ወጣት ሆይ! እደግ! ተመንደግ! – በላይነህ አባተ

በላይነህ አባተ  (abatebelai@yahoo.com)

እያፈጀ ያለው ትውልድ ከባህሉ ከወጣ ቢያንስ ከሃምሳ አመታት በላይ ሆኖታል፡፡ የጀግኖች መፍለቂያ የጎበዝ አለቃ ባህላችንን በመጤ የጥበቃ ጓድ ተክቷል፡፡ መለኮታዊ ሽምግልናችንን በኤፍሬም ይሳቃዊ መጤና ውርጃ ድርድር አበላሽቷል፡፡ በእግዚአብሔር ሚዛን የሚፈርዱ ካህኖቻችንን በወሮበላ ደፍተሮች ተክቷል፡፡ የእውነተኝነትና የታማኝነት ባህላችን በቅጥፈትና በክደት ባህል ተክቷል፡፡ በፍቅር የተሞላ ጉርብትናችንን በጥላቻ ድንበር አጥሯል፡፡ ስንት ጀግና ያፈለቀውን የዘፈን፣ የሽለላና የፉከራ ባህላችንን በፈረንጅ ሙዚቃና ዳንኪራ አድቅቋል፡፡

ዛሬ ግን ይህ እያፈጀ ያለ ትውልድ ለጅብ አሳልፎ የሰጠው አዲሱ ትውልድ በጥረቱ ጭንቅላቱን አስልቶ፣ አንገቱን አቅንቶና ክንዱን አፈርጥሞ ታሪኩንና ባህሉን ከሚደርስበት ጥፋት ተከላክሎ ወደነበረበት ለመመለስ እሚያደርገው ጥረት እደግ ያሰኛል፡፡

በዚህ እያፈጀ ባለ ትውልድ ዘመን በደኖው የዘር ማጥራት ዘመቻ ባለቤታቸው ገደል ተወርውረውና አስራ ሶስት ልጆቻቸው ተበትነው ከአምሳ በላይ “ወታደሮች” በየተራ ደፍረዋቸው ከማህጸናቸው መግል ሲፈሳቸው ያየኋቸው የአምሳ አመት እድሜ እናት እስከ ህይወቴ ፍፃሜ እንዳሳዘኑኝ ይኖራሉ፡፡ አማራ እንደ ድኩላ የታደነባቸው ወልቃይትና ራያ፣ በሬሳ የተሸፈነው ጋንቤላ፣ የወንድሙን አስከሬን እንዲጎትት የተገደደበት ኦጋዴን፣ እናት “ወታደሮች” ከገደሉት ልጃቸው ሬሳ እንዲቀመጡ የታዘዙበት ወለጋ፣ ሕዝብ በጅምላ የተጨፈጨፉባቸው ከተሞች፣ አማሮች የአርበኛ አያቶቻቸው አጥንት በተከሰከሰበት ስደተኛ የሆኑባቸው ጉራፈርዳ፣ መተከል፣ ኢሉባቦር፣ ለገጣፎ እንደዚሁም ዜጎች የታረዱባቸው ሌሎች አካባቢዎች እድሜ ጠጋቡን አድርባይና ሆዳም ትውልድ ሲወቅሱት ለዘላለም ይኖራሉ፡፡

ይህ እድሜውን እየጠገበ ያለ ትውልድ እስክስታ መውረድ፣ ማቅራራት፣ መፎግላትና መፎከር የኋላቀርነት ምልክት ስለመሰለው ራሱን ለምዕራባውያን የባህል አስገዝቶ በተውሶ ዘፈንና ዳንኪራ ሲወላገድ ኖሯል፡፡ መሰልጠን በህሊና መገዛት መሆኑን ስቶ መሰልጠንን እንደ ፈረንጅ መልበስ፣ እንደ ፈርንጅ መናገር፣ እንደ ፈረንጅ መዝፈን፣ እንደ ፈረንጅ መደነስና እንደ ፈረንጅ ማምለክ አድርጎ ወስዶታል፡፡ ምዕራባውያን በአሕዛብነት እንደ አውሬ በሚኖሩበት ዘመን ኢትዮጵያ በህሊናው የተገዛ ስልጡን ሕዝብ አገር እንደነበረች ዘንግቶ እንደ ምዕራባውያን “ለመሰልጠን” ከኮሚኒዝምና ከካፒታልዚም ጋር ባህላቸውን እንደ መርዝ ሳያጣጥምም ሰርብቋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኧረ ቄስ ጥሩ ሰወች ! - ቀሲስ አስተርአየ

