በባህር ዳርና አዲስ አበባ በተከሰቱ ቀውሶችና በሌሎችም አካባቢዎች በሚታዩ ውጥረቶች ተሸንፈን አገራችንን አንድነት በሚፈታትን ቀውስ ውስጥ እንዳንገባ ሰከን ባለ መንፈስ  እናት ኢትዬጵያን በጋራ እንታደግ!!

( ከአበባየሁ አሉላ ) ዋሽንግተን ዲሲ

በባሕርዳርና አዲስ አበባ በሰሞኑ የተከሰተው ቀውስ በሁሉም አቅጣጫ የብዙ ወገኖቻችንን ሕይወት የቀጠፈ በመሆኑ በግራም ይሁን በቀኝ የዜጎቻችን ልብ የተሰበረበት ወቅት ነው!

በዚህ እንቆቅልሹ ባልተፈታ ቀውስ የአማራው ክልል ወገናችንም ብርቅዬ ልጆቹን ያጣበት ወቅት በመሆኑ ሐዘኑና ምሬቱ እጅግ ከፍተኛ ነው!

በመቀጠልም በዚሁ ውጥረት ውስጥ በደቡብ ክልል የሲዳማ የማንነትና ክልል እንሁን እጣብቅኝ ፣ በተመሳሳይ በዋና ከተማችን በአዲስ አብበባና በሌሎችም የሚታየው ውጥረትና በየቦታው የሚታዬ ጅምላ እስሮች ሁላችንንም አዕምሮ ሰላምና  እንቅልፍ እንደሚነሳንና እንደሚያሳስበን ግልፅ ነው፤

በኢትዬጵያ ምድር ፍታዊና ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እውን እንዲሆን በተለይም በዘር ኃረግ ኢትዬጵያን የበለተው የሕወኃት/ኢሕአደግ መንግሥት እስከነአካቴው እንዲወገድ እልፍ አዕላፎ ዜጎቻችን ሕይወታቸውን ፣ አካላቸውንና ማንነታቸውን መስዋዕት አድርገዋል፣ በዚህም እልህ አስጨራሽ ትግል የእልፍ ዓዕላፍ ታጋዬችና የኢትዬጵያ ወጣቶች ብዙ ዋጋ ቢከፍሉም በርግጥ አምባገነኑን አገዛዝ እስከነአካትው ከትከሻቸው ማስወገድ ባይችሉም አስኳሉን ሕወኃትን አቅም ከድቶት ዛሬን ማየት ዕድል አግኝተናል።

በዚህ ለዓመታት መቆሚያ አጥቶ በመላ አገሪቱ ተቀጣጥሎ በነበረው የህዝባዊ  እምቢተኝነት ምጥ ውስጥ አገራችን በገባችበት የታሪክ አጋጣሚ ከውጪ ሳይሆን ሳይሆን በውስጡ ሆነው ይህንኑ ሥርዓት በውል ሲያገለግሉ ከነበሩት የዛሬው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድና ሌሎች ጓደኞቻቸው ዕዕድሉን አግኝተው በለውጥ ኃይልነት  ትላንት ኢትዬጵያ በሕወኃት/ኢህአደግ አመራር ውስጥ ከነበረችበት ዜጎኝ በሁሉም ማዕዘናት በእናት አገራቸው ባይተዋር ሆነው ነፃነትን ተነፍገው ብዙዎችም በአስከፊ ሁኔታ የእስር ሰላባ የነበሩበትንና ዘግናኝ ሰቆቃም በዜጎቻችን ላይ የተፈፀመበት የጨለማ ዘመን በሕዝብ እምቢተኝነት ሰንሠለቱ ተበጥሶ በአጭር ጊዜያት በጠቅላይ ሚኒስትሩ አመራር የተወሰደው ተከታታይ ተራማጅ እርምጃዎች በሕዝባችን ልብ ከፍተኛ ተስፋን መሰነቁ እሙን ነው!

በተመሳሳይም በሁለት የዕምነት ተቋሞቻችንና በምዕመናኖቻቸው ላይ የደረሰውን በደልና መከፋፈል ለማስወገድ የተወሰደው እርምጃ እጅግ አስደማሚ ሲሆን በተመሳሳይም እናት ኢትዬጵያ ጠበቃ አጥታ በቆየችበት 27 ዓመት የመከራ ዘመን በልጆቿ እምቢተኝነትና በለውጥ ኃይሉች በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ ኢትዬጵያንና ኢትዬጵያዊነትን ከወደቀበት አንሥተው ከፍ መደረጉና ነፍስ መዝራታቸው በደስታና በተስፋ የአብዛኞቻችንን ልብ በእጅጉ ሞልቶታል!

