Sport: የቤካም እና የካራገር “ጫማ ሰቀላ” የእንግሊዛውያኑ ብቻ ሳይሆን የኛም ወሬ ሆኗል

ከአሰግድ ተስፋዬ
የተወዳጁ እግር ኳስ ስፖርት « ፈጣሪ » እንደሆነች የሚነገርላት ነገር ግን በዓለም አቀፍ ውድድሮች ብዙም ውጤታማ መሆን ያልቻለው እንግሊዝ በተለያዩ ወቅቶች ምርጥ እግር ኳሰኞችን አፍርታለች።
ከነዚህ ምርጥ እግር ኳስ ተጫዋች ኮከቦች መካከል ላለፉት ሃያ ዓመታት በስፖርቱ በስኬታማነት ያሳለፈው ዴቪድ ቤካምና ከልጅነት እስከ እውቀቱ የመርሲሳይዱን ክለብ መለያ ብቻ የለበሰው ጂሚ ካራገርን ፣ ዋይኔ ሩኒን ፣ ማይክል ኦዌንና ሌሎች ተጫዋቾችን መጥቀስ ይቻላል።
ከእነዚህ ተጫዋቾች መካከል በስፖርቱ ባስመዘገበው ስኬት ግንባር ቀደም የሆነው ዴቪድ ቤካምና የሊቨርፑሉ ጂሚ ካራገር « ጫማ መስቀላቸውን» ገልጸዋል። የማንችስተር ዩናይትዱ የተከላካይ መስመር ተሰላፊው ሪዮ ፈርዲናንድ ደግሞ ራሱን ከብሔራዊ ቡድኑ ማግለሉን ይፋ አድርጓል።
እነዚህ ጉዳዮች የመገናኛ ብዙኃን ሰሞነኛ መሪ ዜና ቢሆኑም ልዩ ትኩረት ያገኘው የዴቪድ ቤካም ጫማ መስቀል ጉዳይ ነው።
አንጋፋውና ውጤታማው የማንችስተር ዩናይትድ እግር ኳስ ክለብ አሰልጣኝ የነበሩት ሰር አሌክስ ፈርጉሰን ካሳደጓቸውና « ፈርጊ ቤቢስ » እየተባሉ ይታወቁ ከነበሩት መካከል አንዱ የሆነው ዴቪድ ቤካም ለእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን በ115 ጨዋታዎች ላይ ተሰልፎ ተጫውቷል። ለአሳዳጊው ማንችስተር ዩናይትድ እግር ኳስ ክለብ ደግሞ 394 ጨዋታዎችን አድርጓል።
የ38 ዓመቱ ቤካም « ቀያይ ሰይጣኖች » በመባል ከሚታወቀው ማንችስተር ዩናይትድ ክለብ ጋር ስድስት የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችንና የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎችን አንስቷል። በምስራቃዊ ለንደን የተወለደው የመሐል ሜዳ ተጫዋቹ ቤካም ከአሳዳጊው ክለብ ከተለያየ በኋላ ለስፔኑ ኃያል ሪያል ማድሪድ ፣ በአሜሪካ ሜጀር ሶከር ሊግ ተሳታፊ ለሆነው ሎስ አንጀለስ ጋላክሲ፣ለጣሊያኑ ኤሲ ሚላን ፣ በመጨረሻ ደግሞ ለፈረንሳዩ ሻምፒዮና ፓሪስ ሴንት ጄርሜን እግር ኳስ ክለቦች ተጫውቷል። ተጫዋቹ በጨዋታ ዘመኑ ከዩናይትድ ጋር ያነሳቸውን ዋንጫዎች ጨምሮ በጠቅላላው 19 ዋንጫዎችን አንስቷል።
ዴቪድ ቤካም በአራት የተለያዩ ሊጎች ከተለያዩ ክለቦች ጋር ዋንጫ በማንሳት ብቸኛው እንግሊዛዊ ተጫዋችም ነው።
ዴቪድ ቤካም ቀያይ ሰይጣኖቹን በተለ ማማጅነት የተቀላቀለው በአውሮፓውያኑ 1991 ሲሆን በቀጣዩ ዓመት ለዋናው ቡድን ተሰልፎ የመጫወት እድል አግኝቷል። ከአንድ ዓመት በኋላ የመጀመሪያውን የፕሮፌሽናል ተጫዋችነት ኮንትራት ፈርሟል። በኦልድ ትራፎርድ በነበረው ቆይታ ያሳየው ምርጥ ብቃቱ ዓለም አቀፍ እውቅና አስገኝቶለታል። ይህንን እውቅናውን ተከትሎም ታላላቅ ተጫዋቾችን በመሰብሰብ የሚታወቀውን የስፔኑን ሪያል ማድሪድን ተቀላቅሎ በአውሮፓውያኑ 2003 የላ ሊጋውን ዋንጫ አንስቷል።
ከስፔኑ ኃያል ወደ አሜሪካው ሎስ አንጀለስ ጋላክሲ ተዛውሮ ተጫውቷል። በዚህ ክለብ በነበረው ቆይታ በውሰት ለጣሊያኑ ኤሲ ሚላን ተሰልፎ የመጫወት እድል አግኝቷል። ወደክለቡ ኤልኤ ጋላክሲ ተመልሶ ዋንጫ ካነሳ በኋላ ለፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንት ጄርሜን ፈርሞ ተጫውቷል። እንዲሁም ዋንጫ ካነሳ በኋላ ጫማ መስቀሉን ይፋ አድርጓል።
