November 26, 2018
20 mins read

የማይቀጡት ልጅ ሲቆጡት ያለቅሳል – ይሄይስ አእምሮ

ወያኔዎች ያላሰቡት ዱብ ዕዳ ወርዶባቸው በአሁኑ ወቅት ይሠሩትን አጥተዋል፡፡ ትግራይን ቀደም ካለ ጊዜ ጀምሮ ከተለያዩ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ገጽታዎች አንጻር እንሰማቸው ከነበሩ መጥፎ ንግርቶች ለማዳን የተያዘውን ብሔራዊ ጥረት ለማኮላሸት ዘርፈ ብዙ ጥረት እያደረጉ ይመስላሉ፡፡ እነዚህን አስቀያሚ ትንቢቶች ቢቻል ለማስቀረት ባይቻል ለማለዘብ እንዲቻል ትንቢቶቹን የማያውቋቸውና ምናልባትም ስለመነገራቸውም ያልሰሙም ሆኑ የነገሮች አካሄድ ያላማራቸው አንዳንድ ኃላፊነት የሚሰማቸው ወገኖች እያደረጉት ያለውን የሞት የሽረት የሚመስል ትግል ዋጋ ለማሳጣትና በውጤቱም የራሳቸውን የግል ፍላጎት ለማስቀጠል የማያደርጉት ሙከራ የለም፡፡ በጥንካሬያቸው ዘመን እንዳሉ ለማስመሰል በተቆጣጠሩት ሚዲያ የማይረጩት የጉራና የትዕቢት መርዝ ደግሞ አይጣል ነው፡፡ ትግርኛ የሚሰማ ሌላ ወገን ያለም አልመሰላቸውም፡፡

እኛ ኢትዮጵያውያን በየቋንቋችን እጅግ ማለፊያ የሆኑ አባባሎች አሉን፡፡ እስኪ እነዚህን ለአብነት ያህል እንመልከት፡-

 

በፊት ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ፤

አሁን ምን ያደርጋል ወጪት ጥዶ ማልቀስ፡፡

 

አይነጋ መስሏት “ቋቷን አበላሸች”፡፡

እናቱ ወንዝ የወረደችበትና የሞተችበት እኩል ያለቅሳሉ፡፡

የማይቀጡት ልጀ ሲቆጡት ያለቅሳል፡፡

 

