እውን ውሳኔው ከዘላቂ የነፃነት፣ የፍትህና የሰላም አርበኝነት የመነጨ ነው? – ጠገናው ጎሹ

September 14, 2019
ጠገናው ጎሹ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ እምነት ላይ ከአገልጋዮቿና አማኞቿ ጋር በእሳት እስከጋማ የት የደረሰውን እጅግ አስከፊ ጥቃት በሰላማዊ መንገድ አደባባይ በመውጣት ቁጣን ከመግለፅ በዘለለ ጩኸትንና አቤቱታን ለመንግሥትና ለህዝብ ለማሰማት ለ1/4/2012 ተጠርቶ የነበረው ሰላማዊ ሰልፍ በቅደመ ሁኔታ ለጥቅምት ወር መጨረሻ መራዘሙን አስመልክቶ የተሰጠውን መግለጫ በጥሞና ከዳመጥኩት በኋላ በአእምሮየ መመላለስ የጀመረውን አስተያየቴን እንደሚከተለው በግልፅና በቀጥታ አስፍሬዋለሁ።

ባለሥልጣን ፖለቲከኞች በዋናነት ተጠያቂ የሆኑበትን ጉዳይ ከምር ወስደው ትክክለኛና ዘላቂ መፍትሄ ለማበጀት እንነጋገር ሲሉ ይሁን ብሎ መነጋገሩ የሚደገፍ አካሄድ ነው። እናም የሰላማዊ ሰልፉ አዘጋጆች የደረሱበትን የሰላማዊ ሰልፍ ቀንን የማስተላለፍ ውሳኔ ከዚሁ   አጠቃላይ እውነትና መርህ  አንፃር  መረዳትና መቀበል አያስቸግር ይሆናል ።

ነገር ግን በሰላማዊነት አደባባይ ወጥቶ የተፈፀመውን እጅግ አስከፊ ግፍና ወንጀል መላው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያውቀውና ጉዳዩ ከአንድ የእምነት ተቋም አልፎ በአገር ህልውና እና ደህንነት ላይ ለመቆጣጠር የሚያስቸግር አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል  እና ይህም እንዳይሆን የጋራ እርብርብን የግድ እንደሚል ማሳወቅ ለምንና እንዴት በመፍትሄ ፍለጋ ምክክር ስም ለሁለት ወራት እንደ ተራዘመ  ለማሳመን የተሄደበት መንገድ  ብዙም  አሳማኝነት ያለው  አይመስለኝም ።ከፍ ሲል ደግሞ ልፍስፍስና የተፈለገውን ውጤት የማያመጣ (clumsy and non-consequential) መሆኑን የአገሩን አጠቃላይ ሁኔታ ማለትም ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ ሞራላዊ ፣ሥነ ልቦናዊ፣ ሥነ ምግባራዊ፣ እና መንፈሳዊ (ሃይማኖታዊ እምነት) ውድቀት በቅንነትና ከምር ለመረዳት ለሚፈልግ የአገሬ ሰው ብዙ ምርምርና ትንታኔ የሚጠይቅ ጉዳይ አይደለም።

አዎ! ሰላማዊ ቅሬታንና ተቃውሞን የመግለፅ መሠረታዊ መብት ለምክክር ሂደቱ እንቅፋት እንዳይሆን በሚል አይነት አስተሳሰብ   የአቋም ሽግሽግ በ11ኛዋ ሰዓት ላይ ለማድረግ የተሄደበት መንገድ ቢያንስ ልፍስፍስ ነው፤ ከፍ ሲል ደግሞ የሸፍጥ ፖለቲካ ጨዋታ ሰለባነት ነው።

መሠረታዊ መብት ይከበር! ፖለቲከኞችም ከሸፍጥና ከሴራ የፖለቲካ ጨዋታ ወጥተው ሃላፊነታቸውን ይወጡ! የጎሳ/የዘር  አጥንት ቆጠራ ልክፍተኞችም ለማፅዳት በማይቻል አኳኋን በተበላሸ የፖለቲካ ሥርዓት ምክንያት ኑሮ ያስመረውንና ናላውን ያዞረውን  ወጣት ትውልድ ልክ በሌለው እብደት እየነዱ የጥፋት መልእክተኛቸው ከማድረግ ተቆጥበው ወደ ትክክለኛው የሰብእና ባህሪ ይመለሱ! ብሎ በሰላማዊ የአደባባይ ትእይንተ ህዝብ ለመጠየቅ የሰበብ ስንክ ሳር የሚደረድር መብቴ ይከበር ባይ አካል   እንዴት የእውነተኛና የዘላቂ መፍትሄ አካል ሊሆን እንደሚችል ለማሳመን ቀላል የሚሆንለት አይመስለኝም።

