ግን ለምን ?  – አረጉ ባለህ ወንድሙነህ

በ አረጉ ባለህ ወንድሙነህ (ጋዜጠኛ) ከ አትላንታ፣ ጆርጅያ

ትናንት ናዚ ጀርመን በአይሁዳዊያን ላይ ስለፈጸመው የዘር ማጽዳት ባነበብነው ታሪክና ባየነው ፊልም የሰውን ልጅ የጭካኔ ልክ አይተን እንዳላነባን፣ የቅርብ ጊዜ የጥቁር ህዝቦች አሳፋሪ የታሪክ  ክስተት የሆነውን የሩዋንዳን የዘር ጭፍጨፋ  እንደ አገርና እንደ ህዝግ ከማውግዛችንም በላይ የአብሮነት ተምሳሌት ተብለን በሞራል ልዕልና ከፍ ብለን እንዳልታየን፣ ሰለጠንን የሚለው አለም ሳይቀር የሃይማኖት ጎራ ለይቶ ደም ሲፋሰስ የሃይማኖት መቻቻልን በተግባር ከማሳይትም አልፈን የሃይማኖት ተሳዳጆችን አንዳላስጠለልን፣ ይህው  ዛሬ በአንድ አገር ለዘመናት አብረን የኖርን አና በተመሳሳይ እጣ ፋንታ የተቆራኘን ህዝቦች አውራጃ ከልለን፣ ሰወችን በቋንቋ ና በጎሳ ከፋፍለን፣ በተዛባ ታሪክና ትርክት ተመስርተን በሰጠናቸው ማንነት ወንጀለኛ አድርገን ከአእምሮ በላይ በሆነ ጭካኔ ስንጨፈጭፍ እንደዜጋ የሆነውን ሁሉ ለመረዳት ያስቸግራል። በዚህ ወቅት ምናልባትም ስሜት ሊሰጥ የመችለው መጠየቅ ብቻ ነው። ግን ለምን? ወደዚህ አሳፋሪ የታሪክ ምራፍ እንዴት ልንገባ ቻልን?  መቸ ነው የሰውነት ባህሪያችንን አውልቅን የአውሬነት ባህሪ የተላበስን? የት ላይ ነው የአብሮ መኖር ሰንሰልቱ የተበጠሰው? ከመቼ ወዲህስ ነው እንዲህ አይነት ጨካኝ ትውልድ ያፈራነው? ሌላም ሌላም።

ከሰባኪወችና ከፖሊቲከኞች መምጣት በፊትም ሆነ በኋላ ይህ ህዝብ የቋንቋ ልዩነት ሳይገድበው አብሮ በፍቅር ኖሯል። ዛሬ ነባርና መጤ ወይም ክርስትያንና እስላም ተብለው አንዱ ለሌላኛው ጠላት ተደርጎ ከመሰበካቸው በፊት እንደ አንድ ህዝብ ከፉና ደጉን አብረው አሳልፈዋል።  በአንድ አካባቢ የሚኖሩ የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች እንደ አካባቢ ተወላጅ ለአካባቢያቸው በአካባቢያቸው አብረው ሰርተዋል። ዛሬ አንዱ ሌላኛውን በጠላትነት ፈርጆ ያርዳል፣ ይሰቅላል፣ ንብረቱን ያቃጥላል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዕዘኑ ለቀሪ

ግን  ለምን? አንዴት ሰው በማንነቱ ብቻ ጠላት ተድርጎ ይፈረጃል? ሃዝንና ደስታን፣ ማግኘትና ማጣትን፣ ጭቆናና ነጻነትን፣ ሁሉንም አብሮ የተካፈለ ማህበረሰብ እንዴት የተለየ ቋንቋ በመናገሩ ብቻ በጠላትነት ተፈርጆ የሞት ፍርድ ይፈረድበታል?  አንዴት ሰው ከሰው ተፍጥሮ በውንድሙ ላይ መጥረቢያ ይሰነዝራል? አንዴት ሰው በአምሳያው የተፈጠረውን በቢላዋ ያርዳል?