በሰሞኑ የዜና ዕወጃቸው ትግራይ ቲቪ አንዳንድ የትግራይና በጉልበት የተወሰዱ የበፊት የአማራ ከተሞችን ሰዎች እያነጋገረ ነበር – በድራማ መልክ መቀናበሩን መገመት ባይከብድም፡፡ ማፈርን የማያውቁት ወያኔዎች የለውጡን ኃይል ከትግራይ ሕዝብ ጋር ለማላተም በጀመሩት ዘመቻ እነሱ በህግ ስም ያደርጉት ከነበረው ወንጀልና የግፍ ተግባር ሊወዳደር ቀርቶ ከመለስተኛ ወቀሳ ውጪ በጥፋተኝነት ሊያስወነጅል የማይችልን ጥቃቅን ነገር ሁሉ እያጎሉ ማቅረባቸውን ተያይዘውታል፡፡ ወያኔዎች በላብራቶሪ ውስጥ ወንጀል ፈልስመው ለንጹሓን ምሥኪን ዜጎች እንዳላደሉ፣ በሙስና የተዘፈቀን ሰው ዕኩይ የዝርፊያ ተግባር በመያዣ ቀይ ካርድነት ይዘውና ሆዳሞችን በገንዘብ ገዝተው ምሥክር በማሰልጠን በንጹሓን ላይ እንዳላቆሙ፣ ዜጎችን በማንነታቸው ብቻ እየለዩ ዘር እንዳይተኩ በክትባትና በልዩ ልዩ ሰይጣናዊ ሥልቶች እንዳላመከኑና ብዙ ዜጎችን በበሽታ በክለውና በመርፌ ወግተው እንዳልጨረሱ፣ በጥላቻ ታውረው በተለይ አማሮችን ሊሰሙት በሚዘገንን ኢሞራላዊ ተግባር በቁማቸው ለመግደል 27 ዓመት ሙሉ እንዳልማሰኑ፣ አሁንም ቢሆን በመላዋ ትግራይ በሚገኙ ግልጽና ድብቅ እሥር ቤቶች አማሮችንና የመከላከያ አባላትን ጭምር በማንአለብኝነት ጥጋብ ተወጥረው በብዛት አጉረው እንደማያሰቃዩ፣ የሀገራችንን አንጡራ ሀብት በጠራራ ፀሐይ አጓጉዘው ትግራይን በተዘረፈ ሀብት እንዳላጥለቀለቁ፣ በጥቅሉ ሰማይና ምድር የማያውቋቸውን ወንጀሎችና ኃጢኣቶች በኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ላይ እንዳልፈጸሙ … የለውጡ ኃይል ግልጽ የሀገር ሀብት ዘራፊዎችን “ለምን አጋለጠ፣ ለምንስ በቲቪ መስኮት በሰንሰለት አስሮ አሳየብን፣ ለምን ጉዳችንና ገመናችን ይፋ ተደረገ?” ከሚል የቂሎች ፈሊጥ በመነሳት ቡራከረዩ እያሉ ነው፡፡ ይህ ያዙኝ ልቀቁኝ በአንድ በኩል ሲታይ የነሱ የነገ ዕድል ከዚህ የማይለይ በመሆኑ አስቀድሞ እየታያቸው ከዚያ የማይቀር መጥፎ የመጨረሻ ዕጣ ፋንታ ለማምለጥ የሚያሳዩት ከንቱ መፍጨርጨር ነው፡፡ ከላይ የታዘዘን ማንም አያስቀረውም፡፡ ሰውን የሚያሳድደው ደግሞ የገዛ ራሱ ኃጢኣት ነውና በዚህም አልፈርድባቸውም፡፡

