ገዳይ ደስ አይበልህ፤ ሟችም ብዙ አይክፋህ – ግርማ በላይ

ግርማ በላይ (gb5214@gmail.com)

ሰሞነኛው የሀገራችን ሁኔታ እንደብዙውን ጊዜው ሁሉ ዕንቅልፍ ይነሣል፡፡ ካለፈው ይልቅ መጪው እያስፈራን በጭንቀት ውስጥ እንገኛለን፡፡ እንደባሕር ዳሩ ዓይነት ዕብደት በአንድ ሀገር ሲደርስ ደግሞ መዘዙ ከፍተኛ ነውና ይህን ሰይጣናዊ ዕኩይ ድርጊት ያሤሩ፣ የጠነሰሱ፣ ያስተባበሩና ያስፈጸሙ ሁሉ በጊዜ ሂደት የታሪክ ቅጣታቸውን መቀበላቸው አይቀርም፡፡ ለጊዜው ግን የተወሰነ ውዥንብርንና የአቅጣጫ መደናበርን ሊፈጥሩ እንደሚችሉ አያጠራጥርም፡፡ የንብ ቀፎ ሲነካ፣ ንግሥቲቷ ብትሞት ወይ ብትጠፋ ሌላ ንግሥት እስኪተካት ድረስ ትርምስ መኖሩ፣ ፍርሀትና ሥጋትም መንገሡ አይቀርም፡፡ ነገር ግን ሁሉም ማለፉ አይቀርምና ያ ያጽናናል፡፡ ዛሬ የገደለና ያስገደለ ነገ ተራው ሲደርስ የእጁን ያገኛል – ይህ ነገር በራሱ ባያስደስትም ፍትህን ከማረጋገጥ አኳያ ግን ትክክለኛ አካሄድ ይመስለኛል፡፡ ይሁንና የጅን እያገኙ መሄድ እስካሁን አልጠቀመንም፡፡

አማራው ክልል በአንድ ጊዜ ከአራት በላይ ከፍተኛ የሥራ ኃለፊዎችን እንዲያጣ መደረጉ፣ በሰበቡም የክልሉ ወታደራዊ ባለሥልጣናት እንዲታሰሩና ከዕይታ ውጪ እንዲሆኑ መገደዳቸው ብዙ ነገር እንድንጠራጠር ያደርገናል፡፡ መጠራጠር ሥራችን ሆኖ የቀረውም መንግሥትና የፖለቲካ ድርጅቶች ግልጽነት ስለሚጎድላቸውና ሁሉንም ነገር – ትንሹንም ትልቁንም – በምሥጢር ስለሚይዙ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ “እሁድ”ን እንኳን “እሁድ” ማለት – ይህን በጣም ቀላሉን ነገር ሳይቀር የሚደብቁ ተፈጥሯቸው ድመት የሆኑ ዕንቆቅልሽ ፖለቲከኞች አሉን፡፡ አንድ ነገር በግልጽ ካልታወቀ ደግሞ ለመላምትና ለአሉቧልታ ወሬ ያጋልጣል፡፡ ሁሉም እየተነሣ ያሻውን ሲናገር እውነት በመሀል ትሰወርና ሕዝብና አገር በሚያምታቱ ወሬዎች ይተራመሳሉ፡፡ እኛ ጋ እየሆነ ያለው ይሄው ነው፡፡ እውነትን ለመደበቅ የሚጥር ሰው ደግሞ ልዩ ተልእኮ ያነገበ ነው፡፡ ከሕዝብና ከሀገር ጥቅም ይበልጥ የራሱን ጥቅምና ፍላጎት የሚያስቀድም ዜጋ ወንበር ከያዘ ችግሩ ዘርፈ ብዙ ነው፡፡ ካለፉት 40 እና 50 ዓመታት ወዲህ ሀገራችንን እየተጠናወታት ያለው ራስ ምታትም ይሄው ነው – የራስን ጥቅምና የሥልጣን ሱስ ከሀገር ማስቀደም ይቅር የማይባል ወንጀልና ኃጢኣት ነው፡፡

በበኩሌ ከሚባለው ነገር ሁሉ ተነስቼ ይህን የባሕር ዳሩን አስቀያሚ ተውኔት “እገሌ አከናወነው፣ እነእገሌ ፈጸሙት” ወደሚል አሳሳች ፍርድ መግባት አልፈልግም – ነጥቦችን ወደ መገጣጠም የአምቼ ሥራም አልገባም፡፡ ይልቁንስ አጠቃላይ ስለሆኑ ነገሮች ትንሽ ማለት እፈልጋለሁ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የመደራጀት መብት ግዴትም አለበት (ይገረም አለሙ)