ቤካም በሦስት ተከታታይ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች ላይ ግብ በማስቆጠር ብቸኛው እንግሊዛዊ ተጫዋች ከመሆኑም በላይ በአውሮፓ ዋንጫ ለግብ የሚሆኑ በርካታ ኳሶችን በማቀበል በታሪክ ሁለተኛው ተጫዋች ነው።
«ለልጅነት ክለቤ ማንችስተር ዩናይትድ ተጫውቼ ዋንጫዎችን አንስቻለሁ። ለአገሬም ከአንድ መቶ በላይ ጨዋታዎችን ከማድረጌም በላይ በአምበልነት መርቻለሁ ። ለታላላቅ ክለቦች ተጫውቻለሁ። ይህ ለእኔ ከስኬትም በላይ ነው» ብሏል ስንብቱን ይፋ ባደረገበት መግለጫው።
«በእግር ኳስ ተጫዋችነት ሕይወቴ ካከና ወንኳቸው ተግባራት ከምኮራባቸው ነገሮች አንዱ አገሬን በአምበልነት መምራት መቻሌ ነው። የሦስቱን አናብስት መለያ በመልበሴ ከታላላቆቹ ተጫዋቾች ተርታ ከመመደቤም በተጨማሪ አገራቸውን ለሚወዱ ደጋፊዎችም የኩራት ምንጭ ሆኛለሁ። በዚህም እድለኛ ነኝ » ብሏል።
ሰዎች ሜዳ ሲገባ ያለውን ሁሉ እንደሚሰጥ ጠንካራ እግር ኳሰኛ እንዲያየኝ እፈልጋለሁ ያለው ቤካም በተጫዋችንት ሕይወቱ የረዱትን ሁሉ አመስግኗል።
የእንግሊዝ ዋና ከተማ የ2012 ኦሊምፒክ የአዘጋጅነት እድል እንድታገኝና እድሉን ካገኘች በኋላም በዝግጅቱ ወቅት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገውን የቤካምን ከእግር ኳስ ዓለም መገለል አስመልክቶ የአገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩንን ጨምሮ በርካታ ሰዎች አድናቆታቸውን ለተጫዋቹ በመግለጽ ላይ ይገኛሉ።
ሰሞኑን ራሳቸውን ከእግር ኳስ ተጫዋችነት ማግለላቸውን ካስታወቁት መካከል የሊቨርፑሉ የተከላካይ መስመር ተጫዋች ጂሚ ካራገር ይገኝበታል። የ35 ዓመቱ ካራገር ክለቡ ሊቨርፑል እሁድ ከኩዊንስ ፓርክ ሬንጀርስ ጋር ከሚያደርገው ጨዋታ ላይ ከተሳተፈ በኋላ ነው ሙሉ ለሙሉ ከጨዋታ ዓለም የሚገለለው።
ካራገር በእግር ኳስ ተጫዋችነት በሊቨርፑል ባሳለፋቸው 16 ዓመታት ሁለት የኤፍኤ ፣ ሦስት የሊግ ፣ሁለት የኮሙኒቲ ሽልድና አንድ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎችን ቢያነሳም አንድም ጊዜ የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ ሳያነሳ ከኳስ ተጫዋችነት መገለሉ እንደሚቆጨው ተናግሯል።
« የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ
አላገኘሁም።ይህ ከፍተኛ ቁጭት ውስጥ እንድገባ አድርጎኛል » ብሏል።
ሊቨርፑል 732 ጨዋታዎችን ያደረገው ካራገር ለክለቡ በርካታ ጨዋታዎችን በማድረግ ሁለተኛው ተጫዋች መሆን ችሏል።ለሊቨርፑል በርካታ ጨዋታዎችን በማድረግ ቀዳሚ የሆነው ያን ካላጋን ሲሆን ተጫዋቹ 857 ጊዜ የመርሲሳይዱን ክለብ መለያ አድርጎ ተጫውቷል።
በቴሌቪዥን የእግር ኳስ ተንታኝ ሆኖ ለመስራት ዝግጅት በማድረግ ላይ የሚገኘው ካራገር « ጫማውን የመስቀል » ውሳኔ ላይ የደረሰው ከ12 ወራት በፊት እንደነበረም ገልጿል።
እንግሊዛዊው የማንችስተር ዩናይትድ እግር ኳስ ክለብ የተከላካይ መስመር ተሰላፊ ሪዮ ፈርዲናንድ ራሱን ከብሔራዊ ቡድን ማግለሉን ይፋ አድርጓል።
ለእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን 81 ጊዜ ተሰልፎ የተጫወተው የ38 ዓመቱ ፈርዲናንድ ከብሔራዊ ቡድኑ ራሱን ለማግለሉ በምክንያትነት የጠቀሰው ትኩረቱን ለክለቡ ለማድረግ በመፈለጉ መሆኑን ተናግሯል። እነዚህ ተጫዋቾች ጉዳይ የሰሞኑ የዓለም የመገናኛ ብዙኃን የፊት ገጽ ዜናና መነጋገሪያ ሆነውሰንብተዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከማይናማር ለተፈናቀሉ ሙስሊሞች እርዳታ ሲያጓጉዝ የነበረ መኪና ተገልብጦ ሰዎች ሞቱ
Share