ሀገሬ ናፈቀኝ / ከግርማ ቢረጋ

ሃገሬ ናፈቀኝ ወንዟ ሸንተረሯ

ናፈቀኝ ሃገሬ ነፃነቷ ክብሯ

ትዝታ ኑሮዋ ባህል ቁም ነገሯ ።

 

ያሳለፍኩት ሁሉ እየመጣ በእውኔ

እንቅልፌንም ነሳኝ ተሰማኝ ኩነኔ ።

 

መንደሬ ሰፈሬ አስፋልት ኮረኮንጁ

ቂማውና ጨብሲው > ጠላውና ጠጁ ።

 

ከረንቦላው ኳሱ ድራፍት ካቲካላው

ብትለው ብትጠጣው ሆድን የማይሞላው።

 

ጣፋጭ ትዝታዋ ሃገሬ ናፈቀኝ

እራቀኝ ሄደብኝ ከቶውን ላይገኝ ።

 

ከቤላ ፈረንሳይ ስድስት ኪሎ ሄጄ

ጭንቀት ሳይኖርብኝ ሽቅብ ታች ወርጄ።

 

 

የኖርኩበት ዘመን ላይገኝ መልሶ

ሊታለፍ የማይችል ፍፁም ተደባብሶ ።

 

 

ሃገሬ ናፈቀኝ ሰላምሽ ትዝታሽ

ቀድሞ የነበረው ወዘና ቁመናሽ ።

 

ከቶ ይናፍቀኛል እንዴት ልሁን ታዲያ

አልፈልግም ልትሆኝ ብቻ መቀበሪያ ።

 

 

ስደት የተባለ ወረርሽኝ ውጦኝ

ከሰፈር ቀበሌ ከጓደኛ አርቆኝ ።

 

ሃገሬ ናፈቀኝ ሆድ ባሰኝ ዘንድሮ

የማይወጣ ነገር ልቤ ውስጥ ተቀብሮ ።

 

ጭራሽ አይረሳም ፈረንሣይም ቤላ

ፍቅር የሞላበት ያደግኩበት ሁላ ።

 

ዜሮ አምስት ውቅያኖስ ቀጭ ቀጭ ሃሰን ሱቅ

በቡዜ ቀብራራው የነበረንን ሳቅ

እንዴትስ ይረሳል ለምንስ አይናፍቅ ።

 

ጃልሜዳ ወጥቼ ቅሜ ተጫውቼ

ጨፋናው ቴዲዬን ሃረሩን አግኝቼ

በቁኮ እና ለጌ ሻለቃን አውርቼ ።

 

የሽፌ ጨዋታ ጌቾ ትህትናው

የፈረንጅ አፉ የቋንቋ ችሎታው

ወልድዬ ወላሞ ነብስህን ይማረው ።

 

ሳቅና ጨዋታው ተካፍሎ መብላቱ

ትዝ አለኝ ሃገሬ ትዝ አለኝ የጥንቱ

ሃገሬ ናፍቆቱ ሃገሬ ስስቱ

ርቆ የሄደን  ሰው ወይ  ማሰቃየቱ ።

 

ጃልሜዳ አራት ኪሎ ቶታል ስድስት ኪሎው

ተጨማሪ ያንብቡ:  በወያኔ “ያደገችዋን” ኢትዮጵያ ዓለም እንዴ ያያታል?- ዶ/ር ዘላለም ተክሉ

የነ አይሰጬ ፈድሉ ሺሰማ ትዝታው

የጊቢው ተማሪ መጥተው ተኮልኩለው ።

 

ጠረባ ትረባው በአረንጓዴ ምላስ

ያ ጊዜ ተገኝቶ ምነው ባይበላስ ።

 

ለመርሳት ብሞክር ዜሮ አምስትን ከልቤ

ጃልሜዳ ጉልትን ላወጣው ከቀልቤ

አልሆንልህ አለኝ መጣ በምናቤ ።

 

ነበረኝ ብዙ ሙድ መገናኝ ገርጂ

ብዙ የሚናፍቀኝ የኖርኩበት ደጅ ።

 

ጉለሌ ጋሽ መጋል ወርቁ ሸክላ ሄጄ

ጳውሎስን አልፌ ኳስ ሜዳ ወርጄ ።

 

ኢዲዩን ጎብኝቼ ስሄድ ዳትሰን ሰፈር

የክትፎውን ጣባ ዮሃንስ ስንሰብር ።

 

 

በቅዳሜ  ጠዋት ሾሌ ነጭ ጠላ በዞረ ጢንቢራ

ጨጓራው ተበልቶ ደልቶን ስናጓራ

ሃገሬ ናፈቀኝ የአራት ኪሎ ቢራ ።

 

ሰብለ ቤት ጨልጬ ሶሎ ቤት ስሸና

ይገቤ አልማዝ ቤት የጆሊ ባር ቡና ።

 

ካሳንቺስ ክትፏችን ከተማ ቤት ቢራ

የመጨረሻዬን ቺርስ ያልኩበት ተራ ።

 

ከወዳጆቼ ጋር የመለየት ለቅሶ

በአረቄና ቢራ ፍፁም ተለውሶ ።

 

ከቶ አይረሳኝም ነብስ ይማር መንግስቱ

ተጫዋች አሳቢ አንተ የኔ ከንቱ ።

 

ተቃቅፈን ተላቅሰን የሸኛችሁኝ ግዜ

ተክሎብኝ የቀረው ሃሳብ ከትካዜ።

 

ሼህ ዑመር ባህሩ ብሬ እና ውዶቹ

ከቶ እንዴት አድርጌ ከልቤ ላውጣችሁ ።

 

አርቆ የሸኘኝ  ላይመልሰኝ ግዜ

ሃገሬ ናፈቀኝ ተጫነኝ ትካዜ።

 

የኤጀርሳ ጎሮ የጎድን ጥብስ ሽታ

የታምራትን ቤት ኡኡታ ጫጫታ ።

 

ትዝ አለኝ ሃገሬ ናፈቀኝ መንደሬ

ስጎነጭ ስጨልጥ ከናፋቂው ወሬ ።

 

ፍፁም አይረሳም የአራት ኪሎ መንገድ

ከሥራ በኋላ ያለው  መንጎራደድ ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሕዝባዊ ዕንቢተኝነት ለኢትዮጵያ ትንሳኤ!

 

በሞት ያጣዋቸው ወዳጅ ዘመዶቼ

ከቶ ላልረሳችሁ በልቼ ጠጥቼ

ከነጫጮቹ ምድር ጠፋሁኝ ሰስቼ ።

 

ጥዬው እንዳልመጣ እሩጬ ፈርጥጬ

የያዘው ይዞኛል ዝቅ  አርጎኝ ከአገጬ ።

 

አይመስለኝም ነበር ልቆይ እንዲህ እርቄ

በሃገር በህዝቤ ሁሌ ተጨንቄ ።

 

ልብ አቅም ሲደክም ሲወርህ እርጅና

ይናፍቃል ቀዬ የሰፈር ጓደኛ ።

 

 

ግና ለምን በኔ ስደት ጨከነሳ

ወይስ እኔ ፈራው አበዛው ወቀሳ ።

 

ሃገሬ ናፈቀኝ ወንዟ ሸንተረሯ

ናፈቀኝ ሃገሬ ነፃነቷ ክብሯ

ትዝታ ኑሮዋ ባህል ቁም ነገሯ ።

 

ሜይ 2019

ግርማ ቢረጋ / ስቶክሆልም

 

Share