በእንዲህ አይነት በእጅጉ  የተልፈሰፈሰና ልክ  የሌለው መስሎና አስመስሎ የመኖር (መኖር ከተባለ)  አስተሳሰብና አካሄድ  ከተዘፈቅንበት የመንፈሳዊና የገሃዱ ዓለም   አዘቅት ወይም አዙሪት ጨርሶ መውጣት እንደምንችል እንኳን ለማመን ለማሰብም ይከብዳል።

በዚህ አይነት በእጅጉ በተልፈሰፈሰና የእውነተኛ ነፃነት ፣ፍትህና እኩልነት አርበኝነት በጎደለው የሃይማኖትም ይሁን የፖለቲካ ሰብእና  ሸፍጠኛና ሴረኛ ፖለቲከኞችን እና የጎሳ/የዘር/የመንደር/የቋንቋ አጥንት ቆጠራ ፖለቲካ ልክፍተኞችን አደብ ማስገዛት ጨርሶ የሚቻል አይደለም (አይሆንም)።  እናም አውቀንም ሆነ ሳናውቅ የፖለቲከኞች የሸፍጥ ፖለቲካ ተውኔት አጃቢዎች ወይም አዳማቂዎች እየሆን እና በተቃራኔውና በአሳዛኝ መልኩ ደግሞ  አደንቁረው ሲገዙት የኖሩትንና አሁንም በተሃድሶ ትርክት ስም በዚያው እንዲቀጥል ሌት ተቀን በአደንቋሪ ዲስኩራቸው የሚያደነቁሩትን መከረኛ ህዝብ አብረን የማደንቆራችን ድንቁርና የሚበጀውን መላ (መፍትሄ) ልናበጅለት ይገባል ። በእውን ነፃነት፣ ፍትህ፣ እኩልነት፣ አብሮነት፣ ሰላም፣ ፍቅርና የጋራ ብልፅግና የሰፈነበትን ሥርዓተ ማህበረሰብ የምንፍልግና የምንናፍቅ ከሆነ የእውነተኛ መፍትሄ መንገዱ ይህኑ መሪር ሃቅ ተቀብሎ የሚበጀውን ማድረግ ነው።

እንዳይድን ሆኖ በተበከለው የኢህአዴጎች የፖለቲካ ሥርዓት ምክንያት ሁለመናችንን የሚጠዘጥዘንን ክፉ የህመም ስቃይ እነሱው የሚያዙልንን የማስታገሻ (የማደንዘዣ) እና እያደር ሰውነታችን ብቻ ሳይሆን ህሊናችንም ክፉኛ እየተለማመደው የሚሄደውን የፍርፋሪ ምፅዋዕት እየተመፀወትን ተመስገን የማለቱን   እጅግ ክፉ ልማድ በቃን ልንለው ይገባል  ።

ከፈጣሪ  የተሰጠውንና እና በህግ የተደነገገለትን   መሠረታዊ መብቱን ተጠቅሞ  በሰላማዊ መንግድ  በገንዛ አገሩ አደባባይ ላይ ጩኸቱን የማሰማት ዝግጁነቱን (እቅዱን)   ወደ ኋላ እንዲስብ  ፖለቲከኞች የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ለማድረግ እንደ ቅድመ ሁኔታ ተቀበለህ በመግለጫ አሳውቅ ሲሉት ለምንና እንዴት ብሎ ሳይሞግት ተቀብሎ እወቁልኝ ማለት እንዴት የድል ጅማሮ እንደሚሆን ለመረዳት በእጅጉ ያስቸግራል ።