በተከታታይ በተወሰድ አበራታች እርምጃዎች በተስፋም ተሞልተን ነገ ከዛሬ በይበልጥ የተሻለ ይሆናል ብለን እንድናልም አስችሎን ነበር!!

በመሆኑም የኢትዬጵያ ሕዝብ በአገር ቤትም ይሁን  ይሁን በውጭ አገራት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ለዚህ ሁሉ ፋይዳ ባለቤት ለሆኑት ለጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አሕመድና ጓዶቻቸው የሰጠው ልባዊ የአደባባይ ድጋፍ እጅግ ከፍተኛና የማይዘነጋ  ነው!

ይህም የሕዝብ ድጋፍ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚወሰዷቸው ቀጣይ እርምጃች ከጥገናዊ ለውጥ ተሻግሮ ሁለንተናዊ ዲሞክራሲያዊት አገር እውን ለማድረግ ወደሚያስችል ምዕራፍ ለማሸጋገር አቅምና ብርታት እንደሚሰጣቸው ይታመናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጎጃም ክልል ይመስረት ስንል ዘረኝነትን መዋጋታችን ነው (ከይገርማል)

ይህም በመሆኑም ሕዝብ በደረሰበት ፈተናና ምሬት የፍርኃት ቆፈኑን ሰብሮ በነቂስም አደባባይ ወጥቶ እንክ እንትፍ ያሉዋቸው የሕወኃት ድርጅትና ዋነኛ መሪ ተዋናዬች እንደ ጉም አቅም ከድቷቸውና ተስፋም ቆርጠው ግንቦት ሃያንም ሽክፈው መቀሌ እንዲከቱ አስገድዷቸዋል፤

በዚህ ሁሉ የህዝባችን ብሩህ ተስፋ ውስጥ ይህንን ሂደት በእንጭጬ ለማስቀረት ጥቅሙና ዓላማው የተሰናከለበት ሕወኃትና የኢህአደግ ቅሪቶች ብዙ መፍጨርጨራቸውና ዛሬም ፈተናም መደቀናቸው አልቀረም፣ በዚህ አጭር ጊዜ ሂደት ውስጥ ለ 27 ዓመታት የተዘራው ዘርንና ጎሣን የተከተለው መርህ ያስከተላቸው የማንነት ጥያቄዎች ፣ ወደ አገር ውስጥ ከተመለሱ ስብስቦች መካከል በጎሰኝነት የሰከሩና አጋጣሚውን በመጠቀም ዓላማቸውን በሕዝብ ውስጥ ሆነው ለማሳካት የሚሰሩና በኢትዬጵያ ጥላቻ መለያየትን በሚሰብኩ ፅንፈኛ ግለሰቦችና አመለካከቶች መወጠር የኢትዬጵያን ብሔራዊ ህልውና መሠረቱን የማናጋታቸው አደጋ የደቀነው ስጋት እጅግ የከፋ ነው፤ እንደዚሁም በብሔረተኝነት የተቃኙት ክልል መንግሥታት ማየልና የፌዴራሉን አቅም መፈታተናቸው፣  የፌዴራል መንግሥቱ ዳተኛ በመሆኑ የዜጎችን የዕለት ተዕለት ሰላምና ደሕንነት የማስጠበቅና መሠረታዊ ሕግን በአግባቡ አለማስከበር አለመቻሉ በዚህ ልልነት በመላ አገሪቱ ሥርዓተ አልበኝነት በመስፈኑ በዚህ ሳቢያ የእርስ በርስ ጥቃቶች የብዙ ንፁኃን ዜጎችን ክቡር ሕይወት ቀጥፏል ፣ በሚሊዬኖች የሚገመቱ ዜጎች ከሚኖሩባቸው ቀዬዎች በግፍ  ተፈናቅለዋል ንብረታቸውንም አጥተዋል ይህም ሆኖ የተፈናቀሉትን መልሶ የሚያቋቁምና የሚጠልል መንግሥት አለማግኘታቸው በጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አስተዳደር ላይ እምነትን አሳጥቷል፤