ይህ የምዕራባውያንን መርዝ ሳያጣጥም የመሰርበቅ ባህሪውም አባቶቹ ከቆሙበት ክብር ሥሩ እንደተመነገለ ዛፍ ገንድሶ ጥሎታል፡፡ አባቶቹ ከቆሙበት ክብር ተገንድሶ ሲወድቅም ምዕራባውያን ለክብር፣ ለህሊናና ለይሉኝታ ባዕድ የሆነውን የትግሬ ነፃ አውጪ እንደ ምሳር በእጅ አንስተው ከትክተውታል፡፡ የራሱን ባህል ብልኮ አውልቆ የሌላውን የባህል ጀርሲ የለበሰ እጣፋንታው እንደ በሰበሰ ዛፍ መከትከት መሆኑን ከዚህ በላይ ምን ያሳያል?

በምዕራባውያን ርዕዮተ ዓለምና ባህል መርዝ አባቶቻችን ከቆሙበት የክብር ተራራ ሥሩ እንደተመነገለ ዛፍ በተገነደስነው በዚህ ትውልድ አፍሮ ለግላጋው ትውልድ በቅድመ አያቶቹ እየተጠራ ይገኛል፡፡ ይህ ትውልድ ከወደቅንበት ትቢያ ተነስቶ ከቅደመ አያቶቹ ማማ ለመውጣት መፍትሔው የቅደመ አያቶቹን ፈለግ መከተል እንደሆነ ተገንዝቧል፡፡ ይህንን መፍትሔ ስላወቀም የቅደመ አያቶቹን ታሪክ እንደ ቅርስ ተመራማሪ በመቆፈር ላይ ይገኛል፡፡ ቅደመ አያቶቹን በጀግንነት መንፈስ ያጠመቃቸው ባህላቸው መሆኑን ተረድቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ይህ ለግላጋ ትውልድ ማፈሪይው ትውልድ እንደ ዛር የጣለውን የጀግና ምንጭ ባህል እንደ ታቦት በክብር አንስቶ ከራሱ ለመስቀል ሲፋትር ይታያል፡፡

ይህ ቅደመ አያቶቹን አክባሪ ትውልድ የማህበረሰብ መሪውን እንደ ቅድመ አያቶቹ የጎበዝ አለቃ ማለት ጀምሯል፡፡ ይህ ለግላጋ ትውልድ እንደ በከነው ትውልድ በማያውቀውና በማይችልበት የማይክል ጃክሰን ዳንስ በሃያ አምስት ዚፖች በተጣበቀ ጃኬት ወይም እንደ አቦይ ገረመድን ወዳጅ ቦይንሲ እርቃኑን መወላገዱን ትቶ እንደ ቅድመ አያቶቹ በሸማና በጃኖ ተውቦ በአገሩ ዘፈንና ጭፈራ ያገሩን ውበት፣ ታሪኩንና ጀግኖቹን መዘከሩን ተያይዞታል፡፡ ይህ ትውልድ ቀረርቶና ፉከራን የትግሬ ነፃ አውጪ ከቀበርበት መቃብር አውጥቶ እንኳንስ በገጠር በከተማ ነፍስ ዘርቶበታል፡፡ ይህን ባህል መልሶም ከአያቶቹ ማማ ያደርሰዋል የሚል ተስፋ አሳድሯል፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ልበ ደንዳና፣ አንገተ ወፍራም መሪ ፕሮፋይል እና ከቨር ፎቶ መቀየር ውስጥ ይደበቃል - ዩሀንስ ሞላ