አዎ! የፖለቲከኞችን ቅድመ ሁኔታ አሜን ! ብሎ በመቀበል  እያደር  እጅግ እየሰለቸ የተቸገርንበትን ድርጊት አልባ የመግለጫ ድርሰት እየደረሱ እወቁልኝ  ማለት  ለሃይማኖትም ሆነ ከሃይማኖት ጋር በጥብቅ ለተቆራኘው አጠቃላይ የሰብአዊ መብት መከበር  ቆሚያለሁ ለሚል ግለሰብ ወይም ቡድን ወይም አካል ጨርሶ የሚመጥን አይደለም።  ለዘመናት ከዘለቅንበትና አሁንም ካለወጣንበት አጠቃላይ ክፉ አዙሪት እንድንወጣ ከምር የምንፈልግ ከሆነ በቅድሚያ እራራሳችንን ከዚህ አይነቱ የፖለቲካ አስተሳሰብና አካሄድ ጋግርት ማላቀቅ ግድ ይለናል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ህዝብን በመጨቆን ሀገርን መምራት አይቻልም!

ይህን አስተያየቴን ሁከትና ጦርነት እንደ ማነሳሳት ለመቁጠር የሚሞክሩ (የሚከጅላቸው)  ወገኖች እንደሚኖሩ በሚገባ  እረዳለሁ ።  በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ እንኳን በተወሰነ ሰዓት ትእይንተ ህዝብ ለቀናት በሚዘልቅ ሰላማዊ እምቢተኝነት  መሠረታዊ መብት ይከበር ብሎ መጮህ  ከፖለቲከኞች ጋር ልንወያይበት ነው ለሚባለው ጉዳይ ተጨማሪና በጎ ግፊት ለማድረግ ያግዛል እንጅ  እንዴት የብጥብጥና የጦርነት ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ለማሳመን  በእጅጉ ያስቸግራል የሸፍጥና የሴራ ፖለቲካ ሰለባ ለመሆን ከቶ አይቃጣኝም ለሚል የአገሬ ሰው።

ጤናማና ቅን ህሊና ያለው ወገን እንዲህ አይነት የጥፋትና የመጠፋፋት አጀንዳ እንኳን በድርጊት የማድረግ በሃሳብ ደረጃም  ይኖረዋል የሚል እምነት ጨርሶ የለኝም ። እኔም እንደ አንድ የአገርና የወገን ጉዳይ እንደ እሚያሳስበው ተራ ኢትዮጵያዊ የሚሰማኝንና የማምንበት በግልፅና በቀጥታ ከመግለፅ በስተቀር አንዳችም አይነት የጥፋትና የመጠፋፋት አስተሳሰብና አካሄድ የለኝም ከማለት ውጭ  እመኑኝ በሚል መማልና መገዘት አለብኝ ብየ አላምንም ። የማይስማማንን አስተያየት የሰነዘረውን ግለሰብ ወይም ቡድን ሁሉ በተንሻፈፈና በተንሸዋረረ  አስተሳሰብ የመፈረጁ ክፉ ልማዳችን ገና ግዙፍና አድካሚ ሥራ የሚጠይቀን መሆኑን በሚገባ ስለምገነዘብ (ስለማውቅ)  የአንዳንድ ወገኖች የተሳሳተ አተረጓጎም  ጨርሶ አይገርመኝም ። አያሳስበኝምም  ። እንደ ግለሰብ ዜጋ ፣ በተለያየ የፖለቲካም  ሆነ የሙያ ዘርፍ እንደተደራጀ ቡድን እና በአጠቃላይ እንደ ህዝብ በተቀናጀና በተባበረ ጥረት ከዘመን ጠገቡ ክፉ አዙሪት ትርጉም ባለውና በፍጥነቱም ሆነ በይዘቱ በላቀ የእውነተኛ ለውጥ መሣሪያነት ለመውጣት ያለመቻላችን እንቆቅልሽ ህመም ግን በእጅጉ አስከፊና ጥልቅ ነው።

የሰላማዊ ሰልፉ (የትእይንተ ህዝቡ) አስተባባሪዎች በሰላማዊ መንገድ እና በነፃነትና በሞራል የአርበኝነት ልእልና የመብት ጥያቄን አደባባይ አውጥቶ የማሰማቱን ጥያቄ ሸፍጠኛና ሴረኛ ፖለቲከኞችሙሴዎች” ተብለው የተሞካሹበት የፖለቲካ ገፅታቸው ከአገር አልፎ በዓለም ህብረተሰብ እርቃኑን እንዳይቀር ለማድረግ የአዘጋጁት የፖለቲካ ተውኔት ሰለባ ለመሆን የመፍቀዳቸው ጉዳይ  ቢያንስ አስተዛዛቢ ነው ። ሲከፋ ደግሞ ህዝብና አገር የእውነተኛ ሰው ያለህ ! እያሉ በሚጮሁበት አስከፊ ሁኔታና ወቅት  ሰው ሆኖና እንደ ሰው ሆኖ ያለመገኘት ክፉ አዙሪት ነው።   በሰማያዊው ዓለምም  ሆነ በገሃዱ ዓለም በኩራት የሚያቆም የእውነተኛ ሰብእና ልእልናም  የለውም።

