ሃይማኖት፤ እምነትና ፖለቲካ፤ ሕዝብ አደናጋሪ የዘመኑ ውዥንብር

በገ/ክርስቶስ ዓባይ
መስከረም 10 ቀን 2012 ዓ/ም

ሃይማኖት ለሰብአዊ ፍጡር የተሰጠ የሕልውና መገለጫ፤ የሕይወት ተስፋና ከአምላክ ጋር የሚያገናኝ፤ በዓይን የማይታይ ግን በመንፈስ የተዘረጋ ድልድይ ነው። ሃይማኖት ከአምላክ በሚሰጥ ልዩ ፀጋ በተለያዩ እምነቶች ይገለጻል። ጥንት፤ ዓለም እምነት አልባ (አረማዊ) በነበረችበት ዘመን፤ ኢትዮጵያውያን በሕገ ልቡና ፈጣሪ እንዳለ በመረዳት ከክፉ ሥራ በመራቅና በጎ ተግባርን በመሥራት ፈጣሪያቸውን ያመልኩ እንደነበር ታሪክ ይነግረናል። ይሁንና ከፈጣሪው ጋር ለመነጋገር የበቃውና የተጨባጭ እምነት አባት መሆኑ የሚነገርለት ታላቁ አባት አብርሃም ነው። አብርሃም የተወለደው ዓለም በጣዖት አምልኮ ተዘፍቃ በነበረበት ወቅት ሲሆን፤ አባቱ ታራ ደግሞ የታወቀ ጣዖት ጠራቢ እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል።

ታዲያ ሦስት ጣኦቶችን ገበያ ወስዶ እንዲሸጥ በአባቱ ታዞ ሄዶ ሳለ፤ ሁለቱን ሽጦ ሦስተኛው ሳይሸጥ በመቅረቱ ያንን ተሸክሞ ሲመለስ ነበር ከፈጣሪው ጋር የተገናኘው። አብርሃም መጀምሪያውኑም አባቱ በሚጠርበው በጣዖት አያምንም ነበር። ሲሸጥ እንኳ ዓይን እያለው የማያይ፤ እጅ እያለው የማጨብጥ፤ እግር እያለው የማይሄድ፤አፍ እያለው የማይናገር አምላክ የሚገዛ በማለት እያሾፈ ነበር የሚሸጠው። በሚገዙትም ሰዎች እጅግ በጣም ይደነቅና ይገረም ነበር።

በኋላም ከዋለበት ገበያ ሲመለስ ስለደከመው፤የተሸከመውን ጣዖት አውርዶ እባክህ እርቦኛልና ምግብ ስጠኝ በማለት ጠየቀው፤ ምንም መልስ አላገኘምና እንደገና ተሸክሞ ጥቂት ከተጓዘ በኋላ አሁንም አውርዶ ኧረ ውሀ ጠማኝ እባክህ ውሀ አጠጣኝ፤ በማለት ጣዖቱን ጠየቀው ምንም መልስ አላገኘም። አሁንም እንደገና ተሸክሞ ትንሽ ከተጓዘ በኋላ ስለደከመው አውርዶ፤ ምግብ ጠየቅሁህ አልሰጠኸኝም፤ ውሀም ለመንኩህ እምቢ አልክ፤ ስለዚህ ደክሞኛልና እግር ስላለህ እባክህ እራስህን ችለህ ተራመድ በማለት ጣዕዎቱን ጠየቀው፤ነገር ግን ምንም መልስ አላገኘም።

በዚህ ጊዜ ነበር በጣም በመናደድ ከአለት ላይ አጋድሞ በድንጋይ  እየቀጠቀጠ ዱቄት ያደረገው። ከዚያም፤አብርሃም በምን ባመልክ ይሻለኛል በማለት ይመራመር ጀመር። በወንዝ አለ፤ ወንዙ በክረምት ይሞላና በበጋ ይደርቃል፤ በዛፍ አለ፤ ዛፍም እንዲሁ ይደርቃል ቅጠሎችም በረገፉ ጊዜ ግርማ ሞገሱ ይገፈፋል፤ እያለ የተለያዩ አማራጮችን አያሰበ ሲሄድ፤ የቀትር ፀሐይ በርትታ ስለነበር፤ በፀሐይ ላምልክ እያለ ሲያስብ፤ ፀሐይም በጨለማ እንደምትረታ በመገንዘብ ላይ እንዳለ ሙቀቷ እጅግ በጣም ኃይለኛ እየሆነ መጣ።

ወዲያው አንድ ሐሳብ ብልጭ አለለትና ወደ ሰማይ አንጋጦ ‘አምላከ ፀሐይ እባክህን አናግረኝ!’ በማለት ጮኸ። ከዚያም አብርሃም! አብርሃም! በማለት ፈጣሪው አናገረው። ቀጥሎም “ከዚህች አንተ ከምትኖርባት አገር በአስቸኳይ ተለይተህ ውጣ! ማርና ወተት ወደሚፈልቅባት ወደ ከንዓን ሂድ፤ በዚያም ዘርህን እንደ ሰማይ ከዋክብት እንደምድር አሸዋም አበዛዋለሁ። አሕዛብ ሁሉ በአንተ ይባረካሉ!” በማለት ቃል ኪዳን ገባለት (ዘፍ 12:1) ። አብርሃምም ምንም ሳይጠራጠር የፈጣሪውን ትዕዛዝ በማክበር በእምነት ፈጸመ።

