የጽንፈኞች ጸሃይ እየጠለቀች ይሆን? – መሳይ መኮነን

/

አዲስ አበባና አዳማ። ኦቢኤንና ዋልታ። በዚህ ሳምንት ያወጧቸው ዘጋቢ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ምናልባትም ማርሽ ቀያሪ ሊሆኑ ይችላሉ ብሎ መገመት ስህተት አይደለም። ሁለቱም ፕሮግራሞች፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ኢትዮያን በዋናንትም የኦሮሚያን ክልል ዘቅዘው የያዙ፡ ሰላምና መረጋጋት ያሳጡ፡ በአንድም ይሁን በሌላ የፌደራሉን መንግስት አስወግዶ በተረኝነት ስካር ውስጥ የተዘፈቁ ጽንፈኛ ሃይሎችን ከአራት ኪሎ ቤተመንግስት ለማንገስ ግብ አድርገው ታላቁን ጥፋት አውጀው የተነሱ ሃይሎችን በጨረፍታ ያጋለጡ ናቸው። ባለፈው ረቡዕ ምሽት በኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ የተሰራጨውና የሰው ልጅ ጭካኔ እስከየት ጥግ ሊደርስ እንደሚችል የታየበት አስጨናቂ አሰቃቂ ትዕይንቶች የበዙበት ፊልም ለህዝብ ቀርቧል። ከዚያ ቀደም ብሎ በዋልታ ቴሌቪዥን በአንድ ባለሀብት ግፍ ተፈጸመብን ያሉ ግለሰቦች አቤቱታ እንዲሁም ባለሀብቱ የሀገርና የህዝብ ሀብትን ላይ የፈጸሙትን ታላቅ ኪሳራና ውድመት የሚተርክ ዘጋቢ ፊልም ተላልፏል። ሁለቱ ዘጋቢ ፊልሞች የተለያዩ ቢሆንም አንድ የፖለቲካ ፍትጊያ ፍጻሜ እየተቃረበ ለመሆኑ አመላካች ተደርገው በመታየት በአንድነት ሊነሱ የሚችሉ ናቸው።

በበኦቢኤን የተላለፈውና ኦነግ ሼኔ ከአምሳያ መዋቅሩ አባ ቶርቤ ጋር በመሆን ነጻ እናወጣሃለን ብለው በሚምሉለት የኦሮሞ ህዝብ ላይ የሰነዘሩት ታላቁ የጭካኔ በትር ከባህር ከሰፋው ጭካኔ በጭልፋ ተቀድቶ የሚታይበት ነው። ዓይን በሾለ ዘንግ ብረት ተጎልግልጉሎ እንዲወጣ የተደረገበት፡ እጅ በገጀራ የተቆረጠበት፡ ምላስና ጆሮ በስለት ተቀንጥሰው የተጣሉበት፡ ኢትዮጵያ ምድር ላይ ተፈጽሟል ተብሎ ለማመን የሚችግሩ እጅግ የሚዘገንኑ የጭካኔ ተግባራት የሚታዩበት ነው። ከዚህም የከፋ ለመናገርና በፊልም ለማሳየት የማይመከሩ አስነዋሪ ለሰው ልጅ ክብር ስንል የማንገልጻቸው የጭካኔ ድርጊቶችም አሉ ይላሉ በወለጋ የአንድ ዞን አስተዳዳሪ። የእነዚህ ጽንፈኛ ሃይሎች የፖለቲካ ትርክት መነሻው አጼ ሚኒሊክ በኦሮሞ ህዝብ ላይ ግፍ ፈጽመዋል የሚል ገሚሱ ከልብወለድ የውጭ ታሪክ ጸሃፊያን የተቀዳ አብዛኛው ደግሞ ህወሀት ምሽግ ውስጥ ከተጻፈ ታሪክ የሚመነጭ እንደሆነ ይታወቃል።

ባልተፈጸመ ታሪክ የፖለቲካ ፕሮግራም ጽፈው የተነሱ እነዚህ ሃይሎች አጼ ሚኒሊክ ፈጽመዋል ካሉት ጭካኔ የባሰ ነጻ እናወጣሃለን የሚሉትን ህዝብ እጅ ሲቆርጡ ዓይን ጎልጉለው ሲያወጡ ምላስና ጆሮ ሲቀነጥሱ አየን- በዘመናችን። በጉጂ በኦነግ ሸኔ ተፈጸመ የተባለው ደግሞ አስነዋሪም ጭምር ነው። ወንድ ልጅ ተደፈረ የሚለው አስደንጋጭ መረጃ በዘጋቢ ፊልሙ ላይ መስማት የሚሰቀጥጥ፡ ለጆሮ የሚያም ነው። ይህን የኦነግ ሸኔን ታላቅ ጭካኔ ምስክር ሳንፈልግ፡ የታሪክ መዝገቦች ሳናገላብጥ፡ ኖረንበት አየነው። ከእንግዲህ እነዚህ ሃይሎች አጼ ሚኒሊክን ብለው የሚሰብኩት ማንን ይሆን?