ጠርሱን ነቅሎ ያደገበትን የህወሃት/ኢህዴግ አስከፊ ወንጀል በመዘርዘር ይቅርታ የጠየቀ ጠቅላይ ሚኒስትር እራሱ በበላይነት የሚመራው መንግሥት አካላት፣ የፖለቲካ ቡድን (ኦዴፓ/ኢህአዴግ)፣   እልፍ አእላፍ ካድሬዎቹና ባለሥልጣኖቹ እና የፀጥታ ሃይሎች ዝም ብሎ ከማየት አልፎ ተባባሪዎች የሆኑበትንና አብያተ ክርስቲያናት ከአገልጋዮቻቸው ጋር ዶግ አመድ የሆኑበትን አሰቃቂ ድርጊት (ወንጀል) ቢያንስ እንደ ሥራ አስፈፃሚው የመንግሥት አካል የበላይ ባለሥልጣን ይቅርታ ለመጠየቅና እንዲህ አይነት የዘቀጠ የመንግሥትነት አካሄድ አይደገምም ለማለት የሞራል ወኔ ሲያጣ ከማየት (ከመታዘብ) የከፋ የየራሳችን ህሊና በእጅጉ የሚፈተን ፈተና   የሚኖር አይመስለኝም። “እኔ ቤተ ክርስቲያን አላቃጠልኩም ፤ ድሮም ይቃጠል ነበር ወደፊትም ሊቃጠል ይችላል፤ ከእኔ በፊት በነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትሮች ላይ ያላሳያችሁትን ጥንካሬ በእኔ ላይ ለምን?” የሚሉ እና ሌሎችንም እራስን ብቻ ሳይሆን የአገርን የክብር ደረጃም በእጅጉ ቁልቁል የሚያወርዱ መከራከሪያ መሰል ዲስኩሮችን መስማትና ማየት ደግሞፈተናውን ብርቱ ያደርገዋል ።

ታዲያ የሰልፉ አስተባባሪዎች የተጎጅው ቤተ እምነት ብቻ ሳይሆን ማነኛውም የመብት መከበርና የሰላም መስፈን ጉዳይ ግድ ይለኛል የሚል ዜጋ ሁሉ በአደባባይ ወጥቶ በሰላማዊ መንገድ ጩኸቱን ያሰማበታል የተባለውን ትእይንተ ህዝብ ለምክክር ሲባል ቀን አራዘምን የሚል ሰበብ የሚደረድሩልን  ከከፍተኛው የሥልጣን እርከን በይፋ ከተነገረው የአላቃጠልኩምና ይቅርታም አልጠይቅም ወይም በሌላ አባባል ሃላፊነት አልወስድም ከሚለው የተለየ ምን አይነት ተአምራዊ የፖለቲካ ሰብእና ጠብቀው ነው?

ክርስቶስ ግፈኛ ገዥዎችና አንዳንድ እኩያን  ፍጡሮቹ የታላቅ መልእክቱን ፣ አስተምህሮቱንና ተግሳፁን ጠቃሚነት ከምር አዳምጠው ለራሳቸውም ሆነ ለመላው የሰው ልጅ የሚበጅ ሥራ እንዲሠሩበት አግባብነትና ገንቢነት ባለው መንገድ (ሁኔታ) በእምነት አውዶች ዙሪያ ብቻ ሳይሆን እየተዘዋወረ ባስተማረባቸው ቦታዎች ሁሉ በግልፅና በአደባባይ ሞገታቸውና ገሰፃቸው እንጅ ከእነሱ ጋር ከመጋረጃው ወይም ከአደባባይ በስተጀርባ እየተሻሸ በሰላምና በፍቅር ስም ከንቱ ውዳሴን ጨርሶ አላስተማረንም ። እንዲያውም እንዲህ አይነቱን ከህዝብ እይታ/እውቀት እና ተሳትፎ በስተጀርባ የሚደረግን የመተሻሸት  አስተሳሰብና አካሄድ ጨርሶ እንድንፀየፈው ነው በጥብቅ ያስተማረን ።ይህንን የተቀደሰና የእውነተኛ ሰብእና ሃያልነት ለመረዳት ሊቅ ወይም ሊቀ ሊቃውንት መሆንን አይጠይቅም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  እንዳንደናገር እንጠንቀቅ፣ - ክገብረ አማኑኤል