አብርሃም ከሚስቱ ከሣራ ይስሐቅን ወለደ፤ (ሰዎች ሲጋቡ የአብርሃምና የሣራ ጋብቻ ያድርግላችሁ የሚባለው ከዚህ የተነሳ ነው፤ ምክንያቱም ጥልቅ ነው ራሱን የቻለ አስደማሚ ታሪክ አለው) ይስሐቅም ርብቃን አግብቶ ኤሳውን እና ያዕቆብን መንታ ልጆች ወለደ። ኤሳው እንደ አባቱ ገበሬ ሲሆን ያዕቆብ ደግሞ በቤት አካባቢ በጎች ይጠብቅ ነበር። እናቱንም በቅርብ ሆኖ ይረዳ ነበር። ከዚያም አብርሃም ሊጠይቃቸው በሄደ ቁጥር የሚያገኘው ያዕቆብን ነበርና ባረከው (ዘፍ 28፡3-4) ። ለርብቃም ‘ስሜ የሚጠራው በዚህ ልጅ ነውና ያዕቆብን ተንከባከቢው’ አላት። እሷም አብርሃም ነቢይ መሆኑን ታውቅ ስለነበር ይህንን ቃል በምስጢር ይዛ ትሳሳለት ነበር። አብርሃምም እንደተናገረው ያዕቆብ የአሥራ ሁለቱ ነገደ እሥራኤል አባት ለመሆን በቅቷል።

እንግዲህ እምነት ከዚህ ይጀምራል። እሥራኤላዊያን ከአባታቸው ከአብርሃም የወረሱትን እምነት አክብረው ያዙ። ቀጥሎም በብሉይ ኪዳን እንደተገለጸው በዚሁ እምነት ያደገውና የጸናው ሙሴ ከፈጣሪው ጋር የመነጋገርን ዕድል ከማግኘቱም በላይ የእምነት ቃል ኪዳን የሆነውን ጽላት ተረክቧል (ዘጸአት 25:20) ። ይህም ጽላት በፈቃደ እግዚአብሔር በቀዳማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ወደ ኢትዮጵያ መምጣቱ ይታወቃል።

ጽላተ ሙሴ (ታቦተ ሕጉ) ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ ብሉይ ኪዳን አብሮ እንደመጣ ማስተዋል ተገቢ ነው። እንግዲህ ኢትዮጵያውያን በኦሪት ሕግ መሠረት ፈጣሪያቸውን እያመለኩ የቆዩ ለመሆናቸው ዋነኛ ማስረጃ ሲሆን፤ ንግሥተ ሳባ የሰሎሞንን ጥበብ ለማየት በሔደችበት ወቅት ከንጉሡ የተሰጣት መሬት ስለነበር ወደ ኢትዮጵያ ስትመለስ ጠባቂዎችን ወክላ መመለሷን ታሪክ ያስረዳል (ነገሥት 10:1-26) ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኢትዮጵያውያን ንጉሥ ሰሎሞን ያሠራውን ቤተ መቅደስ ለመጎብኘት ይመላለሱም ነበር።

ከዚህ የምንረዳው አንድ ትልቅ ዓቢይ ነገር አለ። ይኸውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜ ከሦስቱ ጠቢባን (ሰብአ ሰገል) መካከል አንዱ ኢትዮጵያዊ እንደነበረ ዓለም ያረጋገጠው ሐቅ ነው (ማቴ 2:1-16)። እንግዲህ እነዚህን እውነታዎች በጥሞና ስንመረምር፤ አሁንም ሌላ እውነት ላይ ያደርሰናል። ይኸውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያስተምርበት ወቅት ከአሥራ ሁለቱ ደቀመዛሙርት በተጨማሪ ብዙ ሺህ ተከታዮችና የጉባኤው ተሳታፊዎች እንደነበሩ መጽሐፍ ቅዱስ ይተርካል። ይህም ማለት በዚያ ጉባኤ ኢትዮጵያውያንም ታዳሚዎች እንደነበሩ መረዳት አይከብድም።