የዋልታው ዘጋቢ ፊልምም ከጽንፈኛው የፖለቲካ ሃይሎች ጀርባ የገንዘብ ደምስር ሆነው የተሰለፉ፡ ለእነዚህ ሃይሎች ለስንቅና ትጥቅ የሚሆን ገንዘብ የሚያቀርቡ፡ ለፕሮፖጋናዳ ማሽናቸው የምትታለብ ግት ላም ሆነው የሚያገለግሉ ባለሀብቶች በሀገርና ህዝብ ላይ እየፈጸሟቸው ያሉትን ግፎች አንደኛን ለቅምሻ በማቅረብ መጋረጃውን የገለጠ፡ መሽኮርሞሙን የገፈፈ ሆኖ ለህዝብ ተሰራጭቷል። ባለፉት ሁለት ዓመታት ከመሃል ኢትዮጵያና ከባህር ማዶ ስለአንድ ዓላማ የተሰለፉ የተለያዩ ሃይሎች ሀገር ሲያምሱ፡ የሀገር ተስፋን ሲያጨልም የሚናገራቸው የሚቆጣቸው ጠፍቶ ህዝብ ግፍ እየተጋተ ቆይቷል። የመንግስት ዝምታ ከጽንፈኛ ሃይሎች ሜዳውም ፈረሱም ተለቆላቸው እንዳሻቸው መጋለባቸው ኢትዮጵያ ወዴት እያመራች ነው የሚል ስጋትና ጭንቀት በብዙዎች ዘንድ ለውጡን ተከትሎ ጓዛቸውን ጠቅልለው በልብ የተቀመጡ ስሜቶች ናቸው። እስከመቼ ለሚለው ጥያቄ መልስ የሚሰጥ ሳይኖር ጥያቄው በጥያኤ እየተደረበ ለሁለት ዓመታት ዘለቀ። ምናልባት እነዚህ ሁለት ፊልሞች እንዲቀርቡና ህዝብ ፍርዱን እንዲሰጥ መወሰኑ በመንግስት በኩል ማርሽ ለመቀየር ታቅዶ ይሆን? የህግ የበላይነት ለማስከበር፡ ጽንፈኛ ሃይሎችን አደብ ለማስገዛት የፌደራሉም ሆነ የኦሮሚያ ክልል መንግስታት የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ተጠግተው ይሆን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማራ ክልል የወያኔ መቀበሪያ

ከሁለት ሳምንታት ወዲህ የኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ባለስልጣናት የሚሰጧቸው መግለጫዎች አንዳች ለውጥ ሊኖር እንደሚችል በግልጽ የሚያመላክቱ ናቸው። በዚሁ ሳምንት የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን የሰጠው ጠንከር ያለ ማስጠንቀቂያ በእርግጥም የጽንፈኞች ጸሀይ ልትጠልቅ መሆኗን የሚያሳይ ነው። ተከታታይ መግለጫዎቹ፡ ማስጠንቀቂያዎቹና ዘጋቢ ፊልሞቹ የሚነግሩን ነገር ቢኖር ነገሮች እንድነበሩ እንደማይቀጥሉ ነው። ከሳምንታት በፊት የኦሮሚያ ክልል የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ አቶ ጌታቸው ባልቻ በኤል ቲቪ ላይ ቀርበው በእርግጥም የሽፍቶቹ ጸሀይ እየጠለቀች ናት አሉ። ሁለት እግር አለኝ ብሎ ከጫካና ከከተማ መቆም ከእንግዲህ በትዕግስት የሚታለፍ አይደለም የሚለው የአቶ ጌታቸው መልዕክት እንደተለመደው ቃል ብቻ ሆኖ የሚቀር ይሆን? የብዙዎች ጥያቄ ነበር። በምክትል ፕሬዝዳንት ማዕረግ የማህበራዊ ጉዳይ አስተባባሪ አቶ አዲሱ አረጋ ቂጤሳ ህዝቡ ከሀገር ጥቅም በተቃራኒ ከቆሙት ሃይሎች ሊጠነቀቅ ይገባል ብለው በገለጹበት መልክዕታቸው ሶስት ቡድኖች ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ተናበው የሀገርን ሰላም በማደፍረስ የግብጽን የቤት ስራ እየሰሩ ያሉ መሆናቸውንም ለመጀምሪያ ጊዜ በግልጽ በአደባባይ መናገራቸው መንግስት ትዕግስቱ ለማለቁ ማሳይ ተደርጎ ሊወሰድ የሚችል ነው።