ተጠርጣሪ ወንጀለኛ በሰንሰለት ታስሮ ወደ ማረፊያ ቤት መግባትም ሆነ በሚዲያ መታየት አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የየትኛውም ሀገራት መሪዎችና ታላላቅ ባለሥልጣኖች በፖሊስ ሲያዙ እንደዚሁ ነው የሚደረገው፡፡ ትግራይ ላይ ሲመጣ የተለዬ ሊሆን አይችልም፡፡ የብራዚሉ መሪ፣ የጣሊያን መሪዎች፣ የጃፓን መሪዎች፣ በቅርቡም የደቡብ ኮሪያዋ መሪ፣ ወዘተ. ሲያዙ በእጅ ብረት ተጠርንፈው ነው ወደ ዘብጥያ የወረዱትና የሚወርዱትም፡፡ ጄኔራል ክንፈ ዳኘው ምን ስለሆነ በወታደራዊ አጀብና በመድፍ ተኩስ ታጅቦ በክብር ወደ እስር ቤት እንደሚገባ የሚያውቁት ወያኔዎች ብቻ ናቸው፡፡ ከደነቆሩ አይቀር እንደዚህ ነው – ከልደት እስከሞት፡፡ “በቅሎ ‹አባትሽ ማን ነው› ቢሏት ‹እናቴ ፈረስ› ነች” አለች እንዲሉ ማጣፊያው ሲያጥራቸው ነገሩን ወደ ጎሣ ፖለቲካ አዙረው “ትግራይን  ለማንበርከክ ነው እንዲህ የሚደረገው” አሉና አስደመሙን፡፡ የክንፈ “ወንጀል” በምን ሂሣብ ነው የትግራይ ወንጀል ሊሆን የሚችለው? “አሁን ነው መሸሽ” እንግዲያውስ፡፡ ይህ ታሪክ የአያ ጅቦን ነገር ያስታውሰናል፡፡ ብቻውን ሲለቆምጭ ከርሞ የኋላ ኋላ አደጋ ሲመጣበት ልጆቹ እንዲረዱት ይጠይቃቸዋል፡፡ እነሱ በምን አበሳቸው፡፡ “ብቻህን እንደባለህ ብቻህን ቻለው” አሉታ! ትግራይ ትወቅበት፡፡ የሰው ዘር በሙሉ አንድ ነው፤ ወንጀል በዘርና በጎሣ አይተላለፍም፡፡ ካሰቡትና ካደረጉት ግን የማይሆን የለም፡፡ እናም “የኔ ልጆች ቢሰርቁም ሌቦች አይደሉም!” ብሎ የሚያምን ማኅበረሰብ ወይም ቡድን ካለ ችግር አለ ማለት ነውና ራስን በጊዜ መመርመር ይበጃል፡፡ እንጂ የሞላልኝ ዝርፊያ ለስንሻው፣ የሐጎስ ዝርፊያ ለፍትዊ፣ የደቻሳ ዝርፊያ ለፈይሣ … ምንም ማለት አይደለም፡፡ አስተሳሰባችንን ዘመናዊና ሰብኣዊ እናድርግ፡፡ ሌላው ቀርቶ የልጄ የአልፎአይቼው ይሄይስ ወንጀል የራሱ እንጂ እኔን በጭራሽ አይመለከትም፡፡ በምን ሂሣብ? እሱ ሌላ፤ እኔ ሌላ፡፡ ወደዚህች ምድር አመጣጣችንም ሆነ አካሄዳችን ለየቅል ነው፡፡ ለስደትና በስደት በመጣንባት ቅጽበታዊ ምድር የአንድ ሰው ልጆች – የአዳምና የሔዋን ዝርዮች – የአደምና የሃዋ የአብራክ ክፋዮች – በዘርና በጎሣ እየተቧደንን በከንቱ መባላት አልነበረብንም፡፡ ጥቅመኞች ግን ለዚህ ዳረጉን፡፡ እስኪ ቢቻለን ለማደግ እንሞክር – እነዚህን የመርገመት ፍሬዎች እንንቃባቸውና ወደየኅሊናችን ተመልሰን ከዕልቂት እንዳን፤ ሀገራችንንም ከውድመት እናድናት፡፡ ሩቅ እናስብ፡፡ ሰውነት ከሁሉም ይበልጣል፡፡ ዐይናችንን እንክፈት፤ ዘረኝነት አሳውሮን የልጆቻችንን ወንጀልና የዘረፋ ትዕይንት ላለማየት አንወስን፡፡

በእውነቱ ወያኔዎች በጣም ይገርሙኛል፡፡ መማር ሲያልፍ የማይነካቸው፣ ማደግና መለወጥ የተጠየፋቸው፣ እንደችፍርግ እዚያው ባሉበት መዝለቅን የመረጡ፣ እንደካሮት ወደታች እንጂ እንደሸንበቆ ወደላይ መመዘዝን የሚጠሉ፣ ማገናዘብ ዕርም የሆነባቸው፣ ሰው መሆን የሚናፍቃቸው እነዚህ ጉዶች “እንደተወለዱ ሞቱ” ቢባል የሚያንሳቸው እልም ያሉ ደንቆሮዎች ናቸው፡፡