ገዳይ ማንም ይሁን ማን ባሰበው መንገድ ዓላማውን እስከወዲያኛው ሊያሳካ አይችልም፡፡ በመግደል የትም አይደረስም፡፡ እንደተባለውም  በርግጥም መግደል መሸነፍ ነው፡፡ በሃሳብ ጦርነት እንደማያሸንፍ አስቀድሞ ያመነ አካል ግድያንና እሥርን በአማራጭነት – ፕላን ቢ እንደሚሉት ዓይነት – ይይዝና በሃሳብ በርትተው የሚሞግቱትን በጉልበት ያጠቃል፡፡ ይህ ከንቱነት ነው፡፡ ዛሬ የገደለ ነገ ይገደላልና በመግደል አንድን ዓላማ በምንም መንገድ ከግብ ማድረስ አይቻልም፡፡ እርግጥ ነው – በመግደል ጊዜያዊ ድልና አጋንንታዊ እርካታ ሊገኝ ይችላል፡፡ ይሁንና ኅሊናን ጥቀርሻ አልብሶ በጥፋትና በደም ጎርፍ የሚገኝ ድል እውነተኛ ደስታን ካለመስጠቱም በተጨማሩ የገዛ መጥፊያ መሣሪያን በገዛ እጅ እንደማዘጋጀት ነው፡፡ ወደኋላ ዘወር ብለን ማየት እንዳንችል እልህና በቀለኝነት ሰቅዘው ይዘውን በእውር ድንብር ስለምንጓዝ እንጂ ይህ የግድያና የመበቃቀል አካሄድ እንደማያዋጣ ከታሪካችን እንኳን ብዙ መማር በተቻለን ነበር፡፡ ሥልጣንና ሀብት ግን መላ ሰውነትን ስለሚያሳውሩ ሰዎች ይህን ነባራዊ እውነታ መረዳት አልቻልንም፡፡ የሚታየን ጭብጨባው ነው፡፡ የሚታየን አጀቡና ነገ ስንወድቅ የሚከዳን የዜጎች አሸርጋጅነት ነው፡፡ የሚታየን የፕሮቶኮል ሽርጉዱ ነው፡፡ ፊት ለፊታችን የሚደቀንብን የዓለምን ሚዲያዎችና የዜና ሽፋኖች መቆጣጠራችን ነው፡፡…

የተደረገው “መፈንቅለ መንግሥት” ብዙ ነገር አሳጥቶናል፡፡ በተለይ አማራውን ብዙ የዕዳ ቁልል አስቀምጦበታል፡፡ ከድንጋጤና ሀዘን ለመውጣት ራሱ ጊዜ ይፈጃል፡፡ የጥቃቱ ጠንሳሾች እነማንም ይሁኑ እነማን በዚህ መሀል ግን “የገበያ ግርግር ለሌባ ያመቻል” እንዲሉ ነውና አማራን እንደሣንዱዊች መሀል አድርገው ለማጥቃት ያሰፈሰፉ ኃይሎች ሠርግና ምላሽ ሆኖላቸዋል – ለጊዜው ነው፡፡ ይህን ድርጊት ማንም ይፈጽመው የአሁንና የወደፊት የዞረ ድምሩ ለማንም እንደማይበጅ ሁሉም ሊገነዘበው ይገባል፡፡ የደፈረሰ መጥራቱ፣ የተደበቀ መውጣቱ ደግሞ የታወቀ ነው፡፡ አንድን ነገር ለዘላለም መሠወር አይቻልም፡፡ እንዲያውም በደበቅኸው ቁጥር ጎልቶ የሚወጣው ብዙ ነው፡፡ በዚያ ላይ የጎን ጉዳቱ ከሁሉም የባሰ ነው፡፡ ሌባ ሲሰርቅ “ከባለቤቱ የበለጠ አልኮነንም” ይላሉ አሉ፡፡ ለምን ቢባል ባለቤቱ የቅርብ ንጹሓን ጓደኞቹን ሳይቀር በስርቆት ይጠረጥራቸዋልና፡፡

