙ የኣገር ግንባታ ስራዎች ኣክብሮት በመስጠት ኣገርን የመገንባትና የማሳደግ፣ ኣንዲሁም የቀለምን ጨምሮ ልዩነቶች ቢኖሩም በኣንድነትን ዜጎቿ የሚኖሩባት ኣገር መሆኗን የማረጋገጥ ዓላማ ያለው ህገ መንግስት መሆኑን ማየት ይቻላል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  [የሚኒሶታው መድሃኔዓለም ቤ/ክ ጉዳይ] - አንድነት ይመጣል፡ እውነቱም ይገለጣል (ከዲ/ኤፍሬም ስለሺ)

በኣንጻሩ የኢትዮ|ጵያ ህገ መንግስት መግቢያን ስንመለከት ይህንን ኣናገኛለን።

እኛ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች:-

በሀገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም፣ ዋስትና ያለው ዴሞክራሲ እንዲሰፍን፣ ኢኮኖሚያዊና ማኀበራዊ እድገታችን እንዲፋጠን፣ የራሳችንን ዕድል በራሳችን የመወሰን መብታችንን ተጠቅመን፣ በነፃ ፍላጎታችን በሕግ የበላይነት እና በራሳችን ፈቃድ ላይ የተመሰረተ አንድ የፖለቲካ ማኀበረሰብ በጋራ ለመገንባት ቆርጠን በመነሳት፤

ይህን ዓላማ ከግብ ለማድረስ፣ የግለሰብና የብሔር/ብሔረሰብ መሠረታዊ መብቶች መከበራቸው፣ የፆታ እኩልነት መረጋገጡ፣ ባሕሎችና ሃይማኖቶች ካለአንዳች ልዩነት እንዲራመዱ የማድረጉ አስፈላጊነት ጽኑ እምነታችን በመሆኑ፤

ኢትዮጵያ ሀገራችን የየራሳችን አኩሪ ባሕል ያለን፣ የየራሳችን መልክዓ ምድር አሰፋፈር የነበረንና ያለን፣ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በተለያዩ መስኮችና የግንኙነት ደረጃዎች ተሳስረን አብረን የኖርንባትና የምንኖርባት ሀገር በመሆንዋ፤ ያፈራነው የጋራ ጥቅምና አመለካከት አለን ብለን ስለምናምን፤

መጪው የጋራ ዕድላችን መመሥረት ያለበት ከታሪካችን የወረስነውን የተዛባ ግንኙነት በማረምና የጋራ ጥቅማችንን በማሳደግ ላይ መሆኑን በመቀበል፤

ጥቅማችንን፣ መብታችንና ነፃነታችንን በጋራ እና በተደጋጋፊነት ለማሳደግ አንድ የኢኮኖሚ ማኀበረሰብ የመገንባቱን አስፈላጊነት በማመን፤

በትግላችንና በከፈልነው መሰዋዕትነት የተገኘውን ዴሞክራሲና ሰላም ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ፤

ይህ ሕገ መንግሥት ከዚህ በላይ ለገለጽናቸው ዓላማዎችና እምነቶች ማሰሪያ እንዲሆነን እንዲወክሉን መርጠን በላክናቸው ተወካዮቻችን አማካይነት በሕገ መንግሥት ጉባዔ ዛሬ ኀዳር 29 ቀን 1987 አጽድቀነዋል፡፡