ከባህሩ የወጣ አሳ ወዲያው ወደ ባህር ሲገባ ነፍስ እንደሚቀጥለው ከቅደመ አያቶቹ ባህል ያወጣነው ይህ ትውልድም ባህላችን ጨርሶ ሳይጠፋ ወደ ቅደመ አያቶቹ ባህል ስለገባ እንደ ቅድመ አያቶቹ ተጀንኖ ከተራራ የመታየት እድል ይኖረዋል፡፡ ከንቱው ትውልድ ከባህሉ ወጥቶ ለቅኝ አገዛዝ የዳረግነው ይህ ወጣት በባህሉ መዋኘት ሲቀጥል በዘፈኑ፣ በቀረርቶውና በፉከራው አንስቶ እማይጠግባቸውን ቅድመ አያቶቹን የመሳሰሉ ጀግኖች የመፍጠር ብቃት ያዳብራል፡፡

ታሪክ እንደሚመሰክረው የዚህ ትውልድ ቅድመ አያቶች ባህል ጀግና እንደ ፊደል ይዘራል፣እንደ እሸትም ያፈራል፡፡ የዚህ ትውልድ ቅደመ አያቶች ባህል እንደ አቡነ ጴጥሮስ፣ አቡነ ሚካኤል፣ አባ ገብረየሱስ፣ መላከ ብርሃን አድማሱ ጀምበሬ፣ መላከ ሰላም አለማየሁ ሻሾና ነቢዩ ሼህ ሁሴን የመሳሰሉ ብቁ የሃይማኖት አባቶች ያወጣል፡፡ የዚህ ትውልድ ቅድመ አያቶች ባህል የመለኮትን ፍርድ የሚፈርዱ ሀዲስ አለማየሁን የመሳሰሉ ሽማግሌዎች ይፈጥራል፡፡

ይህ ትውልድ የቅድመ አያቶቹን ጀግና አፍላቂ ባህል ተጎናፅፎ እንደ ቅድመ አያቶቹ ተጀንኖና በዓለምም እሚገባውን ሥፍራ ይዞ የመኖር እድል ይኖረዋል፡፡ ይህ ትውልድ የባህሉ ስሌት የገባው ይመስለኛል፡፡ ስሌቱም ስለገባው በወኔ እየዘለለ ከባህሉ ባህር በመግባት ላይ ይገኛል፡፡ ይህ ትውልድ የቅድመ አያቶቹን ፈለግ ተከትሎ በባህሉ እየጎለበተ እንደ ቅድመ አያቶቹ አገሩን የአገር አውራ አድርጎ በዓለም ተከብሮ ይኖራል፡፡

ይህ ትውልድ “የተማሩ” አባቶቹ “ለመሰልጠን” የወረወሩትን ጃኖ አንስቶ ለብሷል፡፡ ይህ ትውልድ “የተማሩ” አባቶቹ “ለመሰልጠን” ያቀነቀኑትን የፈረንጅ ዜማ እንደ አተላ ደፍቶ ያገሩን ጣዕመ ዜማ አንቆርቁራል፡፡ ይህ ወጣት “የተማሩ” አባቶቹ “ለመሰልጠን” በኋላቀርነት የተሳለቁበትን ቀረርቶና ፉከራ እርሱ ኮርቶበት አራዳ ጊዮርጊስ ሳይቀር ተፎግሎበታል፡፡ ይህ ወጣት “የተማሩ” አባቶቹ  “ለመሰልጠን” የተደፈቁበትን የፈረንጅ ባህል ተጠይፎ በቅደመ አያቶቹ ባህል እንደ አሳ መዋኘት ጀምሯል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያ፡ አላቻ ጋብቻ - ዶ/ር ዘላለም እሸቴ

ይህ ባባቶቹ አፍሮ በአያቶቹ የሚምል ወጣት ያስደስታል፤ እደግ ተመንደግም ያሰኛል፡፡ ወጣት ሆይ! እደግ! ተመንደግ!

 

ሚያዚያ ሁለት ሺ አሥራ አንድ ዓ.ም.

Share