አንዳንድ እውነታዎች፡፡

ትግራይ በፊት መስመር ተሰላፊ የኦሮሞ ድርጅቶች (ኦህዲድ/ኦነግ…) ከሚመራው የፌዴራል ተብዬው መንግሥት እጅ ወጥታለች፡፡ ይህች ግዛት የማትበላ የረጂም ዛፍ ላይ ፍሬ ከሆነች ውላ አደረች፡፡ ይህን እውነታ የሚረዳ ዓለም አቀፍ ኃይል አለ፡፡ ይህ ኃይል አራት ኪሎ ላይ ያስቀመጠውን ወኪሉን እንደማማከሩና ትዕዛዝ መሰል መመሪያ እንደመስጠቱ ተመሳሳይ ግዛት ተፈጥሮ ከፌዴራሉ የበላይነት ሥልጣን እንዳይወጣ በጊዜ የጮኸን ጅብ አደብ ማስገዛት እንደሚገባ ለተረኛው ዘረኛ አገዛዝ ማሳሰቡ አይቀርም፡፡ የአማራው ክልል አንዳንድ ባለሥልጣናት ሕወሓት የቀየሰላቸውን ፈለግ ተከትለው በብሔርተኛነት ስሜት አማራ አማራ እያሉ መደራጀትና ኃይልን ማዳበር ተያይዘው ነበር፡፡ በማጎብደድ ሥነ ልቦና የሚታወቀው የአማራ ክልል ወካይ ነው የሚባለው ድርጅት ግን የተሰጠው አንጻራዊ ነጻነት እጅግ ውሱን መሆኑን የተረዳ አልነበረም፡፡ ትልቅ ሕዝብ ይዞ በአብዛኛው በሠርጎ ገብ ድቅል አማሮች የሚመራው ይህ ድርጅት ክልሉን የጥቂቶች ፀረ-አማራ ድርጅቶች መናኸሪያ አደረገው፡፡ ስለዚህም የክልሉን መብት ለማስጠበቅ የሚያደርገው እንቅስቃሴ ሁሉ በነዚህ ጥቂት ባለጊዜዎች ራዳር ውስጥ መግባቱ አልቀረም፡፡ በሌላ ረገድ ሥጋን ሰጥቶ ቢላዎን የመከልከል ዓይነት “በብሔራችሁ ተደራጁ፤ ግን ትጥቅና ስንቅ አይኑራችሁ፤ የሚመጣባችሁን ጥቃት ሁሉ በዱላ ብቻ ተከላከሉ” የሚል የበላይ ትዕዛዝ ያልተዋጠላቸው የአማራ ክልል ኃላፊዎች ራሳቸውንና ክልሉን ከጠላት ለመከላከል የሚያስችል አቅም በመገንባት ረገድ ደፋ ቀና ይሉ ነበር፡፡ ሌላው ቀር በኒኩሌር ሳይቀር የሚጠረጠር “ክልል” መኖሩን እንደማናውቅ ክላሽን መታጠቅም እንደብርቅ ተቆጥሮ የአማራ ክልል ይወገዝና መሪዎቹም ይብጠለጠሉ ገቡ፡፡ “ነጠብጣቦችን ሙሉ”…

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሕልውናው አደጋ ያንዣበበት ታሪካዊው የላሊበላ ቅርስ ደብር (ከ ሙሉጌታ ገዛኸኝ)

የአማራ ብሔርተኝነትን የሚያቀነቅኑ ፀረ-አማራ ኃይሎች (ሕወሓትና ኦነግ/ኦህዲድ) “ያውጡብሽ እምቢ ያግቡብሽ እምቢ” አለች እንደተባለችው ሴትዮ የአማራን መደራጀት ይወዱታል ይጠሉታልም፡፡ የሚጠሉት ኃይሉንና ተፅዕኖውን ስለሚፈሩት ነው፡፡ የሚወዱት እንደነሱው ጠባብ ብሔርተኛ እንዲሆንላቸውና ሌሎች ብሔረሰቦችን ለመዋጥ እንዲመቻቸው፣ በእግረ መንገድም ኢትዮጵያን አፍርሰው ማንም እንደልቡ የሚፈነጭባት የተበታተነች ሀገር እንድትሆን ስለሚፈልጉ ነው፡፡ ይህ ሁኔታቸው እነዚህን አካላት የሁለት ተቃራኒ እምነቶች ተከታይ እንዲሆኑ አስገድዷቸዋል፡፡ በመሠረቱ አንድ ሰው ሁለት የተለያዩ ነገሮችን በአንዴ ሊወድ ወይ ሊጠላ አይችልም – እንዲያ ካደረገ ጤነኛ አይደለም፡፡ የሆኖ ሆኖ ይህ የ“አስቸጋሪ እንግዳ ተዘቅዝቆ ይተኛል” ዓይነት ክስተት በሀገራችን ተፈጥሯል፡፡ ይህን የአማራን መደራጀትና መጠናከር ያልፈለጉ ወገኖች … “ነጠብጣቦቹን” ራሳችሁ ግጠሙ፡፡