ሁሉም ነገር ከአምሮ በላይ ነው። የአገዳድል ጭካኔው በጥንት ሮማውያን  ዘመን እነ ኔሮና ካሊቡላ የተባሉ በሰው ስቃይ የሚደሰቱ ( ሳዲስት) ነገስታት  ፈጽመውታል የተባለውን አረመኔያዊ ድርጊት የሚያስታዉስ ነው። ዛሬ የኛ ጉዶች በወገናቸው ላይ  የፈጸሙት አሰቃቂ ግድያ ገና ሃይማኖት ሳይሰበክ በህገ ልቦና ይተዳድር ከነበረና የሞራል ልዕልናው ከፈተኛ ክሆነ ማህበረሰብ በተገገኙ ወጣቶች የተፈጸመ መሆኑን ማመን ያስቸግራል።

ላለፉት ሁለት አመታት በኦሮምያ ክልል ዘርና ሃይማኖትን ለይቶ እየተፈጸመ ያለው ጥቃት በትክክለኛ ስሙ እንጥራው ከተባለ የዘር ማጽዳት ጭፍጨፋ (ጀኖሳይድ) ነው።  ዜጎች በቀያቸውና በአገራችው  አንደ ክፉ አውሬ በስለት ተጨፍጭፈው እየተገደሉ ነው።  እየተፈጸመ ያለው ድርጊት በትክክል በሩዋንዳ ከተፈጸመው የዘር ማጽዳት ጭፍጨፋጋር ተመሳሳይ ነው። ልይነቱ የሟቾቹ ቁጥር መብዛትና ማነስ ብቻ ነው።

ከሰሞኑ የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮምያ የተደረገው ጭፍጨፋና ንብረት ማውደም ከአርቲስቱ ግድያ ጋር ኝኙነት ስላለው ሳይሆን ዜጎችን በማንነታቸው እንደክዚህ በፊቱ ሁሉ ለማቃት አመቺ አጋጣሚ በመፍጠር የተካሄደ ነው። በእርግጥም እነዚህ አራጆች ኦሮምን አይወክሉም። የኦሮምን ህዝብ አገር ቤት  በጋዜጠኝነት ሙያየ  ተዘዋውሬ በሰራሁበት ወቅት አውቀዋለሁ። ከወለጋ እስከ ሃረር፣ ከጅማ እስከ ቦረና በተዘዋወርሁባቸው ሁሉ የታዘብሁት የአሮምን አግላይነት ሳይሆን አቃፊነቱን ነው። ጭካኔውን ሳይሆን ርህራሄውን ነውንፉኘቱን ሳይሆን ለጋስነቱን ነው ። ታዲያ የሰውን ልጅ በአሰቃቂ ሁኔታ የሚገድል፣ አብሮት የኖረውን ወገኑን በስለት የሚያርድ፣ የገደለውን ዘቅዝቆ የሚሰቅል፣ አስከሬን አስሮ የሚጎትት ትውልድ ከይት መጣ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የቄሣርን ለቄሣር፣ የእግዜብሔርን ለእግዚያብሔር ስጡ! ባላገር የሚበላው ቢያጣ፣የሚከፍለው አያጣም!

ለአገዛዝ እንዲመቻቸው አለያም በአቋራጭ ወደስልጣን ለመውጣት ፖለቲከኞቻችን  በቀመሩት ስሌት መሰረት አንዱን በሌላኛው ላይ ለማስነሳት ሆን ብለው በጋቱት የተዛባ ታሪክ ላለፉት ሶስትና አራት አስርት አመታት በጥላቻ የተሞላ ትውልድ ተፈጥሯል። ከአንድነት ይልቅ ልዩነት፡ ከመቻቻል ይልቅ ቂምና ቁርሾ ለአዲሱ ትውልድ በስፋት እንዲሰብክ ተደርጓል። ዛሬ ህዋሃትና የአላማ አጋሮቻቸው በጠዋቱ የዘሩት ዘር ፍሬ እያፈራላቸው ይመስላል። በቀላኡ ለጥፋት የሚነሳና  ወደተፈለገው አቅጣጫ የሚነዳ ትውልድ ፈጥረዋል። ግደል ሲሉት የሚገድል። በራሱ የማይመራ ከንቱ ትውልድ።