የህወሀትና የጽንፈኛ የኦሮሞ የፖለቲካ ሃይሎችና ግለሰቦች ሽርክና በእርግጥ ሰሞኑን የተጀመረ አይደለም። ባለፉት ሁለት ዓመታት ክንብንቡን ገልጦ በይፋ ጋብቻው ይፈጸም እንጂ ውስጥ ውስጡን ጥንስሱ ሲጠመቅ የከረመ ለመሆኑ በየጊዜው ሲነሳ ቆይቷል። ጋብቻው ያልተቀደሰ ቢሆን እንኳን ከመቀሌ እስከሞያሌ የህወሀትና የጽንፈኛ የኦሮሞ ፖለቲካ ሃይሎች እፍ ያለ ፍቅር ከኢትዮጵያ ፍርስራሽ ላይ የየመንደራቸውን ዘውድ ፍለጋ ላይ ግብ አስቀምጠው መንቀሳቀስ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። በተለይ የህወሀት ቡድን በሺዎች መስዋዕትነት በእጁ ያስገባውን የአራት ኪሎ ቤተመንግስትን በጥበብና በብልሃት ተነጥቆ ወደ መቀሌ ከተፈናቀለ በኋላ ከኦሮሞ ጽንፈኛ የፖለቲካ ሃይሎች ጋር ሳይነጋገሩ የሚግባቡ፡ ሳይወያዩ የሚናበቡ ስለአንድ ግብ ስለአንድ ሀገር መፍረስ የጋራ አጀንዳ ቀርጸው አንድ ላይ የተሰለፉ ለመሆናቸው አያሌ ማስረጃዎችን በማቅረብ መግለጽ ይቻላል።

መንግስት መሽኮርመሙን በገፈፈበት በሰሞንኛው ተከታታይ መግለጫው የህወሀትንና የጽንፈኛ ሃይሎችን ያልተቀደሰ ጋብቻ ገሃድ እያወጣው ነው። አቶ አዲሱ አረጋ ከሰሞኑ የማህበራዊ ሚዲያ የተቃውሞ ሰልፍ ጥሪ ጀርባ ሶስት ሃይሎች አሉ ብለው ከገለጹ በኋላ አንደኛውን በስም ጠቅሰው ወያኔ ይባላል ሲሉ አፍረጥርጠውታል። የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ም/ል ኮሚሽነር አቶ ግርማ ገላንም፡ የህወሀት አዛውንቶች ከመቀሌ አርፈው አልተቀመጡም፡ ከስንቅና ትጥቅ ድጋፍ ባሻገር ጀሌዎቻቸውን ለእኩይ ተግባር ከሸኔና አባቶርቤዎች ጋር አሰልፈዋል ሲሉ በግልጽ ተናግረዋል። ዘንድሮ አካፋን አካፋ ማለት መጀመሩ በእርግጥም አንድ ትልቅ እርምጃ ነው። ማድበስበሱ ሀገር እያጠፋ ነውና።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከዘረኛው ሰርዓት የሚጠቀሙ ኢህአዴግ ምን ያድርግህ? ሲሉ እንደ ሀገር ክህደት የሚቆጠር ወንጀል ነው! - በቶማስ ሰብሰቤ