ነገር ግን ዓለም የሚገነዘበው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ሠረገላ ላይ ተቀምጦ ትንቢተ ኢሳያስን በማንበብ ላይ እንዳለ (ኢሳ 53፡7-8) መንፈስ ከደቀመዛሙርቱ አንዱ ወደ ሆነው ፊሊጶስ ወርዶ ጃንደረባውን እንዲገናኘው እንዳዘዘው ይናገራል። አሱም ከአስተማረው በኋላ ጃንደረባው እንደተጠመቀ ያትታል (የሐዋርያት ሥራ 8:27) ። ይሁን እንጂ የክርስትና እምነት ወደ ኢትዮጵያ የገባው ቀደም ብሎ እንደሆነ የሚያጠራጥር አይደለም። ይሁንና ሶሪያዊው ከሳቴ ብርሃን አቡነ ሰላማ (ፍሬምናጦስ) ፤ የመጀመሪያው ጳጳስ ሆኖ ከእስክንድሪያ ተሹሞ ከተመለሰ በኋላ የክርስትና ሃይማኖት በኢትዮጵያ በይፋ ተቀባይነት ማግኘቱ ተዘግቧል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ይድረስ ለጎንደር ሕዝብ

በኋላም እ.ኤ.አ በ612-13 ዓ/ም በአለው ዘመን የነቢዩ መሐመድ የቅርብ ቤተሰቦችና የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ቁራዮሽ በመባል የሚታወቁት አረመኔዎች፤ ጸረ እስልምና ሃይማኖት ኃይሎች ሊገድሏቸው ባሳደዷቸው ጊዜ መጠለያ ፍለጋ የመጡት ወደ ኢትዮጵያ ነበር። ከዚያን ጊዜም ጀምሮ የእስልምና ሃይማኖት ወደ ኢትዮጵያ መግባቱ ይታወቃል። እንግዲህ ከዚህ የምንረዳው፤ አንደኛ በሕገ ልቡና፤ ሁለተኛ በሕገ ኦሪት፤ ሦስተኛ በክርስትና ሃይማኖት፤ አራተኛ በእስልምና ሃይማኖት ፈጣሪዋን እያመለከች የምትገኝ ጥንታዊት አገር ኢትዮጵያ ብቻ መሆኗን አስረግጦ መናገር ይቻላል።

ምስጋና ለአያት ቅድመ አይቶቻችን ይሁንና ይህንን ታሪክ በራሳቸው ፊደልና ቋንቋ ከትበውልን አልፈዋል። ከዚያም እምነታቸው የአንድ ወቅት ብቻ ሆኖ እንዳይቀር በማሰብ ለዘለዓለም ለልጅ ልጅ እንዲተላላፍ ባህል እንዲሆን አድርገው ሥርዓት ተክለውልናል። በተጨማሪም እ.ኤ.አ ከ525-571 ዓ/ም የነበረው ቅዱስ ያሬድ የክርስትና ሃይማኖት የበለጠ እንዲጠናከር የሚያደርግ በዓለም ልዩ የሆነውን ጸዋትወ ዜማ ደርሶ አርፏል።

እ.ኤ.አ .እስከ 325 ዓ/ም ድረስ በዓለም አንድ የክርስትና ሃይማኖት ብቻ ነበረ። ከዚያ በኋላ ግን የካቶሊክ ሃይማኖት በመመሥረቱና የዶግማ ልዩነት በመከሰቱ ዓለም ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሁለት የክርስትና ሃይማኖት ተከፈለች። ይኸውም፤ የካቶሊክና የኦርቶዶክስ ክርስትና ሃይማኖት ተብለው ተለያዩ። ከዚያ በኋላ ከካቶሊክ እንደገና በጀርመናዊው ሉትር አማካይነት፤እ.ኤ አ.በ1531 ዓ/ም ሉተራን ቤተክርስቲያን፤ ቀጥሎም በእንግሊዙ ንጉሥ ሔንሪ 8ኛ አማካይነት እ.ኤ.አ በ1534 ዓ/ም የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ተመሠረተ። ከዚያም ምንም መቆሚያ የሌለው የተለያዩ የፕሮቴስታንት (ጴንጤ ቆስጤ) ሃይማኖቶች እንደ አሸን በየቦታው መከፈት ቀጠሉ።

የኦርቶዶክስ ሃይማኖት በቅዱስ ሲኖዶስ የሚመራና በፓትሪያርክ የሚተዳደር ሲሆን፤ የካቶሊክ እምነት ደግሞ በፖፕ (በጳጳስ) ሲመራ መንበሩም ቫቲካን ነው። ነገር ግን ከስሙ መረዳት እንደሚቻለው የፕሮቴስታንት (ተቃዋሚ) ሃይማኖት መመሪያቸውን በመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ በማድረግ፤ ምንም ዓይነት ማዕከላዊ አስተዳደር የለውም። ሁሉም በየቦታው ፓስተር ነን በሚሉ አፈ ጮሌዎች፤ የየራሳቸውን ስብስብ በመያዝ የጸሎት ቤት በመክፈት የዋሁን ሕዝብ በማታላል ይዘርፋሉ። ለዚህ ምንም ዓይነት ማስረጃ ማቅረብ አይጠበቅብንም። ልብ ያለው ልብ ይበል፤ በተለይ አገራችንን እያጠፉ ያሉት እንዲህ ዓይነት ጥራዝ ነጠቅ የፈረንጅ አስተሳሰብ አምላኪዎች ናቸው።