ይህ መንደርደሪያ ምንም ኣንኳን ያማሩ ቃላት የታጀበ ቢሆንም ኣንድ ከሚያደርጉ፣ የሰውን ልጅ ክብር፣  ደህንነትና ጥቅም ከሚያስከብሩና መብቱንና ነጻነቱን ከፍ ከሚያደርጉ ቃላት ይልቅ ለመለያየት የሚያመቻቹ ሃረጎች የሚጎሉበት ሆኖ ኣናገኘዋለን። ለብዙ ኣመታት በነጻነት የኖረች ኣንድ ሃገር ሳትሆን ገና በመቋቋም ላይ ያለች ጀማሪ ኣገር የሚያስመስሉ ሀረጎችን ይዟል። ለምሳሌ ያህል “ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች፣ የራሳችንን ዕድል በራሳችን የመወሰን መብታችንን ተጠቅመን፣ በራሳችን ፈቃድ ላይ የተመሰረተ፣ የወረስነውን የተዛባ ግንኙነት፣ የግለሰብና የብሄር ብሄረሰቦችን መሰረታዊ መብቶች፣  የየራሳችን መልከኣምድር ኣሰፋፈር ያለን፣ መጪው የጋራ ዕድላችን መመስረት፣“ ወዘተ። የሚሉት ሀረጎች ኣንድ ኣገር ስለመሆናችን አምብዛም የማያሳዩና የሚለያዩን የሚመስሉ ናቸው። ልዩነታችንን የሚያጎሉና የታቀዱ መለያየቶችን የማበረታታት ይዘት ያላቸው ሆነው አናገኛቸዋለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰውየው (የመጨረሻ ክፍል) ከይገርማል ታሪኩ

ይህ ህገ መንግስት ከኣለም ኣቀፍ ድንጋጌዎች የተወሰዱ ጥሩ የሚባሉ የሰው ልጅ መብቶችን ለማረጋገጥ የሚጠቅሙ ኣንቅጾችን የያዘ ነው። ይህ መልካም ነው።  ሆኖም በቃልና በጽሁፍ ማስቀመጥና በተግባር መተርጎም ኣጅግ የተለያዩ በመሆናቸው ኣነዚህ ኣንቀጾች በኣጃቢነት የተደረደሩ ስለመሆናቸው በተግባር የታዩት የሶስት ዓስርት ዓመታት የመብት ጥሰቶች ቋሚ ምስክሮች ናቸው።

በዚህ ህገ መንግስት ውስጥ ከተደነገጉት መካከል ፍጹም የማልስማማበትና በማንኛውም ኣገር ህገ መንግስት የለም ብዬ የማምነው ድንጋጌ ኣንቀጽ 39 ነው። (የሃገርን መገንጠል የሚፈቅድ ህገመንግስት ካለ ይቅረብ) ከመነሻው ይህ ኣንቀጽ ያለመው በመጀመሪያ የኢትዮጵያ ክፍል የነበረችውን የኤርትራን መገንጠል፣ ከዚያም ኣንደየሁኔታው ትንንሽ ኣገሮች ለማስከተል የታሰበበት መሆኑ ብዙዎች የሚስማሙበት ይመስለኛል።

ይህ ህገ መንግስት የተመሰርተው ጥቂት ሆነው የመገንጠል ኣላማ ሲያራምዱ የነበሩ ግለሰቦች ከጻፉት የኣንድ ፓርቲ ማኒፌስቶ ማስፈጸሚያ አንዲሆን ታስቦ መሆኑን ቀደም ብለው የተገነዘቡ ኣንዳሉ ሁሉ በተለይ ኣሁን ብዙዎቻችን በኣስቸጋሪው መንገድ ካለፍን በኋላ በሚገባ የተረዳን ይመስለኛል። ከዚህ ስንነሳ ደግሞ ዋና ዋና የዚህ ህገ መንግስት ጉድለቶች ለኣንድ ጠንካራ ኣገር ታስቦ ሳይሆን የተዳከሙ ትንንሽ መንግስታትን የመመስረት ኣላማን ለማስፈጸም ኣንዲረዱ ተደርገው የተቀረጹት ኣንቀጾች ሆነው ኣናገኛቸዋለን።