ጽንፈኛ ሃይሉ ከአውስትራሊያ ለንደን ካናዳ አሜሪካና አዲስ አበባ ተጠላልፎ ከመቀሌ ጋር እየተናበበ በእርግማን ሌት ተቀን ተጠምዷል። የጋራ ታሪክ የለንም፡ ኢትዮጵያ የምትባል በአንድ ብሄር አምሳያ የተፈጠረች የነፈጠኛ ምናብ የሆነች ሀገር ካልጠፋች ሰላም አናገኝም፡ በልባችን የፈጠርናትን የገነት ምድር አንረግጣትም በሚል የቀን ህልም የሚንከራተተው የጽንፈኛው ካምፕ የመጨረሻውን የሞት ሽረት ትግል በይፋ ከፍቷል። የዚህ ካምፕ የፊት መስመር ተሰላፊዎች በሳምንት ለሰባት ቀናት በቀን ለ24ሰዓታት በኢንተርኔትና በሳተላይት በሚያሰራጯቸው የቴሌቪዥንና የሬዲዮ መድረኮች ላይ ተጥደዋል። መቀሌ፡ አክሱም፡ ሽሬ አዲግራት አድዋ፡ ከቤት ሳሎኑ ከሶፋው ላይ ቁጭ ብሎ እነዚህን ሰዎች በቴሌቪዥን መስኮት መመልከት የተለመደ ሆኗል። ህወሀቶችና ጽንፈኛ የኦሮሞ ፖለቲከኞች ስለአንድ ነገር በአንድ ጉዳይ ተጣምረዋል። ተናበው አመጽ ይጠምቃሉ። ተነጋግረው አጀንዳ ይቀርጻሉ።

በእርግጥ ኢትዮጵያ ካልፈረሰች፡ ከእንደገና ተጠፍጥፋ ካልተሰራች በቀር የኦሮሞ ህዝብ ትግል ለውጤት አይበቃም የሚል አደገኛ፡ በቀን ቅዠት ካልሆነ በቀር በእውን ሊሆን በማይችል የውሃ ቅዳ ውሃ መልስ ዥዋዥዌ ፖለቲካ ውስጥ እድሜ ዘመናቸውን እየፈጁ ያሉ የኦሮሞ ልሂቃንና የፖለቲካ ሃይሎች ተጉዘው የማይጨርሱትን መንገድ መቀጠላቸውን እያየን ነው። እነዚህ ሃይሎች አሁን ላይ ከያሉበት ተነቃንቀዋል። በሚዲያው መጠነ ሰፊ ዘመቻ ከፍተዋል። ከህውሀት ጋር ተናበው እየሰሩም ናቸው። የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ም/ኮሚሽነር አቶ ግርማ እንደውም ህወሀቶች በኦሮሚያ ክልል በአንዳድንድ ቦታዎች ከሚርመሰመሰው የሽፍታ ሃይል ጋር ተሰልፈው ሲተኩሱ እጅ ከፍንጅ መያዛቸውንም ይጠቅሳሉ። የሰሞኑ የእነዚህ ሃይሎች ርብርብ ወደ ቤተመንግስት የሚደረግ የመጨረሻ ሙከራ ይመስላል። ከመስከረም 25 በኋላ ሀገር ለማፍረስ የሚያስችል እቅድ ነድፈው በየአቅጣጫው ተነስተዋል። የመቀሌው ቡድን ትጥቁን ስንቁን አዘጋጅቷል። ነጭ ለባሾችን መልምሎ ለስምሪት አዘጋጅቷል። ህዝቡ ላይ የስነልቦና ጦርነት ለመክፈትና የአዲስ አበባውን መንግስት ለማዳከም በሚዲያውና ቀውስ በመፍጠር በርካታ ግንባሮችን ከፍቷል።

በእርግጥ አሁን ነገሮች ተቀይረዋል። የጽንፈኛው ካምፕ ኮምፓሱ እንደጠፋበትና ወጀብ እንደሚንጠው መርከብ ወዲህና ወዲያ እየተላተመ ነው። ወለጋንና ምዕራብ ጉጂን የቀውስ ቀጠና አድርጎ የከረመው ኦነግ በሸኔና በአባ ቶርቤ መዋቅሮቹ ላይ መንግስት ብርቱ ምት በማሳረፍ ተራ የሽፍታ ቡድን ደርጃ አውርዷቸው ለመጨረሻው ፍጻሜ እንዳስጠጋቸው እየተነገረ ነው። በቅርቡ ለኤል ቲቪ ቃለመጠይቅ የሰጡት የኦሮሚያ ክልል ኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ ጌታቸው ባልቻ ወለጋና ጉጂ ጫካ መሽጎ ሀገር እየበጠበጠ ያለው ሃይል ጸሀይ እየጠለቀችበት ነው፡ መንታ መንገድ ላይ ቆመው የምርጫ ቦርድ ሰነድ በአንድ እጅ፡ ጠመንጃ በሌላ እጅ የያዙት ኦነጎች ከእንግዲህ አንዱን የሚመርጡበት የመጨረሻ እድል ተሰጥቷቸዋል ሲሉ ገልጸዋል። የወለጋና ጉጂው ቀውስ ጭንቅላቱ አዲስ አበባ እንደሚገኝ ደርሰንበታል ነበር ያሉት አቶ ጌታቸው።