አስተምህሯቸውም ለሰሚው የሚገርም ነው። ቅድስተ ቅዱሳን፤ ቤዛዊት ዓለም፤የኢየሱስ ክርስቶስን እናት እመቤታችን ድንግል ማርያምን ጨምሮ፤ ለቅዱሳን፤ ፃድቃንና፤ሰማዕታት፤ የሚገባቸውን ከብር አይሰጡም። ይልቁንም ፓስተር ተብየዎች እራሳቸውን ከመጠን በላይ በማግዘፍ ልጸልይላችሁ እያሉ የዋሁን ሕዝብ በማታለል የግል ፍላጎታቸውን ይፈጽሙባቸዋል። መሠረታቸው ከዚህ ዓለም መንግሥት ጋር የተገናኘም ስለሆነ መንፈሳዊ ሥራ ሳይሆን ዓለማዊ ተግባራትን በመሥራት የሰውን ሕይወት ያበላሻሉ፤ የሞቀ የደመቀ ትዳራቸውን ያፈርሳሉ። በተለይ አብዛኛው የዘመኑ የሃይማኖት ድርጅቶች የፖለቲካ ዓላማ ማራመጃ እንዲሆኑ ተብለው የተቀረጹ ስለሆኑ ስውር ካድሬዎች በጥንታዊውና ጠንካራው ሃይማኖት ድርጅቶች ውስጥ ሠርገው በመግባት በተለያዩ ሰንካላ ምክንያቶች የየዋሁን አማኝ ልብ በማሸፈት አንድነታቸውን መክፈልና ማዳከም ይሆናል።

ለምሳሌ ጆሆቫ ዊትነስ የተባለው ሃይማኖት በአሜሪካው የስለላ ድርጅት አማካይነት የተጀመረ እንደሆነ ይነገራል። ይኸው ሃይማኖት በአገራችን በተለይም በኤርትራ የተጀመረውና የተስፋፋው በ1950ዎቹ ዓ/ም መጨረሻ አካባቢ፤ አሜሪካውያን በእሥራኤልና የአረቦች ጦርነት ወቅት አሥመራ በነበረ በቃኘው እስቴሽን በነበሩበት ወቅት እንደሆነ በሕይወት ያሉ እማኞች ይመሰክራሉ። በተለይም ፕሪዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የዚህን ሃይማኖት አመጣጥ ጠንቅቀው ስለሚያውቁ ለጆሆቫ ዊትነስ ተከታዮች እውቅና እንደነፈጉ ውስጥ አዋቂዎች ይተነትናሉ።

ከዚህም በተጨማሪ የአውሮፓ ቅኝ ገዥዎች ታዳጊ አገሮችን ለመሰለል አስቀድመው ሚሲዮናውያን ሰላዮችን በሃይማኖት ስም በመላክ ያሰልሉ አንደነበር ይታወቃል። ነገር ግን እነዚህ ሚሲዮናዊያን ጥልቅ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት አልነበራቸውም። ምንም እንኳ ጺማቸውን ቢያሳድጉም፤ ካባ ቢለብሱም፤ መስቀል ቢያነግቱም፤መጽሐፍ ቅዱስ ቢሸከሙም፤ እነርሱ ግን የሚሊታሪ መኮንኖች ነበሩ።

ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር የተጋጩት፤ በወቅቱ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡት የእንግሊዝ ሰላዮችን፤ ‘ለምን ጉዳይ መጣችሁ? ምንስ ይዛችሁ መጣችሁ?’ ተብለው ሲጠየቁ የሚሰጡት መልስ ‘የእግዚአብሔርን ቃል ለማስተማር ነው፤ ያመጣነውም መጽሐፍ ቅዱስ ነው’ በማለት እንደመለሱ ታሪክ ያስተምረናል። ንጉሡም ‘እኛ ብዙ ሊቃውንት አሉን፤ መጽሐፍ ቅዱስንም እዚሁ እናጽፋለን፤ ይልቅስ የእኛን ወዳጅነት የምትፈልጉ ከሆነ የዕደ ጥበብ አዋቂዎችና የመሥሪያ ዕቃ አምጡና ሕዝቤን አስተምሩልኝ’ ማለታቸው ይነገራል። ነገር ግን የጠየቁት ሳይፈጸም ሰላዮች ግን ከየአቅጣጫው ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸው እየጨመረ ስለመጣ እንዲታሠሩ ማዘዛቸው ይታወቃል።