በዚህ የተነሳ ኣሁን በደረስንበት ደረጃ በኣንድነት ከመጠናከር ይልቅ በልዪነት አየተከለልን አንድንለያይ የሚያደረጉን ስራዎች ምን ያህል ኣንደለያዩንና ኣሁንም በትጋት አየሰሩ ያሉ መኖራቸውን አንመለከታለን። ይህ ህገ መንግስት በጥቅሉ በምንም መመዘኛ ኣገርን በሉዓላዊነቷ ኣንድ ኣድርጎ የሚያኖር ህገ መንግስት  ኣይደለም።

የኣገራችን የወቅቱ መሪ፣ `በኣገር ኣንድነት ላይ ኣንደራደርም አኛ ሳንፈርስ ኢትዮጵያ ኣትፈርስም` የሚለው ኣባባላቸው የኣገራችንን ኣንድነት የሚወዱ ዜጎችን ምን ያህል ኣንዳስደሰተ ኣምናለሁ። አዚህ ላይ ዋናው ቁም ነገር ይህንን ኣንድነት ኣስጠብቆ ለትውልድ የሚያልፍ ኣንድነትና ነጻነት ለማውረስ የሚያስችሉ መሰረቶች ምን ያህል አየተጣሉ ነው? የሚለውን ስናይ ደስታችን በትካዜ ይለወጣል። ከነዚህ ዋና ዋና መሰረታዊ ርምጃዎች ኣንዱ ኣገርን የሚለያዩ ኣንቀጾችን የያዘው ህገ መንግስት ያለማወላወል ማሻሻል መሆን ኣንዳለበት ኣምናለሁ። ህውሃት ህገ መንግስቱ የሚሻሻለው በመቃብሬ ላይ ነው ኣንዳለች ተሰምቷል። ህዋሃት ዓላማዋ ጸረ ህዝብና ዘረኝነት የተጠናወተው በመሆኑ ቦታዋን ማስጠበቅ ኣልቻለችም። ስለዚህ የህወሃት ይሆነን ሁሉ በጥንቃቄ መመርመርና ከወጥመዷ መውጣት ተገቢ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አባ ሠረቀ ብርሃን በሽተኛ እንጅ በሽታ አይደሉም

በመሆኑም መንግስት ለውጥ ለኣገር ኣንድነት ቁርጠኛ አስከሆነ ድረስ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ነገር ቢኖር ይህን ህገ መንግስት ኣገራዊ ይዘት ኣንዲኖረውና በመግቢያው ላይ  ለናሙና ኣንደተመለከተው ኣንደ ኣሜሪካና ኣንደ ደቡብ ኣፍሪካ ህገ መንግስታት የኣገርን ሉኣላዊነትንና የህዝብን ደህንነትና ነጻነት ማስጠበቅ ተቀዳሚ ዓላማው ያደረገ ህገ መንግስት ኣንዲሆን ማድረግ ይገባዋል። ቢያንስ ይህ ኣስከሚሆን ድረስ ኣወዛጋቢ ኣንቀጾች የሚታገዱበት ሁኔታ ሊፈጠር ይገባል። ይህ ኣገርን ለቅርጫ ያቀረበ ህገ መንግስት ካልተሻሻለ ኣንድ ጠንካራ ኣገር ይዞ ለመዝለቅ የሚደረገውን ትግል አጅግ ውስብስብስ ያደርገዋል። ስለዚህ ብዙ መስዋዕትነት ከመከፈሉ በፊት ይህ ህገ መንግስት ሊመረመርና ሊሻሻል ይገባል። ኣገርን የማያጸና ህገመንግስት ካለመኖር ኣይሻልም።

ሆኖም፣ ብዙ መስዋዕትነት ቢጠይቅም የኣገራችን ኣንድነት ይቀጥላል፣ ሉዓላዊነቷ ይጠበቃል። ተስፋችን ጽኑ ነው ምክንያቱም ኢትዮጵያ በመጨረሻ አጆቿን የምትዘረጋበትን ታውቃለችና።

ፈጣሪ ኣገራችንን በኣንድነቷ ኣጽንቶ ይጠብቅልን!

ገብረ ኣማኑኤል

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share