“ከመልካም ሽቶ መልካም ስም ይሻላል” – በሰሎሞን ዳኞ

የማንም ፖለቲካ ፓርቲ አባል አይደለሁም፡፡ ነገር ግን ማንም ይሁን ለአገራችን የሚጠቅም ነገር ሲሠራ ስመለከት ነፍሴ ትረካለች፡፡ ለምሳሌ ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዓብይ አሕመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ ጀምሮ የተገኙትን በርካታ ለውጦች እንደማንኛውም አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ አደንቃለሁ፡፡

ይህን ጽሑፍ እንዳዘጋጅ ያነሳሳኝ ሰሞኑን ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ አገር አቀፍ ፓርቲ ሆኖ በአዲስ መልክ በመዋቀር ላይ ስለመሆኑና ወደ 30 ዓመታት ገደማ ሲጠቀምበት የነበረውን ስሙን “ብልጽግና ፓርቲ” በሚል እንደሚተካ የሰማሁት ዜና ነው፡፡ ውሳኔውን “እንደ ትንሽ ትል” ሆኘ ስመለከተው የሚያስደስት እንጅ የሚያስከፋ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡

ኢህአዴግ መልካም ስም እንደሌለው አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነው፡፡ የፓርቲው ፈጣሪዎችና መሪዎች ይህንና ያን ሠራን እያሉ ተቀባይነት ለማግኘት ያልፈነቀሉት ድንጋይ ባይኖርም አብላጫው ሕዝብ ኢህአዴግን የሚስለው ግን በጎሳ የሚከፋፍል፣ የአገር ስሜት የሚገድል፣ ሙሰኛ፣አድሎአዊ፣ የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፎ የሚሰጥ፣ ዜጎች በፍርድ ቤቶች ላይ እምነት እንዳይኖራቸው የሚያደርግ፣ ዘግናኝ ኢሰብአዊ ድርጊቶችን የሚፈጽም፣ ወዘተ አድርጎ ነው፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለ እንኳን ተግባሩ ስሙም ከተጠላ ቆይቷል፡፡ በሕዝቡ ቋንቋ ኢህአዴግ ማለት ወያኔ ነው ወያኔ ማለት ደግሞ ኢህአዴግ ነው፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ አንድ ጸሐፊ፡-

የወያኔ ልማት ሄደ ገሠገሠ

ጎሳውን ከጎሳ እያተራመሰ

መብራት እያጠፋ

ቤት እያፈረሰ፡፡

ሲል ያቀረባት ግጥም የሕዝቡን እይታና የውስጥ ስሜት በትክክል ትገልጻለች፡፡

ኢህአዴግ መንገድ አልሠራምን? አዎ ሠርቷል፡፡ ሕንፃዎችን አልገነባምን? ብዙ ገንብቷል፡፡ ነገር ግን ከገነባው ይልቅ ያፈረሰው ሚዛን ስለደፋ ልብ ውስጥ ሊገባ አልቻለም፡፡ በአጠቃላይ ፓርቲው አገሪቱ አሁን ለምትገኝበት ምስቅልቅል በመዳረጉ ወርቅ ቢያነጥፍም የሚያምነው የለም፡፡ ይህም “ከመልካም ሽቶ መልካም ስም ይሻላል” የሚለውን የመጽሐፍ ቃል የሚያረጋግጥ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኦነግ ምክንያት የታሰሩ የኦሮሞ ወጣቶችም ይፈቱ | ቡልቻ ደመቅሳ

ዶ/ር ዓብይን ሕዝቡ በነቂስ አደባባይ ወጥቶ ድጋፉን የሰጣቸው የፍቅር፣ የይቅርታና የመደመር ፍልስፍና ይዘው በመምጣታቸው እንጅ ኢህአዴግ በመሆናቸው እንዳልሆነ ማንም የሚያውቀው ነው፡፡ በእኔ እምነት ለእሳቸው ራዕይና ባጠቃላይ የለውጥ ኃይሉ ለአገሪቱ እየተመኘ ላለው ዕድገት ኢህአዴግ አይመጥንም፡፡ አዲስ የወይን ጠጅን በአሮጌ አቁማዳ እንደማስቀመጥ ይቆጠራል፡፡ ስለዚህ ነገሮችን ከነባራዊ ሁኔታዎችና ከወቅቱ ጋር እያስማሙ መሄድ ብልህነት ስለሆነ እየተወሰደ ያለው ርምጃ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ እንዲያውም ዘግይቷል ባይ ነኝ፡፡