በጥንታዊነቷ፤በታሪኳ፤ በቋንቋዋና በሃይማኖቷ ጥንካሬ፤ የሚቀኑባትን ኢትዮጵያን እንደ ዩጎዛቪያ ከምድረ ገጽ ለማጥፋት፤ ሕዝቦቿን ለመበተንና ሃይማኖቷን ለመበረዝ የሚደረገው ዘመቻ ከቀን ወደቀን እያደገና እየተጠናከረ መጥቷል። በ16ኛው ክፍለ ዘመን ሃይማኖቷን አንደኛ፤ የቱርክ ኦቶማን በግራኝ አህመድ አማካይነት እ.ኤ.አ ከ1526-1555 ዓ/ም ወደ እስልምና፤በሁለትኛ ደረጃ ደግሞ አሮፓውያንም በአፄ ሱስንዮስ ዘመነ መንግሥት እ.ኤ.አ ከ1606-1632 ዓ/ም በአለው ጊዜ ወደ ካቶሊክ ለመቀየር ተሞክሮ እንደነበር ታሪክ መዝግቦት ይገኛል። ነገር ግን በወቅቱ በነበሩ አባቶቻችን አርቆ አስተዋይነትና ጥንካሬ የሁለቱም ኃይሎች ሙከራ አልተሳካም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ተራ ኢትዮጵያዊ መሆናችንን አንናቀው ! ግርማ ካሳ

ከዚያም ወዲህ በተለይ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ኢትዮጵያ ለጥንቱ ሃይማኖት ትኩረት ባለመስጠትና፤ በዘመኑ ሥልጣኔ በመማረክ ወደ አስኳላ ትምህርት ቤት ዘው ብላ በመግባቷ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የተወለደው ትውልድ ወላጆቹን የማያከብር፤ አገሩን የማይወድ፤ እና ሃይማኖቱን የሚንቅ እየሆነ መጣ።

አሁን አገራችንን እያመሷት ያሉት የዚያ ትውልድ ዓባላት ናቸው። የራሳቸውን በመናቅ የውጭውን ሃይማኖት እያመለኩ ይገኛሉ። ፈረንጅ አምላኪው ትውልድ፤ አገሩን በገንዘብ የሚሸጥ፤ ወገኑን የሚከዳ፤ ብኩን ትውልድ ሆነ። በተጨማሪም በቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት አሁንም እንደገና ሚሲዮኖች አገልግሎት እንዲሰጡ በጠየቁ ጊዜ ትምህርት ቤት ባልተቋቋመባቸው አካባቢዎች ገብተው እንዲሠሩ ይፈቅድላቸው ነበር። ከዚህም የተነሳ በሚሲዮን ትምህርት ቤት እየተማሩ ያደጉት ሰዎች የአገራቸውን ታሪክና ታላቅነት በሚገባ ስላልተማሩ፤ ፈረንጅ አድናቂዎችና አምላኪዎች ሆነዋል። እንደዚህ ያሉት ምሁር ተብየዎች በፖለቲካውም ሆነ በሃይማኖቱ ረገድ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ፍላጎት፤ ባህልና ሥነ ልቦና ጋር ሊጣጣሙ አልቻሉም።

ከ1966 ዓ/ም የኢትዮጵያ አብዮት ወዲህ ያለው ትውልድ፤ በአብዛኛው የጠፋ ትውልድ ነው። በመጀመሪያ ደረጃ ማርክሲዝም ሌኒንዝምን ስላነበቡ ብቻ ፈጣሪያቸውን ጭልጥ አድርገው ካዱ። እገሌ ከእገሌ ሳይባል የዚያ ትውልድ ዓባላት ለኢትዮጵያ ውድቀት ከፍተኛውን አስተዋጸዖ ማድረጋቸው አይካድም። ይህ ብቻም አይደለም አገራችን አሁን ላለችበት የተመሰቃቀለ ችግርም ተጠያቂዎች አነሱው ናቸው።

ፈጣሪ የለም በማለት፤ በተለያዩ የፓርቲ ድርጅቶች ተቧድነው የእስኳድ ዓባል በመሆን ወንድማቸውን ሲገድሉ የነበሩ፤በኋላም በዚሁ አቋማቸው በመቀጠል የኢሠፓ ዓባልና የፖለቲካ ካድሬ የነበሩ፤ ግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ/ም የወያኔው ኢሕአዴግ ኢትዮጵያን በተቆጣጠረ ጊዜ፤ ብዙ ዜጎች በስደት ወደ ወጭ አገር መሄዳቸው ግልጽ ነው። ነገር ግን ኢትዮጵያውያን በሄዱበት ሁሉ ከአያት ከቅድመ አያቶቻችን የወረሱትን አምልኮተ እግዚአብሔር ለመመሥረት ጥረት በሚያደርጉበት ጊዜ የዚሁ ዓባላት ርዝራዦች አማኝ መስለው ሰርገው በመግባት ችግር ሲፈጥሩ ቆይተዋል።