ሌላው በሰሞኑ ዜና የገረመኝ ትግራይንና ሕዝቧን እንደወከሉ ተደርጎ የቀረቡት ዜጎች የተናገሩት ነገር ነው፡፡ በታሰሩት ሰዎች ላይ ዶኩመንታሪ ተሠርቷል መሰለኝ፡፡ እንደዚያ ሆኖ ከሆነ ስህተት ነው በርግጥ፡፡ ከወያኔ አንጻር ግን ይህን ነገር ለመቃወም ትግራይና ተጋሩ የመጀመሪያ ሊሆኑ አይችሉም፤ አይገባምም፡፡ ኧረ እጅግ ያሳፍራል፡፡ ተጋሩ የት ከርመው ነው ዛሬ ለተቃውሞ የተነሱት? አማራው እየተገደለ ወደ ገደል ሲጣል የት ነበሩ? አማራው ላይ ያ ሁሉ ሊሰሙት የሚዘገንን ግፍና ስቃይ ሲደርስ እነዚህ “ለሰው መብት ተቆርቋሪ” ትግሬዎች የት ነበሩ? ወይንስ የሰው ግርድና አመሳሶ አለው? እንደዚያ ያለ ነገር የማውቀው በአይሁዶችና በኢ-አይሁዶች ነው፡፡ ዝርዝሩ ብዙ ስለሆነ ወደዚያ አሁን አልገባበትም፡፡  ሕወሓት ለ27 ዓመታት ያን ሁሉ ሰማይና ምድር የማይችሉት ዘረፋና ቅጣ ያጣ ግፍና በደል በኢትዮጵያውያን ላይ ሲፈጽም እነዚህ ትናንትና ትከሻቸውን እየሰበቁና “እናሳያቸዋለን! ጦርነትን እንኳን መዋጋት ጠፍጥፈን እንሠራዋለን” በሚል የቆዬ ዕብሪት  ለጂኒራር ክንፈ የተከራከሩት ሰዎች እስከዛሬ የት ተደብቀው ነበር? ድምፂ ወያኔና ትግራይ ቲቪስ በአማሮች ላይ የደረሰውን ስቃይና በደል በሌሎች ሚዲያዎች እየሰሙ ለምን ጆሮ ዳባ ብለው አለፉት? የአማራ ነፍስ ከዶሮ ነፍስ ታንስ ይሆን? ወያኔ የሚፈጽመውን ሰቆቃ እንደ ጽድቅ፣ በወንጀለኛ ወያኔዎች ላይ የምትደርስን ትንሽዬ የሚዲያ ሽንቆጣ ግን እንደታላቅ ድፍረትና ወንጀል መቁጠር ከምን የመነጨ ይሆን? “እኛ አዛዥ ናዛዥ ስለሆንን ራሳችን የፈለግነውን ብናደርግም ማንም ሊናገረን ቀርቶ ዝምባችንን እሽ ሊለው አይገባም” ለማለት ይሆን? አዎ፣ “እሽ አትበሉን የሹም ዶሮዎች ነን” ማለት አሁን ነው፡፡ አዎ፣ “የማይቀጡት ልጅ ሲቆጡት ያለቅሳል ማለትም አሁን ነው፡፡ ድንቁርና ማለት እንዲህ በተሟላች መልኳ ስትቀርብ ነው፡፡ እጅግ በጣም የሚገርም የታሪክ አጋጣሚ፡፡ …

ይሄ “ሌላውም ይታሰር” የሚሉት ነገር ደግሞ አልገባኝም፡፡ አንደኛ ሌላውም እየታሰረ ነው፤ ትግሬ ተለይቶ የታሰረበት ሁኔታ የለም፤ ወደፊትም የሚኖር አይመስለኝም፡፡ ሁለተኛ ከሚታሰሩት አብዛኛዎቹ ትግሬ ቢሆኑ ከቅርብ ጊዜው ሸፋፋ ታሪካችን አንጻር አያስገርምም፡፡ ወያኔዎች ከጥቂት አንጎለቢስ ሆዳሞች ጋር ሆነው በበሉት ሌላው አማራና ኦሮሞ ምን ቤት ነኝ ብሎ ነው እስራታቸውን የሚጋራው? ሌላው ቆሞ ለተመለከተ፣ ከቶውንም ላልበላበት ነገር መናጆ መሆን አለበት እንዴ? 27 ዓመት ሙሉ ትግሬ ለትግሬ እየተጠራራች ከነቤተሰቧ ቅርጥፍ አድርጋ  በበላች አሁን ደርሶ ለመከራው ሲሆን ሌላውም ጎሣ ይያዝልኝ ብሎ መደንፋት ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው? ሕዝብን በዘረኝነት ስሜት አነሳስቶ ሁከት ለመፍጠርና ዘረፋንና ግፍና በደልን እንደቀድሞው ለመቀጠል ታስቦ ከሆነ ከአሁን በኋላ ይህ ዓይነቱ ሃሳብ ከምኞት የማይዘል ቅዠት ነው፡፡