የዚህ ዘመኖቹ እኛም  ምን እየሆንና ምን እያደረግን እንደሆነ የየራሳችን ህሊና (ነፍስ) ከምርና ከቅንነት ከጠየቅን ትክክለኛውን መልስና የመፍትሄ መንገድ ለማግኘት ከቶ የሚሳነን አይደለም ። አይሆንምም።

የሰልፉ አስተባባሪዎች  ፍፁም ሰላማዊና ከጊዚያዊ መረጋጋት አልፎ የሚሄድ መፍትሄ አስፈላጊነትን በአፅንኦት ለማስገንዘብ ያግዛል በሚል ያዘጋጁትን ህዛባዊ ሰልፍ (ትእይንት) ከፖለቲከኞች ጋር በየቢሮው ያደረጉትንና  በቀጣይነትም ይካሄዳል የሚሉትን ምክክር ምክንያት በማድረግ ወደ ኋላ የሳቡበት አስተሳሰብና አካሄድ ከልፍስፍስና እውን ከማይሆን የሰላም ፈላጊነት   (unrealistic pacifism) የሚያልፍ አይመስለኝም ። ይህ ግንዛቤየ የድንቁርና ቢሆንና ነገሮች ሁሉ መሠረታዊና ዘላቂ ወደ ሆነ የለውጥ ጎዳና እንዲወስዱን ማድረግ ቢቻለን እንዴት መልካም ነበር። በመሬት እየሆንና እያደረግን ያለነው ነገረ ሥራችን ግን ይህን የሚያረጋግጥ አይደለም ። ለዚህ ነው አውቀንም ሆነ ሳናውቅ የለወጥ ብልጭታ ታየን በሚል የአገራችን እውነተኛ ፈውስ እና የህዝቧ መከራና ውርደት ፍፃሜ እውን ሆኑ እያልን በስሜታዊነት ፈረስ መጋለብ ከጀመርን ብዙም ሳንራመድ  ወደ ዚያው ዘመን ወደ ቆጠርንበት የጎሳ/የዘር/የቋንቋ አጥንት ቆጠራ ፖለቲካ አዙሪት በባሰ አኳኋን እየተዘፈቅን በብርቱ የተቸገርነው ።

በሰላማዊ መንገድ መብትን በአደባባይ መጠየቅንና የባለሥልጣኖችን ሃላፊነትና ተጠያቂነት የማስገንዘብ ዝግጅትን  ከፖለቲከኞች ጋር ከተደረገውና ይደረጋል ከሚባለው ውይይት ጋር ተፃራሪ ይመስል ለውይይቱ እድል ለመስጠት ለረጅም ጊዜ አስተላልፈነዋል የሚለው መግለጫ (እወጃ)  በህዝብ ዘንድ ቀቢፀ ተስፈኝነትን ስለሚያስከትል ከተዘፈቅንበት አዙሪት  ለመውጣት የምናደርገውን ጥረት  በእጅጉ ረጅም ከባድ ያደርገዋል። አዎ! በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ ፖለቲከኞች በሚመርጡለት ጊዜና ሁኔታ ሳይሆን መሠረታዊ መብቱን በአደባባይ ጭምር ለመጠየቅ ያለውን ቁርጠኝነት በማሳየት ፖለቲከኞች ትርጉም ወደ አለው የምክክር ጠረጴዛ እንዲመጡና ሃላፊነታቸውንና ተጠያቂነታቸውን እንዲወጡ ግፊት ለማድረግ የሚሽኮረመም አስተሳሰብና አቋም  እንኳን የሰማያዊውን ተልእኮ ተሸክሚያለሁ ለሚል ለማነኛውም ቅን ለሆነ ነፃነትና ፍትህ ፈላጊ የአገሬ ሰው ጨርሶ አይመጥንም ።

የሰልፉ አስተባባሪዎች ውይይት ማድረግጉና የሰላማዊው ትይንተ ህዝብ ዓላማና ግብ የሚቃረኑ የመብት ማስከበሪያ መንገዶች (ሥልቶች) ይመስል  የውሳኔያቸውን መታጠፍ   ስሜትን በሚስብና ነገር ግን ወደ መሬት ወርዶ   የነፃነትና የፍትህ ማስከበሪ ሃይል በማይሆን የቃላት ድርሰት (ምጥቀት)  እወቁልን ብለው ያነበቡልን መግለጫ አገራችን ከምትገኝበት የሃይማኖትም ሆነ የፖለቲካ ምስቅልቅል  ለመውጣት ለሚደረገው እልህ አስጨራሽ ፈተና ጨርሶ አይመጥንም።

የፍርድ ቤት ሥርዓት ተብየውን በአስቀያሚው የፖለቲካ ጨዋታቸው  ጠርንፈው በሃሰት በተፈበረከ ክስ (ውንጀላ) በየማጎሪያ ቤቱ የሚማቅቁትን ንፁሃን ዜጎች በረጃጅምና ተደጋጋሚ ቀጠሮ  እንዲጉላሉ  በማድረግ ቀን በተቆጠረ ቁጥር   ህዝብ  እንዲዘናጋና እንዲደነዝዝ  የሚያደርጉ የኦዴፓ/ኢህአዴግ ባለሥልጣናትና በየደረጃው የሚገኘው የካድሬ ሠራዊት አባላት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ላይ የደረሰውን አስከፊ ግፍና ወንጀል በተመሳሳይ ዘዴ ለማዘናጋት (ለማደንዝዝ) አይሞክሩም ብሎ ማመን  ወይ የአገርን መሪር  እውነት  ያለማወቅ የለየለት  ድንቁርና  ፣ ወይም ደግሞ   የለየለት መስሎና አስመስሎ የማደር ክፉ ልክፍት ነው።

ይህን አስተያየቴን ብዙ የዋህ ወገኖች እንደ ሚያስቡት (እንደ ሚፈልጉት) ከዚህ በተሻለ ሃይለ ቃል ለመግለፅ ብችል እሞክረው ነበር። ነገር ግን መሪሩን ሃቅ እያስታሙሙ ወይም አካፋውን የወርቅ ማፈሻ ማንኪያ እያስመሰሉ ማሽሞነሞን ለማንምና ለምንም ስለማይጠቅም አላደረግሁትም ። አላደርገውምም።

የሰልፉ አዘጋጀች (ማህበራት) መመካከርንና ዘላቂ መፍትሄ ማበጀትን  ጨምሮ ፖለቲከኞች ሃላፊነታቸውን ይወጡ ዘንድ በማነኛውም ሰላማዊና ገንቢ በሆነ ዘዴና እርምጃ ሁሉ ከመጠየቅና መብትን በመብትነቱ እንዲከበር ከማድረግ ወደ ኋላ በማሸግሸግ መሠረታዊ የሆነውን ሰላማዊ ሰልፍ ወይም ትእይንተ ህዝብ የማድረግ   መብትን ለመደራደሪያነት አሳልፈው የሰጡበት አካሄድ ከዘለቅንበትና አሁንም ከምንገኝበት ክፉ አዙሪት የመውጣት ፈተናው በእጅጉ ብርቱ እንደሆነ ነው የሚነግረን  ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ከክልል ባለሥልጣናት እና እንዲሁም ሃላፊነታቸውን በሙያ ነፃነት  ከመወጣት  ይልቅ የሸፍጥና የሴራ ፖለቲካ መሳሪያዎች ከሆኑ የፖሊስና የደህንነት አካላት ጋር  የተደረገውን ውይይት በር የማስከፈት ትልቅ ድል እንደሆነ የሚነግሩን የሰልፉ አስተባባሪዎች ወይ ዘመን ጠገብ የሆነውን የፖለቲከኞቻችንን ሸፍጥ በቅጡ ለመረዳት የሚያስችል የእውቀትና የሞራል አቅም ያንሳቸዋል ፤ ወይም  እያወቁ መሠረታዊ መፍትሄን እውን በማድረግ  ሳይሆን በእሳት አደጋ ማጥፋት ላይ ተጠምደዋል ፤  ወይንም ደግሞ  ለሃይማኖት መብት መከበርና ለወገን ከመከራና ከውርደት  መውጣት  እስከ መስዋእትነት የሚዘልቅ ታጋድሎ እንደሚያደርጉ የሚነግሩን  ከአንደበታቸው  እንጅ ከትክክለኛው ህሊናቸው የሚመነጭ አይደለም ማለት ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሀገራችንን ችግር ከነችግር ፈጣሪዎቹ ልቅምቅም አድርጎ ለማስወገድ

ይህ ክፉ የእኛነታችን አባዜ ለዘመናት አብሮን የዘለቀና አሁንም እንደ ተጠናወተን የቀጠለ መሆኑን ለመረዳት ብዙ ንግግር (ዲስኩር) የሚጠይቅ ከቶ አይደለም።  የቲዎሎጅ (የነገረ መለኮት) ተማሪና ሊቅ መሆንንም አይጠይቅም።    እጅግ ረጅምና እልህ አስጨራሽ የጋራ ትግል የሚጠይቅ ከባድና ውስብስብ ፈተና  ላይ መሆናችንን ተረድቶ  በቅንነትና በአርበኝነት መንፈስና የተግባር ሰውነት  የሚችሉትን ሁሉ ማድረግን ነው የሚጠይቀው።

ከፖለቲከኞች (ከመንግሥት/ከገዥው ቡድን ባለሥልጣናት) ጋር  በእኩልነት ያገባናል በሚል የመንፈስ ጥንካሬ  በዘላቂ የመፍትሄ ሃሳብ ዙሪያ መወያየት ተገቢነቱ ባያጠያይቅም የተፈፀመውን ወንጀል አጣርቶ ተገቢውን እርምጃ የመውሰድ ሃላፊነት የሚወድቀው በነዚያው በተሃድሶ ስም መከረኛውን ህዝብ አደንቁረውና አደንዝዘው ህወሃት/ኢህአዴግ ሠራሹን ሥርዓት በኦዴፓ/ኢህአዴግ ተረኝነት እያስቀጠሉ ባሉት ፖለቲከኞችና ባለሥልጣናት ላይ መሆኑ በግልፅና በቀጥታ መታወቅ አለበት።  አጣርተን እስክንጨርስ በሰላማዊ መንገድ  ተቃውሞን በአደባባይ የመግለፁ ዝግጅት እንዲገታ እንደ ቅድመ ሁኔታ ተቀበሉና  መግለጫን በመግለጫ ሽራችሁ ለህዝብ ድል አብስር” ሲባል ይሁን ብሎ መቀበልና ተፈፃሚ ማድረግ  የእውነተኛ የነፃነትና የፍትህ አርበኝነትን ሰብእና  ጨርሶ አያሳይም ።

ምናልባት የጎሳ/የዘር/የመንደር አጥንት ቆጠራ ፖለቲካ ልክፍተኞች የፈረደበትን ወጣት ትውልድ ልጎም የሌለው የእብደት ፈረስ እያስጋለቡ በእኛ (ኬኛ) ከተማ (ፊንፊኔ) የእኛንና የመሰሎቻችንን  እብደት የሚያወግዝ ወይም ተጠያቂ የሚያደርግ እንኳን የአደባባይ ትእይንተ ህዝብ የአዳራሽ ስብሰባም የሚያካሄድ ወዮለት ማለታቸውን ተከትሎ የተለወጠ ውሳኔ አይሆንም ብሎ መገመት ተራ ግምት የሚሆን አይመስለኝም

በእንዲህ አይነት ልክ የሌለውና አደገኛ የጎሳ/የዘር/የቋንቋ አጥንት ቆጠራ ፖለቲካ አክራሪነት የተለከፉ ግለሰቦችና ቡድኖች እያስፈራሩ በሚዘውሩት መንግሥትና የገዥ ቡድን አገር እንዴት አገር ይሆናል? ይህኑ መንግሥትና የገዥ ቡድን እንመራለን ከሚሉ ፖለቲከኞች ጋር ከመጋረጃው በስተጀርባ  ተደረገ የሚባለውና ሊደረግ ታስቧል በሚል  ሰብብ በአደባባይ መብትን ይጠይቃል የተባለለትን ሰላማዊ ሰልፍ እስከማስቀየር (እስከማስተው) የደረሰው የምክክር ትርክትስ እንኳን ዘላቂ መፍትሄ ትርጉም ያለው ጊዚያዊ እፎይታስ እንዴት ሊያስገኝ ይችላል ?

ፍፁም ሰላማዊ የሆነ ትእይንተ ህዝብ ማካሄድ በምክክሩ አስፈላጊነት ላይ ተጨማሪ እገዛ እንጅ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድር ይመስል የሁለት ወራት ቀጠሮ መስጠት (ያውም በፖለቲከኞች ሸፍጥ የውሃ ሽታ ሆኖለሚቀረው)  ጨርሶ አሳማኝነት የለውም። ተማርን ብለው በእጅጉ የመከኑ የጎሳ/የዘር/የመንደር/የቋንቋ አጥንት ቆጠራ ፖለቲካ ልክፍተኞች ለሩብ መቶ ክፍለ ዘመን በፖለቲካ ወለድ ወንጀል ከተዘፈቁበት መውጣት ባቃታቸው ፖለቲከኞች (ባለሥልጣናት) እየታገዙ ያዙንና ልቀቁን ባሉ ቁጥር ለአገርና ለወገን ሰላም ስንል የሚል እጅግ ልፍስፍስ ሰበብ እየደረደሩ እንዴት ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እውን ለማድረግ እንደሚቻል ለመረዳት በእጅጉ ከባድ ነው ። ከፍ ሲል ደግሞ   ስሜት አይሰጥም።

የእንዲህ አይነት የአክራሪ መንደርተኞችን እብደትና በሥልጣን ላይ የሚገኙ ተባባሪዎቻቸውን አደገኛ ሸፍጥና ሴራ በሰላማዊና በአብሮነት መንፈስና ድርጊት አደብ ለማስገዛት ከመንቀሳቀስ ይልቅ እነሱ ያዙንና ልቀቁን ባሉ ቁጥር የሰላምንና የሰላማዊነትን ትክክለኛ ትርጉምና አስፈላጊነት በተልፈሰፈሰ (የእራስ መተማመን በጎደለው) አኳኋን እየተረጎምን እና ይህኑ ደካማነታችን ለማሳመን እዚህ ግባ የማይባል ሰበብ እየደረደርን እስከመቸና እንዴት ከገባንበት አስከፊ አዙሪት ለመውጣት እንደምንችል ለመረዳት በእጅጉ ይከብዳል ።

ለሩብ መቶ ክፍለ ዘመን ከፊታችን የተደቀነውን መሪር ሃቅ  እየሸሸን (እየፈራን) እና ይህኑ ልክ የለሽ ፍርሃታችን ለማስተባበል ድርጊት አልባ የዲስኩርና የሰበካ ቃላታን እያዥጎደጎድን  የዘለቅንበትን አባዜ ታግለን ማሸነፍ ካለብን የሸፍጥ ፣የሴራና የቅሌት ፖለቲካ ጨዋታን መፀየፍና የሚበጀንን የእውነተኛ ነፃነት ፣ ፍትህና እኩልነት ሥርዓት እውን ለማድረግ የአርበኝነትን ወኔ መላበስ ግድ ይለናል ። ከዚህ በመለስ ያለው ምናልባት የተሻለ የፍርፋሪ ምፅዋእት ያስገኝ እንደሆን እንጅ ከፖለቲካ ባርነት ወይም ከሰብአዊ ፍጡር በታች ከመዋል አዙሪት ጨርሶ አያወጣንም ።

 እናም ልብና አእምሮ ይስጠን እንዳንል አሳምሮ ሰጥቶናልና ትክክል የሚሆነው የሰጠንን ድንቅ ተፈጥሮ ለእራሳችን ብቻ ሳይሆን እኛ ለመሰለ የሰው ልጅ ሁሉ በሚጠቅም ሁኔታ ሥራ ላይ እናውለው ዘንድ እንዲረዳን እየጠየቅን ከተዘፈቅንበት ክፉ አዙሪት ለመውጣት የምር ትግል ማድረግ ነው     

አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር የባዶ ተስፋኝነት ልማድ እስረኞች ከመሆን ወጥተን ተስፉን በሁሉም የህይወት ዘርፉችን እውን ለማድረግ የሚያስችለንን ሥራ እንድንሠራ እየተመኘሁ አበቃሁ

 

Share