አንድ መንግሥት እንደመንግሥት ሊወጣ የሚችላቸው መሠረታዊ እርምጃዎችና ተግባራት አለሟሟላት ሕዝባችን በጠበቀው የተስፋ ጭላንጭል ላይ ጭጋግ መሸፈኑ ዛሬ እመሬት ላይ የሚታይ ዕውነታ መሆኑን ሁላችንም እንገነዘባለን፤

ወደ ሰሞነኛው የባሕር ዳርና አዲስ አበባ ቀውስ ስንመለስ ክስተቱ ለሁሉም እንቆቅልሽ የመሆኑን ያክል ቀውሱን ተከትሎ ተያያዥነት የሌላቸው ሰላማዊ ዜጎች ፣ የፓለቲካ ድርጅትና የማሕበረሰብ ተቋማት አመራሮችና አባላት እንደትላንትናው በጅምላ መታሠራቸው በይበልጡኑ ተከስቶ የነበሩት ቀውሶች ሆን ተብለው የተወሰኑን ወገኖችን ለማጥቃትና ሰላማዊ ትግላቸውን ለማጨናገፍ በአገዛዙ ሆን ተብሎ የታቀድ ድራማ እንደሆነ ጥርጣሬ ፣ ያለመተማማመና ውዥንብር በሕዝባችን ህሊና እንዲያቃጭል አድርጓል፤

አገዛዙ ግልፅነትን ለማስፈን የክስተቱን መነሾና መንስዔ በገለልተኛ ወገን አጣርቶ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ ሲገባው ክስተቱን አግነውት የመንግት ግልበጣ ነው በሚል ሕዝብን ከማማለል ይልቅ ነገም ይኽው ዓይነት ቀውስ በሌሎች አካባቢዎች እንዳይደገም መንስዔውን ከስረ መሰረቱ ማወቅና ማከም ሲገባ ማን አደረገው ማንስ አለበት በሚል ማዘናጋት እየተኬደ ያለበት መንገድ ቀውሱን በቀውስ ለማስቀጠል አደጋን የሚጋርጥ በመሆኑ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አስተዳደር ሁኔታዎችን በማረጋጋት መነሻውን ማረቅና መለየት በዚህም ይህ ጥያቄ ምላሽ አጥቶ ለደዌው መድኃኒት ሳይገኝለት በተመሳሳይ በባሰ ቀውስ ውስጥ እንዳይገባ ጥንቃቄ ማድረግ እጅግ ይጠበቅበታል! ስለሆነም ማህበረሰቡን ክፍሎች በማሳተፍ በገለልተኝነት የተድበሰበሰውን ዕውነት ገልጦ መፍትሔ ሊያስቀምጥና ከስህተቱም ልማር ይገባል፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣን እንደያዙ ከሰብአዊ መብት ማስከበር አኳያ ሲናገሩ “ አጣርተን ዜጎችን የምናስረው እንጂ እንደትላንትናው አስረን ግን አናጣራም ” ብለው ነበር! ነገር ግን በዚህ በባህር ዳሩና አዲስ አበባ ቀውስ ሳብያ ያለአግባብ በየዕለቱ ሰዎች እየታፈኑ በመታሰር ላይ ናቸው ይህም አፈናና እስር በስቸኳይ እንዲቆም! የአብንና የባላደራው ምክር ቤት አመራርና ሌሎችም በግፍ የታሠሩት በአስቸኳይ እንዲለቀቁ በማድረግ ሁኔታውን በማረጋጋት የተከሰተውን ውጥረት ማርገብ ከቶውንም ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ አይደለም፤ ከነዚህና መሰል አለመረጋጋቶች በማርገብ ወደ ፊት በመጓዝ አገራችን አደገኛውን ግዜ እንድትሻገረው ሕዝብ የጣለቦትን እምነትና ታሪካዊ አደራውን በግልፅነትና በተጠያቂነት መወጣት ይገባል፤

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያልታሰረው ማን ነው?? (ከአንተነህ መርዕድ)