‘ጅብ ከማያውቁት አገር ሄዶ ቁርበት አንጥፉልኝ አለ’ እንዲሉ በተለያዩ አገሮች በስደት በሚኖሩባቸው አካባቢዎች፤ የሰበካ ጉባኤውን እና የስብከተ ወንጌል መድረኩን በመቆጣጠር፤ ምዕመኑ ሕንፃ ቤተክርስቲያን ለመሥራት ባላቸው ጉጉት፤ ያለ የሌላቸውን በማዋጣት ሲተባበሩ፤ እነዚህ አስመሳይ ከሀዲዎች ግን፤ የተሳሳተ አስተምህሮ በማራመድ፤ ቤተ ክርስቲያን ሳይሆን ቅድሚያ አዳራሽ እንሠራለን እያሉ፤ የተዋጣውን ገንዘብ በተለያዩ ምክንያቶች በማባከን፤ ምዕመኑን ከማሳባሰብ ይልቅ እያናደዱ፤ እያሳዘኑና እየበተኑ መሆኑ በስፋት ይነገራል። በእነዚህ ከሐዲዎች አመለካከት ቤተ ክርስቲያን መመሥረት ማለት መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት እንደ ማቋቋም ይቆጥሩታል። የሚሰበሰበው ገንዘብ ለቁጥጥር እንዳያመች በዘመናዊ አሠራር ማለትም በኮምፒውተር እንዲቀነባበር አይፈለግም።

በተጨማሪም ‘ሰው ሲታጣ ይመለመላል ጎባጣ!’ እንዲሉ በውጭ በስደት አገር የሚኖሩ ካህናትም የጀርባ ታሪካቸው በደንብ ሳይጠና፤ ከችግር አንፃር የአለውን ክፍተት እንዲሞሉ በሚል እየተመደቡ፤ ከካህን የማይጠበቅ ችግር ከመፍጠራቸውም በላይ፤ ከመንፈሳዊነት ይልቅ ዓለማዊ ጥቅምን የሚያስቀድሙ በመሆናቸው፤ እንዲህ የመሰለውን ውሳኔ በጽናት ሲቃወሙ አልታዩም። ከዚህም የተነሳ ምዕመኑ በሃይማኖቱ ጸንቶ በመቆም ፋንታ ለእምነት ስብራት መጥፎ ምሳሌ እየሆኑ ታላቅ ጉዳት አድርሰዋል።

በአሁኑ ወቅት፤የሕዝባችንን የዋህነት እንደ ድክመት በመቁጠር፤ ቅጥረኛ የሃይማኖት ሰባኪዎች አንደአሸን ፈልተው ኢትዮጵያን ለማፍረስ በገንዘብ ኃይል የዋሁን ሕዝብ ለማሞኘት፤ሆነ ብለው አስመሳይ ድራማ እየሠሩ ሕዝብን በስፋት ሲያታልሉ እየታየ፤ ኃላፊነት ተሰምቶት ሀይ ብሎ ያስቆማቸው ኃይል አለመኖሩ ያሳዝናል ። እንዲህ ያለውን ዓይን ያወጣ ሸፍጥ፤ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ችላ ሳይል፤ በቅድሚያ ለቤተሰቡ፤ ቀጥሎም ለቅርብ ጓደኞቹ፤ከዚያም ለሚያውቀው ሁሉ በማስረዳት እነዚህን ትውልድ ገዳዮችና አገር አፍራሽ ሐሳዊ ሰባክያን (ፓስተር ተብየዎች) ተከታይ እንዳይኖራቸው ማድረግ ይጠበቅበታል። እጅግ በጣም የሚገርመው ደግሞ እነሱ የዲያብሎስ ተላላኪዎች ሆነው እያሉ (በኋላኛው ዘመን ብዙ ተዓምራትን በማድረግ የተመረጡትን እንኳ የሚያስቱ ሐሳዊ ሰባክያን ስለሚመጡ መንቃት ያስፈልጋል፤ ማቴ 24፡) ሌላውን ሲነቅፉ መታየታቸው ነው።

በአሁኑ ወቅት በዓለም ወደ 47፣000 ሺህ የሚቆጠሩ የፕሮቴስታንት ሃይማኖት እምነቶች እንዳሉ ይገመታል። እንዲህ ያለው መከፋፈል ለምን መጣ ብለን ስንጠይቅ፤ የካቶሊክ ሃይማኖት የተቋቋመው ፖለቲካን መሠረት አድርጎ በመሆኑ፤ ከመጀመሪያው አዕማድ ወይም ምሰሶ ከአፈነገጠ በኋላ ሊሎችም ከዚያው እየወጡ አዳዲስ ቤተ ክርስቲያኖችን ለማቋቋም መብቃተቸውን ማስተዋል ብልህነት ነው። ዋናው ምክንያት ግን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ዶግማ እና ቀኖና የጥንቱና የጠዋቱ በመሆኑ ብዙዎች ጸንተው ለመቆም አልቻሉም። ሕጉ ጥብቅ ነው፡ነገር ግን ለአማንያን ደግሞ ብዙ በረከትና ፀጋ የሚታፈስበት ሃይማኖት ነው።

በዓመት ከ200 ቀናት በላይ መጾም ግድ ይላል። እነዚህ አጽዋማት የውዴታ ግዴታዎች ናቸው። ይህ ብቻም አይደለም ስትጾምና ስትጸልይ፤ ሁለመናህ መጾም አለበት፤ ዓይንህ፤ ጆሮህ፤ አንደበትህ፤ሆድህ፤ብልቶችህ ሁሉ መጾም አለባቸው፤ እጅህ ደግሞ ድውይን በመርዳት፤ ድኆችን በመመጽወት፤ የታመሙትን በመጠየቅ፤ የታሠሩትን በመጎብኘት፤ ያዘኑትን በማጽናናት መታጀብ አለበት። እንዲህ ዓይነቱ ጥብቅ ሥርዓት ለፕሮቴስታንት (ጴንጤ ቆስጤ) የሚመች አይደለም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለዛች አገር የሚገባት እውን ይሄ ነውን?