ኢህአዴግ በብልጽግና ፓርቲ መተካቱ ብቻ ሳይሆን ስያሜውም በጣም ደስ የሚል ነው፡፡ ተስፋ የሚፈነጥቅ ድንቅ ስም ከመሆኑም በላይ እጥር ምጥን ያለ ስለሆነ በሕዝቡ ዘንድ በቀላሉ ይለመዳል፡፡ ብዙ ወላጆች ለልጆቻቸው ስም ለማውጣት ብዙ ሲጨነቁና ሲጠበቡ የሚታዩት ስም ያለውን ፋይዳ ስለሚገነዘቡ ነው፡፡ እንዲሁ ያገኙትን ሁሉ እያነሱ ልጆቻቸው ላይ አይለጥፉም፡፡ የብልጽግና ፓርቲም ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት ተወዳጅ ስያሜ ይዞ ብቅ በማለቱ የፓርቲው ሰዎች ሊኮሩ ይገባል፡፡

በርካታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለአዲሱ ፓርቲ ድጋፋቸውን ከመግለጽ አልፈው አብረው ለመዋሃድ መወሰናቸውን እያሳወቁ ነው፡፡ ይሄ በራሱ ትልቅ ድል ነው፡፡ ሌሎች ተመሳሳይ ዓላማ ያላቸው ተፎካካሪ ፓርቲዎችም እንዲሁ ቢያደርጉ የአገራችንን ትንሣኤ ሊያፋጥን ይችላል፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ከመቶ በላይ ፓርቲ ሕዝቡን ግራ ከማጋባት ውጭ የሚፈይደው ነገር የለም፡፡

ብልጽግና ፓርቲን የደገፉ እንዳሉ ሁሉ የነቀፉ አልጠፉም፡፡ በተለይ ህወሓት አምርሮ ተቃውሟል፡፡ እዚህ ላይ መታወቅ ያለበት ይህ ድርጅት ሥልጣኑን በእነ ዶ/ር ዓብይ ቡድን ድንገት ከተነጠቀ ጀምሮ በድንጋጤ፣ በብስጭትና በሐዘን ውስጥ ያለ መሆኑን ነው፡፡ ይህን የሚያሳብቁበት በተለያዩ ጊዜያት ያወጣቸው የነበሩት መግለጫዎችና በእልህ ሲወስዳቸው የነበሩት ርምጃዎች ናቸው፡፡ እናም ቢቃወም የሚገርም አይሆንም፡፡ የሚገርመው ግን አምስቱ የሐዘን (Grief) ደረጃዎች የሚባሉትን ገና አለማለፉ ነው፡፡ ህወሓት “እኔ ከሞትሁ ሰርዶ አይብቀል” በሚል ፈሊጥ ከመዳከር ይልቅ ሽንፈቱን ተቀብሎና የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰጠውን ይቅርታ አክብሮ በአዲስ መንፈስ አገሩን መካስ በተገባው ነበር፡፡ ከወደቁ ወዲያ መንፈራገጥ መላላጥ እንጅ ሌላ የሚያተርፈው ነገር የለም፡፡ ምናልባት በኢትዮጵያዊነቱ ኩሩ የሆነውን የትግራይን ሕዝብ ከተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በዘላቂነት ለመነጠል አስቦ ከሆነ የሚሳካለት አይመስለኝም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ወይስ አማራ ጨፍጫፊ መንጋ (አጨመ)

ሌላው አዲሱን ፓርቲ ተቃውመዋል እየተባለ የሚወራባቸው አቶ ለማ መገርሳ ናቸው፡፡ ለውጡ አንዲመጣ ብዙ ከለፉት ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት አቶ ለማ በዚህ እጅግ ወሳኝ ወቅት ከሚያፈገፍጉ ይልቅ “አብረው ያቦኩትን አብረው ቢጋግሩት” ጥሩ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡ በሌላ በኩል ነገሩ ለበጎ ሊሆን ይችላል፡፡ ፈረንጆች “What got you here will not get you there” የሚል አባባል አላቸው፡፡ በግርድፉ ሲተረጎም “አሁን ለደረስክበት ስኬት ያበቁህ ነገሮች ወደፊት ልትደርስበት ወደምታልመው ግብ አያደርሱህም” እንደ ማለት ነው፡፡ ምናልባት አቶ ለማ የተጠሩት ወይም አስፈላጊ የነበሩት እስከ አሁኗ ደቂቃ ድረስ ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡ የቀሩትን የትግል ምዕራፎች ሌሎች ጥሪ ያላቸው ዜጎች የማያስቀጥሉበት ምክንያት የለም፡፡

ወደፊት የሚሆነውን ለመተንበይ አስቸጋሪ ነው፡፡ የሩህሩሁ ጌታ ፈቃድና ረድኤት ተጨምሮበት የብልጽግና ፓርቲ አገራችንን እንደ ስሙ በከፍታ ማማ ላይ ዳግም ያቆማት ዘንድ ምኞቴ ነው፡፡ እስከዚያ ድረስ ግን ሥርዓት አልበኛ አክራሪ ብሔርተኞች እያደረሱት ያለውን ጥፋት መንግሥት ከሁሉም ቅድሚያ ሰጥቶ ማስቆም ይኖርበታል፡፡ ሰላም ከሌለ የታሰበው ዓላማ ግቡን ሊመታ አይችልምና፡፡   ቸር ያሰማን!

solotena@yahoo.com

Share