እንግዲህ የሆድን ሁሉ ቢያወጡት ሆድ ባዶ ይቀራል፡፡ ግን ዋናው ጉዳይ ዛሬ የሞተ አምባቸው፣ ዛሬ የሞተ ሰዓረ፣ ዛሬ የሞተ አሣምነው… አፈር አያሟሹም፡፡ ሞት ለነሱ የመጀመሪያ ቢሆንም ለሰው ልጅ ግን ለማንም የማይቀር የአዳምና የሔዋን ዕዳ ነው – የመቀዳደም ጉዳይ ነው፤ መግደል ጅልነት የሚሆነው ለዚህ ነው፡፡ ትናንት የሞቱ ጓደኞቻቸውንና የሰው ዘሮች ሞት ነው እነሱም ሰሞኑን የሞቱት፡፡ በነሱ ላይ ጨክኖ ቃታውን የሳበ ወንጀለኛ ሰው ከተኮሰባት ደቂቃ ጀምሮ ለስንት ሰዓትና ደቂቃ በሕይወት እንደሚቆይ አያውቅም፤ የመቆየት ዋስትና የሚሰጠውም የለም፡፡ የምንተላለቀው ዝም ብለን ነው፡፡ መተላለቃችን የሚያሳየው ዓለም ወደፊት ስትራመድ እኛ ኢትዮጵያውያን ግን በብርሃን ፍጥነት የኋሊት እየተሸቀነጠርን መሆናችንን ነው፡፡

በሀገራችን የማየው ዜጎችን አላግባብና በሥጋት ብቻ ከያሉበት እየያዙ ማሰሩም እጅግ የሚያሳፍረኝና የሚያሳዝነኝ ጉዳይ ነው፡፡  አእምሯችን ማሰብ አቁሟል፡፡ ዐይኖቻችን ማየት ተስኗቸዋል፡፡ ጆሯችን ማድመጥን ዕርም ብሏል፡፡ ከእንስሳነት ደረጃም ወርደን የለየልን ጨካኝ ዐውሬ ሆነናል፡፡ ሰው ሰው የማንሸት ግዑዝ ፍጡራን እየሆን ነው፡፡ ከሆድ ባልወጣው ስብዕናችን ንጹሓንን እየገደልንና እያሰርን የትም እንደማንደርስ ማወቅ ነበረብን፡፡ የትናንትን የጠነባ ዘረኝነት የጎሣ ማርሽ ቀይረን ዛሬም እንደትናንቱ የሚከረፋ ማኅበራዊና መንግሥታዊ ሥርዓት ዘርግተናል፤ በዚህም ከመኩራራት በስተቀር አካሄዳችንን ለማስተካከል ምንም ዓይነት እርምጃ ስንወስድ አንታይም፡፡ በትምህርት ደረጃችን በዓለም አንቱ የተባለ መጠሪያ ቅጽል ከስማችን በፊት ብናስቀምጥም በአስተሳሰብ ግን በትንሹ ከአንድ መቶ ዓመት በፊት ከነበሩ አያት ቅድመ አያቶቻችን እንኳን የማንጠጋ ማፈሪያዎች ነን፡፡ ሰው ጎራ ለይቶ ጓስ ይጋጠማል እኛ ግን ጎራ ለይተን በዘር እንጨራረሳለን፡፡ ከዚህ በላይ መረገም በየትም ዓለም የለም – አሁንና ዱሮም ምናልባትም ወደፊትም፡፡ ኢትዮጵዊነት ከዚህ ዘመን በላይ ሊያሳፍር አይችልም፡፡ መጥኔ ለቀሪ! እንግዲህ ምን ይዋጠን? ሌላ ምርጫ ከሌለን እንጸልይ፡፡ የርሱ ከሁሉም ይበልጣልና፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአቢይና ጓደኞቹ በሽታ ከሌሎች ይለያል! - ይነጋል በላቸው

“There are many things worth living for, a few things worth dying for, and nothing worth killing for.”  Tom Robbins

“ልንኖርላቸው የሚገቡን በርካታ ምክንያች አሉ፤ ልንሞትላቸው የሚገቡን ጥቂት የማይባሉ ምክንያቶች ደግሞ አሉ፤ ልንገድልበት የሚያበቃን ምክንያትና ተጠየቃዊ አካሄድ ግን ፈጽሞ የለም፡፡”

የጥቅሱ ምንጭ፡- ኢንተርኔት

1 Comment

  1. Ha..ha..”yet hije lifenda!” I really cracked laughter when I read this paragraph.

    “…….. ሌላው ቀር በኒኩሌር ሳይቀር የሚጠረጠር “ክልል” መኖሩን እንደማናውቅ ክላሽን መታጠቅም እንደብርቅ ተቆጥሮ የአማራ ክልል ይወገዝና መሪዎቹም ይብጠለጠሉ ገቡ፡፡

    What kind of person would make such an assumption?
    1. Lacks knowledge of what it takes to acquire a nuclear armament.
    2. Extremist out of self-interest – deliberate disinformation to agitate others.
    3. Someone who is suffering from “Schizophrenia” (a brain disorder that affects a person’s ability to think, feel and behave clearly. Symptoms include, delusions, hallucinations, trouble with thinking and concentration, and lack of motivation.)

Comments are closed.

Share