አንዱ አስገራሚ ጉዳይ ደግሞ ሃይማኖት የሌለውን፤ ሌላውን ሕዝብ ሰብከው መመለስ ሲገባቸው፤ ከፍተኛ ትኩረት አድርገው የዘመቱባት በዚህች ጥንታዊት የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ላይ ሲሆን፤ የሆነ ያልሆነ ቁንጽል ትርጉም እየሰጡ ምዕመናንን ጥርጣሬ ውስጥ መክተት ሥራየ ብለው ይዘውታል። በተለይ ደግሞ ሰማንያ አሐዱን መጽሐፍ ቅዱስን በማጥላላት በሐሰት እንደተጨመረ በማስመሰል፤ የጠፋው ዓለም ያጸደቀውን ስድሳ ስድስቱን ብቻ እንደሚቀበሉ ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከራሉ። በቅርብ እንኳ አንድ ኤርምያስ ነኝ የሚል ጥፉ፤ ስለ ቅድስተ ቅዱሳን እመቤታችን ድንግል ወላዲተ አምላክ ማርያምን አስመልክቶ መምህር ዘበነ ለማ ያስተማረውን በመተቸት አዋቂ በመምሰል ያስተላላፈውን ስምቼ እጅግ በጣም ገርሞኛል።

አባቶቻችን እንዲህ ያሉትን አማንያን መናፍቅ ይሏቸዋል። የራሳቸውን ጥለው የሰው የሚናፍቁ ወይንም ክብራቸውን የጣሉ ቀላዋጮች ማለታቸው ነው። ለዚህ አንድ ሁለት ምሳሌ ማንሳት ተገቢ ይሆናል። አንደኛ እመቤታችን የስለት ልጅ መሆኗ ይታወቃል። ነገር ግን በሦስት ዓመቷ ወደ ቤተ መቅደስ ገባች ይልና ከዚያ በኋላ ስላለው ሕይወቷ ብዙም አይዘረዝርም። በኋላም ቅዱስ ገብርኤል ‘ትጸንሻለሽ፤ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ፤’ ብሎ አንዳበሠራት ይናገርና የኤልሳቤጥን መጸነስ ከመልአኩ ስለሰማች ልትጠይቃት እንደሄደችና ፈጣሪዋን እንዳመሰገነች (ሉቃስ 1:26-38) ከመተረክ በስተቀር ብዙም አይናገርም።

ነገር ግን እመቤታችን በቤተ መቅደስ በነበረችበት ወቅት ብዙ መከራና ሥቃይ ደርሶባታል፤ እንዲሁም ብዙ ተአምራትን ሠርታለች። ይህ ሁሉ በስድሳ ስድስቱ መጽሐፍ አልተጠቀሰም። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም መወለዱን፤ ከዚያም በስምንተኛው ቀን ሊገርዙት ወሰዱት (ሉቃ 2:23-24) ይልና በ30 ዓመቱ በዮርዳኖስ ተጠመቀ ከዚያም ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ ይላል (ማቴ 3፡ 13-17)። ነገር ግን ሠላሳ ዓመታት ሙሉ እንዴት ቆየ፤ እንዴትስ አደገ የሚለውን ስንመረምር በስድሳ ስድስቱ መጽሐፍ የተብራራ አይደለም። ከዚህ የምንረዳው ጠላት ዲያብሎስና ጭፍሮቹ የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪክ ለመቆንጸልና ትርጉሙን ለማጣመም በተለያየ መልኩ ብዙ ብዙ ደባ ፈጽመዋል። በሦስተኛ ደረጃ መጽሐፈ ሄኖክም እንዲሁ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ከዓለም ተሰውሮ ቆይቷል። ይሁን እንጂ መጽሐፉ የተገኘው በኢትዮጵያ ሲሆን፤ በ18ኛው ክፍለ ዘመን የእንግሊዙ ሰላይ ጀምስ ብሩስ በድብቅ ሠርቆ እንደ ወሰደውና ዓለምም እየተደመመበት ለመሆኑ የሚያጠያይቅ አይደለም።

አሁንም እንደገና የኢትዮጵያን ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት፤ በተሐድሶ ስም የቋንጃ እከክ የሆኑባት የዚያ ትውልድ ርዝራዦችና የፕሮቴስታንት ሃይማኖት ተከታዮች፤ መናፍቃን ወይም ጴንጤዎች ናቸው። በቅድሚያ የራሳቸውን ታሪክ የማወቅ ጉጉት የላቸውም፡ ቢያውቁም ደግሞ ሥርዓቷን ይፈራሉ። ጾም አይወዱም፤ የዚህም አንዱ መገለጫው የዲያብሎስ መጨዋቻ የመሆን ምልክት ነው። እናታችን ሔዋን እና አባታችን አዳም ከነበራቸው ክብር የተዋረዱትና ከገነት እንዲወጡ የተደረጉት አትብሉ የተባሉትን በመብላት ነው።

ሥጋችን፤ የዚህ ዓለም፤ እና ዲያብሎስ፤ በአንድ ላይ ሆነው የሰውን ልጅ ወደ ሲዖል የሚያወርዱ ኃይሎች ናቸው። ሥጋም በጾም በመቀጣት በየጊዜው መንጻት አለበት፤ ዓለምንም በመናቅ፤ለጊዜያዊ ጥቅም ሳይሆን ለሰማያዊውና ዘለዓለማዊው ሕይወት መትጋት ይኖርብናል። ዋናውና አንደኛው ጠላታችን ዲያብሎስ ከነጭፍሮቹ በመሆን ‘ከአፍ የሚወጣ እንጂ ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም’ በማለት የተጣመመ ትርጉም እየሰጡ በጾም ፋንታ ሥጋችንን እንድናወፍር ያደፋፍሩናል። ለሰማያዊው ተድላና ደስታም እንዳናስብ አእምሯችንን በማደንዘዝና በብልጭልጭ ዓለም እንድንታለል ያጓጉናል።

በአገራችን፤ የእስልምና ሃይማኖትም ኦርጂናሉ (ሱኒ) ነው። የክርስትናውም ቢሆን ኦርጅናሉ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ነው። ነገር ግን ዘመን አመጣሽ ተቀጥያ ሃይማኖቶች በኢትዮጵያ ጠላቶች የተቀመሩ፤ እውነትንና ምዕመናንን በተለይም ወጣቱን ትውልድ ከጥንቱና ከአባቶቹ ሃይማኖት እንዲያፈነግጥና እስከነአካቴው እንዲጠፋ ለማድረግ በገንዘብ ኃይል እየተስፋፉ የመጡ ናቸው። ይህም አልበቃ ብሎ አሁን ደግሞ ፍጹም ዳቢሎሳዊ የሆነው የግብረ ሰዶም ተግባር በቅድስቲቱ ሀገራችን እንዲስፋፋና ትውልድ ጭራሹኑ እንዲመክንና አገር እንድትወድም የተቀነባበረ ሴራ እየተሠራ ይገኛል።

የዚህ ሁሉ ችግር መንስዔው የፖለቲካ መሪዎች አቋም ዋናኛ መለያ ሆኖ ሊወሰድ ይችላል። የፖለቲካ መሪዎች የሕዝቡን ፍላጎት፤ ጥያቄና እምነት ከምንም ባለመቁጠር የግላቸውን የዲፕሎማሲ ገጽታ ለማሳመር ሲሉ ተገቢውን ወቅታዊ እርምጃ በቁርጠኝነት አይወስዱም። ሟቹ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ዓለም አቀፍ የግብረ ሰዶማውያን ስብሰባ በኢትዮጵያ እንዲደረግ በመፍቀዳቸው በዚያው ዓመት ሕይወታቸው አልፏል።ፓትርያርኩም ባለመቃወማቸው በጥቂት ቀናት ልዩነት ወደ እማይቀረው ዓለም ሄደዋል። አሁንም ቢሆን የሃይማኖት አባቶችም ሆነ የታዋቂ ፖለቲካ መሪዎች ከማጉረምረም ውጭ ለሕዝብና ለአገር ደኅንነት ሲሉ በጽናት ቆመው ይህንን ውሳኔ ለመቃወም አልደፈሩም።

ስለዚህ ከዚህ ሁሉ ውዥንብር ትውልዱን ለመታደግ፤ ወላጆች ልጆቻቸውን ሰብሰብ አድርገው በመያዝ ሙስሊሙ ወደ መስጊድ ሔደው ቁራን እንዲቀሩ፤ ክርስቲያኑም ወደ ቤተ ክርስቲያን በመውሰድ የአገራቸውን እምነትና ትውፊት እያዩና እየተማሩ፤ ዕጣኑን እያሸተቱ፤ ጸበሉን እየጠጡ፤ እምነቱን እየተቀቡ እንዲያድጉ የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው። ልጆቻቸውን በመንከባከብ እንዲህ የማያደርጉ ወላጆች፤ ልጆቻቸው አጫሽ፤ ጫት ቃሚ፤ሠካራም፤ ሌባና ነፍሰ ገዳይ፤ ስለሚሆኑ መከራቸው ብዙ ነው። የወላድ መካን እንዳይሆኑ ገና በወጣትነት ዕድሚያቸው ጠንክሮ ማንነታቸውን አውቀው እንዲያድጉ ማድረጉ የበለጠ ይመከራል።

-//-

Share