በጽንፈኛው ካምፕ የገባው መተረማመስ ፍጥነቱ እየጨመረ መጥቷል። ለኦሮሞ ህዝብ አንድ ሆነን እንታገላለን ብለው የተማማሉ ሶስት ድርጅቶች በወጉ አንድ የጋራ ስብሰባ እንኳን ሳያደርጉ፡ ቃለመሃላ የፈጸሙበት ፊርማ ቀለሙ ሳይደርቅ ብትንትናቸው መውጣቱ ትዝብት ላይ ጥሏቸዋል። ድሮም የስልጣን ጥማት እንጂ ለኦሮሞ ህዝብ የሚያፈሱት አንዲት ብልቃጥ ደም የላቸውም የሚል ትችት የሚቀርብባቸው እነዚህ የፖለቲካ ሃይሎች በወጉ ያላቆሙትን ጥምረታቸውን በስልጣን ድርሻ ተጣልተው በጠዋቱ መፋታታቸው ለኦሮሞ ህዝብ ተጨማሪ አንገት የሚያስደፋ ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሙስናው ጉዳይ - ከክንፉ አሰፋ (ጋዜጠኛ)

የህወሀትና የጽንፈኛ ካምፕ ሰሞኑን በተደጋጋሚ እየገጠመው ያለው ኪሳራ መስከረም 25 ከመድረሱ በፊት ያልተቀደሰው ጋብቻ ሊፈርስ ይሆን የሚል ጥያቄን አጭሯል። በአብዛኛው የኦሮሞ ወጣቶችና በፖለቲካ የነቃ ተሳትፎ እያደረገ ባለው የማህበረሰብ ክፍል ዘንድ የእነዚህ ሃይሎች አካሄድ ውግዘት እየገጠመው መጥቷል። በተለይም የጽንፈኛውን የኦሮሞ ካምፕ በገንዘብ በመደገፍ የሚታወቁ ባለሀብቶች ሰልፋቸውን አስተካክለው ከቤተመንግስቱ ቡድን ጋር አብረው ለመስራት መወሰናቸው በጭምጭምታ ደረጃ መረጃው ሾልኮ ከወጣ በኋላ ነገሮች በፍጥነት መቀያየራቸውን እየታዘብ ነው። አንዳንዶቹ የጽንፈኛው ካምፕ የፋይናንስ ምንጭ የሆኑ ባለሀብቶችም በህግ የሚጠየቁበት የወንጀል ፋይል እየጠበቃቸው መሆኑ ጊዜ ከማን ጋር እንደሆነች በግልጽ የታየበት ነው ማለት ይቻላል።

የገንዘብ ምንጫቸው አደጋ ላይ የወደቀባቸው ሃይሎች ከዋልታ ዘጋቢ ፊልም በኋላ ለቅሶ ተቀምጠዋል። የሚያልቧት ላም አንገት ላይ ገመድ የሚጠልቅ መሆኑ ከምን ጊዜውም በላይ ተገልጦላቸዋል። ወላጅ አልባ ሆነው እንዳይቀሩ ከወዲሁ በስጋት እየተናጡ ነው። በእርግጥ ህወሀቶችና የጽንፈኛው ካምፕ ጊዜ እየከዳቸው፡ አቅም እያነሳቸ፡ ትንፋሽ እያጠራቸው ቢመጣም የሞት ሞታቸውን የመጨረሻ እድላቸውን ለመሞከር ተዘጋጅተዋል። ለመስከረም 25 ከወዲሁ ቀጠሮ ይዘዋል። ከወዲሁ የሚዲያውን ጦርነት አፋፍመዋል። መቀሌ፡ ዋሽንግተን ዲስ፡ ለንደን፡ አውስትራሊያ፡ አዲስ አበባ ያሉ ሚዲያዎቻቸው የ24 ሰዓታት የሙሉ ጊዜ ዘመቻ ከፍተዋል። ህዝብ መንግስት ላይ እንዲያምጽና በህዝብ እልቂት ቤተመንግስት ለመግባት በፊት ለፊት መጥተዋል።