በተያያዥ ከዚህ በፊት በብዙ ምሁራንና ጠበብቶች በተደጋጋሚ እንደተገለፀው አገሪቱ የምትመራበትንና የምትጓዝበት ፍኖተ ካርታ በግልፅ ባለመቀመጡ ለአስተዳደሩ መርኃግብር  አፈፃፀም በታቀድ መርኃ ግብሮች ለመመራትና  የኢትዬጵያ ህዝብ ነገን በግልፅ አሻግሮ ማሳየት አልተቻለም! ይህንንም  ከግምት በማስገባት ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በመምከር ለሁሉም ግልፅ ሊሆን የሚችል ፍኖተ ካርታ ( Road Map ) ማስቀመጥ የግድ ይላል።

በመንግሥታዊ ከፍተኛ የሥልጣን እርከኖች የሚሰጡ ሹመቶች ህዝብ ከዚህ በፊት ያለፈባቸውን ስጋቶቹን በማያጭር መልኩ ግልፅነትና ተጠያቂነት ባገናዘበና ወደ አንድ ወገን ባላዘመመ ብቃትን፣ የአገርና የህዝብ ታማኝነትን ብቻ አካታች በማድረግ የህዝብን ስሜት በማጤን ግልፅና ታአማኒነት የተሞላበት ድልድል ማድረግ የግድ ይላል፤ በታሪክ አጋጣሚ ይህችን አገር ህልውና የማስቀጠልና አንድነቷን አስጠብቆ እውነተኛ ፍትህና ዲሞክራሲ ወደ ሰፈነባት ምዕራፍ መውሰድ በዋነኝነት በዕርስዎ እጅ የወደቀ ነው! ይህ ተግባር ውስብስብ ችግሮችን መሻገር የሚጠይቅ በመሆኑ ከቃላትም በዘለለ ከድርጅት ታማኝነት ይልቅ ለሕዝብና ለአገር ታማኝ በመሆን ሕዝብንም ብቸኛ ጉልበትዎ በማድረግ በማይናወጥ አቅዋም በዙሪያዎ ያሉትን መሳሰሳቦች በመበጣጠስ ወገን በሙሉ ልብ የጣለብዎትን አደራ በመወጣት በንግግሮ እንዳሰመሩት ኢትዬጵያን በማይናወጥ መሠረት ላይ ለማኖር ከሁሉም የአንድነት ኃይሎች ጋር በጋራ መድረክ በመምከር ለእውነተኛው የህዝብ ባለድርሻ የማሻገር ታሪካዊ ኃላፊነት በእጅዎ ነው።

በሌላም በኩል የፓለቲካ ሊህቃን ከህዝብ ጎን በመቆም ፍትህ እንዳይጓደል እውነተኛ ፍታዊ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እውን እንዲሆን ትላንት የታገልነው አገዛዝ ዛሬም በሙሉ ቁመናው እንዳለ ባለመዘናጋትና አገሪቱም የምትመራበት ሕገመንግሥት የአገርን አንድነት ለማፅናት ሳይሆን የብሔር ማንነትና ቋንቋን መሠረቱ ያደረገ ፌዴራል ሥርዓት ዛሬም መንግሥታዊ ቅርፁ እንደመሆኑ የተቃዋሚ ድርጅትቶች ሕዝብን አቅጣጫ ማስያዝ ሲገባ መሠረታዊ ለውጥ እውን ባልሆነበት ለውጡን ማስቀጠል በሚል ቧልት ሕዝብን ከማዘናጋት ተቆጥበው ሰላም እንዲሰፍን የድርሻቸውን እየተወጡ ከኢሕአደግ አገዛዝ ሽግግርን ከመጠበቅ ሰብሰብ በማለት ተዋህደው ወይንም ግንባር ፈጥረው እውነተኛ ፍታዊና ዲሞክራሲያዊ ሥርዓተ ማህበር  እውን እንዲሆን የጋራ አማራጭ አቅጣጫን መተለምና ይህም እንዲተገበር በአገዛዙም ይሁን በሕዝባችን ዘንድ ሊሰማ የሚችል አቅም መገንባት የግድ ይላል፤

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአባይ ግድብ ዲፕሎማሲ አጀንዳ! (ከግርማ ሞገስ )

አቅምን በጋራ ገንብቶ እውነተኛ ተፎካካሪ ሆኖ መውጣት ፋይዳ የሚኖረው ዛሬ አንበሳውን ድርሻ የያዘው ኢሕአደግና በተለይም የለውጥ ኃይሉ ቃሉን ጠብቆ አገሪቱን ወደ እውነተኛ ዲሞክራዊ ሥርዓት ሽግግር ጥርጊያ መንገድ መውሰድን አዛንፎ ይልቁንም ኢሕአድግን እራሱን አስማምቶ ( Consolidat ) አድርጎ በመውጣት በይበልጡኑ ይህችን አገር ወደ ባሰ አምባገነናዊ  አገዛዝ እንዳይወስድ የተቃዋሚ ድርጅቶች ከግል ማግዘፍ ፉክክር ወጥተው ተለጣፊና ተከታይም ሳይሆኑ ሂደቱ ፈሩን እንዳይለቅና አሁን በአማራው ክልል የሚታየው ፣በደቡቅ ክልል በተለይም በሲዳማ ቋፍ ላይ የደረሰው የክልል ጥያቄ ፣ አሁንም ሕወኃት መቀሌ መክተቱ ብቻ ሳይሆን ከፌዴራሉ ቁጥጥር ወጥቶ አጥፊዎችን በመጠለል የራሱን መግለጫዎች በተናጥል እያወጣ የኢትዬጵያን ውጥረት በማባባስ የሚጫወተው አደገኛ ሚና ፣ የኦሮሚያ ፅንፈኞች ያላቸውን አጀንዳ ለማሳካት የሚሄድበት መንገድ ፣ በዋና ከተማችን ከህግ አግባብ ውጭ ከተማዋን በማስተዳደር ሂደት ምክንትል ከንቲባውን ተከትሎ የአዲስ አበባ ሕዝብ ባይተዋርነት የተከሰቱ ውጥረቶች አገሪቱ በሁሉም ማዕዘናት ያጠላው አደጋ  አገሪቱንም ወደ ሁሉአቀፍ ቀውስ እንዳያስገባ እውነተኛ ተፎካካር የሚያደርግ ቁመናን በመገንባት የአገዛዙንም ሂደት በዓይነቁራኛ የመከታተል መሪ ሚና የመጫወት ታሪካዊ ኃላፊነት አለባቸው ።

በምሥራቅ ፣ በምዕራብ ፣ በሰሜንና ደቡብ በሁሉም ማዕዘናት የሚገኘው ኢትዬጵያዊ ማህበረሰባችን በጥሞና ሊገነዘብ የሚገባው የውጭም ይሁን የውስጥ ጠላቶቻችን ይህች ምትክ የሌላት እናት አገራችን አለቀላት አበቃላት እያሉ ሲያሟርቱ በሕዝቦቿ አንድነትና በፈጣሪያችን ጥበብ እንደገና ለማበብ የነበራት ተስፋ ከፍተኛ ቢሆንም ዛሬ ያንዣበቡትን አደገኛና ፈታኝ ወቅት ” በጥበብ ፣ በኢትዬጵያዊነትና ኢትዬጵያ በሚል ብቻ ”  በመሻገር እርስ በርስ ከሚያጠላልፉንና ጥላቻን ከሚያብሱ ተግባራት በመቆጠብና አደብ በመግዛት ይህችን አገር የማፅናት ታሪካዊ ኃላፊነት ከጥንት አባቶቻችን በእኛው በዛሬዎቹ እጅ በመውደቁ ይህ ትውልድ ከማንነት ጥያቄ በዘለለ ለአንዲት እናት አገር ዘብ መቆም ከምን ጊዜውም በላይ በቅድሚያ ይጠበቅብናል፤

በየፊናችን አሉን የምንላቸው የክልልም ይሁን የማንነት ጥያቄዎቻችንን አገር ስትፀናና በትግላችን ፍታዊትና ዲሞክራዊት ኢትዬጵያን በመገንባት በዲሞክራሲያዊ አግባብ ፍላጎቶቻችንን በየደረጃው ለመፍታት ጊዜና ዕድል መስጠት ይጠበቅብናል!

ይህንን ባለማድረግ ከዛሬ ነገ ችግሮቻችን በማወሳሰብ ወደ ሁሉ አቀፍ ቀውስ ውስጥ እንድንገባና እንድንበተን ለሚተጉት እድል ብንሰጥ ምን ጊዜ የዛሬው ትውልድ ፀፀት ውስጥ በሚከት የታሪክ ተወቃሽ እንደሚንሆን ልብ ልንል ይገባል።

 

“ኢትዬጵያ በልጆቿ አንድነትና ትግል ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር”

 

 

1 Comment

Comments are closed.

Share