ፖለቲከኞቹ የጥፋት አላማቸውን አሳክተዋል። ከመነሻውም ያቀዱት ይህን ነበር። የእርስ በርስ መጨራርስ። አንድ ፣ ሁለት፣ ሶስት እያልን ዛሬ ላይ ደርሰናል።  በህዝቦች መካከል ልዩነቶችን ማጉላት የፖለቲካ አጄንዳ ከሆነ ዋል አደር ብሏል። ለ27 አመታት አገሪቱን የገዛው ህዋሃት/ኢህአዴግ የአገዛዝ መሰረቱ ፌደራሊዝም በሚል ሽፋን የተለበጠ ልዩነትና መቃቃርን ነው። ይህም ለአገዛዙ ምቹ ሁኔታን ፈጥሮለታል። በንጹሃን ደም ላይ ተረማምደው አቋራጭ ስልጣን የሚፈልጉ አክራሪውች ደግሞ  ጠላት ፈጥረው ደጋፊ ለማብዛት ተጠቅመውበታል። ለውጥ መጣ ከተባለና ከልዩነት ይልቅ አንድነት እየተቀነቀነ ባለበት በአሁኑ ውቅት እንኳ የዘር ፖለቲከኞች ከመቸውም በበለጠ በወጣቱ ጭንቅላት የልዩነትና የጠላትነት ስሜት ሰብከዋል፣ ይባስ ብሎም የሰወችን የርስበርስ መገዳደልና መፈናቀል እንደ ስልት እየተጠቀሙበት ነው።

ዛሬ የሚታየው ዘርና ሃይማኖት ተኮር ጭፍጨፋ ለአመታት የዘር ፖሊቲካ አቀንቃኞች የደገሱት ነው። ምናልባትም ያሰቡትን ያክል ዉጤት ኣላመጣም ይሆናል። በዜጎች አይን ግን የዝር ፖለቲካው ልጓሙን በጥሶ ወደ ከፋ ጥፋት እየገሰገሰ ነው። የመንግስት የዘገየ ርምጃ  ለተፈጠረው ጥፋት አስተዋጾ አድርጓል።

በወገኑ ላይ ስለት የሰነዘሩና ንጹሃን ዜጎችን በግፍ የጨፈጨፉ ወጣቶችም ከህግ እንኳን ቢያመልጡ ከህሌናችው አያምልጡም። ለልጆቻቸውም የሚያስተላልፉት በንጹሃን ደም የጨቀየ ታሪክ ብቻ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአማራ ሕዝብ ላይ የተከፈተው ዘመቻ በአስቸኳይ ይቁም!!!

በርግጥ እነዙህ ወጣቶች የሚወክሉት ማህበረስብም  የለም ከወከሉም በወገን ደም ስልጣን ላይ ተረማምድው ስልጣን ላይ ለመፈናጠጥ የሚያልሙና ለጥፋት የላኳቸውን ፖለቲከኞችን ነው። የጥፋት አላማ እድሜዉ አጭር ነው። ውሎ ሲያድር በህዝብ ደም የሚነግዱ ፖለቲከኞች ሴራችው ይጋለጣል።  እስከዚያ ግን መንግስት መንግስት የሚያስብለውን ተግባር መፈጸም ይጠበቅበታል። ያ ካልሆነ ግን አገር አንደ አገር የመቀጠሏ ሁኔታ ጥያቄ ውስጥ ይገባል።

ፈጣሪ አገራችንን ይጠብቅ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share