እነዚህ ሃይሎች ከተሳካላቸውና በለስ ከቀናቸው ኢትዮጵያን አፍርሶ በኮንፌዴሬሽን ግንኙነት ለጥቂት ጊዜ አብረው የሚቆዩበት በሂደት ደግሞ የየሰፈራቸውን መንግስት መስርተው ምስራቅ አፍሪካን የለየለት የብጥብጥ ቀጠና ለማድረግ እንደሆነ ከማንም የተሰወረ አይደለም። ይህ የመሆን እድሉ ግመል በመርፌ ቀዳዳ የመሽልክ ያህል ጠባብ ቢሆንም በተስፋ መቁረጥ በሚወስዱት የአጥፍቶ መጥፋት እርምጃ ትተውየሚያልፉት ጠባሳ በቀላሉ የሚታይ ሊሆን አይገባም። ከእነዚህ ሃይሎች ጥምረት የኢትዮጵያ ውድቀት እንጂ ትንሳዔ አይገኝም።

መንግስት ቆርጬአለሁ ብሏል። የኦቢኤንና የዋልታ ዘጋቢ ፊልሞች የሚነግሩን ብዙ ነገሮች አሉ። ያለምክንያት እነዚህ ፊልሞች አልታዩም። ጊዜና ወቅት ጠብቀው የቀረቡ በመሆናቸው ቀጣዮቹ የመንግስት እርምጃዎ ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ መገመት የሚከብድ አይሆንም። የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ማስጠንቀቂያም የጽንፈኞች ጀንበር ከወዲህ ማዘቅዘቅ መጀመሯን እንድናምን የሚያደርገን ነው። አዎን።የኢትዮጵያ ህዝብ ትከሻው ዝሏል። ጦርነት የሚሸከምበት ጫንቃው ደክሟል። የመንግስት ትዕግስት ማለቁን በተግባር ማየት ይፈልጋል። አቶ ጌታቸው ባልቻ እንዳሉት የማይጨረስ ስራ አልተጀመረም። ያልተቀደሰው ጋብቻ ፈርሶ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ሰላምና ደህንነታቸው የሚረጋገጥበት የቤት ስራ የመንግስት ቀዳሚ አጀንዳ መሆን ይገባዋል። የግብጽንም ረጅም እጅ መቁረጥ የሚቻለው ባልተቀደሰው ጋብቻ ላይ መንግስት በሚወስደው ቆራጥ እርምጃ ነው።

1 Comment

  1. ወንድሜ መሳይ፣
    የጽንፈኞች ከምትል’የከሀዲዎች ጸሃይ’ ብትል በትክክል ይገልጻቸዋል።
    በኣለም ላይ ከሀዲዎች፣ ባንዳዎች ባንድ ሀገር ላይ ያለ ከልካይ ሲቀልዱ እንደ እኛ ሀገር ታይቶ የሚታወቅ ያለ ኣይመስለኝም።የሚታየው ፖለቲካ ሳይሆን ሀገር ብተና ነው ።
    ታሪካችንን በመቶ ኣመት ገድበው መስተጋብራችንን ሲያንኩዋስሱ፣ ለኢትዮጵያ ሳይሆን ለጥቁር ኣፍሪካ ኮክብ የሆኑትን መሪያችንን ሲያዋርዱ ዝም ኣልናቸው፣ ያስተሳሰረችንን ባንዲራችንን ጥለው እራፊ ጨርቅ ሲያውለበልቡ ኣይተን ኣለፍን ፣ ለምእተ ኣመታት እንደ ግሉ ያጣበቀችንን ፣ ፊደል ያስቆጠረቻቸውን ሃይማኖታችንን ሲያረክሱ ጆሮኣችንን ደፈን፣ እስልምናንም እንዲሁ። ሰሜን ከደቡቡ፣ ምስራቅን ከምራብ እንደ ድልድይ ሆና ያገለለችንን በሁሉም ተሳትፎ የዳበረችውን የኣማራ ሳይሆን ሀገራዊ ኣማሪኛችንን (ኢትዮጵያዊ ቁዋንቁዋችንን) እንድትጫጭ ኣርገው ወደ ባቢሎን ዘመን ሲያመጡን በታዛቢነት ኣለፍነው፣ኣረ ስንቱ???!! ጎበዝ ምን ቀረን ከኢትዮጵያዊነት ፧ ሁሉንም ወሰዱብን እኮ።ቀፎ ኣችንን ኣስቀርተውናል።
    We have to reverse this situation right now . No time to lose .

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share