አንድ ነገር ትዝ አለኝ፡፡ ትናንት ማታ የጂኒራር አበበ ተ/ሃይማኖትን የዋልታ ቲቪ ቃለ ምልልስ በከፊል ተከታተልኩ፡፡ በነገራችን ላይ ወያኔ የቁም ስቅላቸውን ካበላቸው ነገሮች መካከል ቃላትና የማዕረግ ስሞችም በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ ከነዚህም መካከል “ኮሎኔል፣ ብ/ሜ/ሌ/ጄኔራል፣ ዶክተር፣ ዴሞክራሲ፣ ነፃነት፣ሰላም፣ ፌዴራል መንግሥት፣ ህገ-መንግሥት” የሚሉት ዋና ዋናዎቹ ናቸው – እንዴ፣ የአራተኛ ክፍል የዝቅተኛ ውጤት ደካማ ምሩቅ ሙሉ ጄኔራልና በድራቦሹም ፕሮፌሰር የሚኮንባት ብቸኛ ሀገር እኮ ናት ኢትዮጵያ! ስንገርም፡፡ ወያኔ እንዴት እንዳዋረደን መቼስ … ፡፡  እናላችሁ ይህ ሰውዬ፣ ይህ ጂኒራር ተብዬ ለማያውቁት ሲታጠንላችሁ “የአዲሱ መንግሥት የፓርላማ አባላት የዶ/ር ዐቢይ ‹ራበር ስታምፕ› ናቸው” ብሎ ዕርፍ አይል መሰላችሁ? እንደውነቱ ብዙ ነገር ትክክል ብሏል – ለሰይጣንም ቢሆን የሚገባውን አለመከልከል ደግ ነውና፡፡ ግን በዳዴ እየሄደ ያለና እርሱና ወንድም እህቶቹ ለ40 ምናምን ዓመታት ያግማሙትን ሀገራዊ ጉዳይ በግማሽ ዓመት ምን ያድርጉት ሊል እንደፈለገ አልገባኝም፡፡ እርሱ የባዶ ስድስት ኃላፊ እያለ ያሰቃይና ይገድል እንደነበረ የሚሰማለትን ከምን ጊዜው ረስቶ እንዲህ የዴሞክራሲ ጠበቃ ሊሆን እንደቻለም አልገባኝም፡፡ የሆኖ ሆኖ አቤ ጆቤ ወንድሞቹ አደጋ ውስጥ የገቡ በመሰለው ቁጥር በሚዲያ ብቅ እያለ ዋስ ጠበቃና ተከራካሪ ሊሆንላቸው መፈለጉን አልቃወምም፡፡ ግን ግን ከሚጠቅሰው የወንድሞቹ ሀገራዊ የዕድገትና ብልፅግና በረከቶች በተጓዳኝ እነዚሁ የብዔልዘቡል አሽከሮች ወንድሞቹ በሕዝቡና በሀገሪቱ ላይ ያደረሱትን በመቶዎች ዓመታት ሊጠገን የማይችል ቁሣዊና መንፈሳዊ ኪሣራ በተመለከተ ትንሽ ቢተነፍስ በወደድኩለት – በደፈናው እንጂ ጠቀስ የሚያደርጋት ያቺ ያቺን በቅጡ አይነካካትም፡፡ “ክርስቶስ ለሥጋው አደላ” እንደሚባል ይህ ሰውዬ ለጨፍጫፊ ወንድሞቹ ያለውን አዘኔታ ከመግለጽ ባለፈ ለተጎዳው ሕዝብ ማሰቡን ያስረዳበት የሃሳብ ይዘት በጣም ደካማ ነው፡፡ ይልቁንም የወንድሞቹን ገመና ለመሸፈን የሄደበት ርቀት በዝቶ ታይቶኛል – እንደኔ፡፡ ነገር ደግሞ እንደተመልካቹ ነው፡፡

1 Comment

Comments are closed.

Previous Story

የለውጡ ተግዳሮቶች በኔ ዕይታ – ይነጋል በላቸው (ከአዲስ አበባ)

92752
Next Story

አጭጭር ዜናዎች

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop