የድምጻችን ይሰማ ወቅታዊ ጽሑፍ፡ ሺህ ሆነን እንደ አንድ፤ አንድ ሆነን እንደ ሺህ – የፅኑዎች ትግል

ከድምጻችን ይሰማ የተላለፈ ወቅታዊ ጽሁፍ
ቅዳሜ ሰኔ 28/2006

የኢህአዴግ መንግስት በኢትዮጵያ ሙስሊሞች ላይ የከፈተው ሁለንተናዊ ጥቃት እና ጭቆና በብዙ ሚሊዮናት ዜጎች ላይ የተከፈተ ጥቃት ቢሆንም እኛ … ብዙ ሚሊዮናት… ዜጎች ግን ብዝሃነታችን፣ የቋንቋችን መለያየት እና የብሔራችን አንድ አለመሆን እክል ሳይፈጥርብን በእምነት ገመድ ተሳስረን የተከፈተብንን ጥቃት ስንመክት እነሆ ሦስተኛ ረመዳናችንን ያዝን።

በእነዚህ አመታት ውስጥ ‹‹ወርቅ በእሳት ይፈተናል!›› እንዲሉ እኛ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችም ከባድ የእንግልት እና የመከራ ጊዜያትን አሳልፈናል። መንግስት አንድ መንግስት በዜጎቹ ላይ ሊያደርሰው የሚችለውን ሰቆቃ አንድም ሳያስቀር አሟጦ በእኛ ላይ አድርሶብናል። የሐምሌ 6/2004 የሌሊት ጭፍጨፋ፣ የአርሲ አሳሳው ግድያ፣ የገርባ፣ የደጋንና የሀረሩ ሕይወት ቀጠፋ፣ የዒድ ሶላቱ ህፃንን ከአዛውንት፣ ወንድን ከሴት ያልለየ ድብደባና ግድያ፣ በማእከላዊ በወኪሎቻችን እና በበርካታ ወንድም እና እህቶቻችን ላይ የተፈፀሙ ዘግናኝ እና ኢሰብአዊ አካላዊ ጥቃቶች፣ እንዲሁም ተቆጥረው የማይዘለቁ የእስር፣ የድብደባ እና አካል የማጉደል ጥቃቶች ወሰን ያለፉና መንግስታዊ ጭካኔ የታየባቸው የሰቆቃ ዳራዎች ነበሩ።

የእነዚህ ሁሉ እርምጃዎች የመጨረሻ ግብ ደግሞ አንድነታችንን መበተን፣ ተስፋችንን ማጨለም እና ወደ አፄው ዘመን የተሸማቀቀ ማንነታችን መመለስ ነበር። ዳሩ ግን በፍየል ዘመን በግ ሊያደርጉን ለሚሹ አካላት እጅ ባለመስጠት እና አንድነታችንን በማጠናከር፣ ‹‹ብልጦች አይደለንም! ብልጣ ብልጦች ግን አያታልሉንም!›› እያልን የተቃጡብንን ጥቃቶች ስንመክት ከርመናል። ወደ ፊትም በአላህ (ሱ.ወ) እርዳታ በዚሁ የአንድነት መንፈስ የሚደርሱብንን ጥቃቶች በሙሉ መመከታችንን እንቀጥላለን!
ሺህ ሆነን እንደ አንድ አካል እንድንታገል መሠረቱን የጣሉልን ደግሞ ‹‹አንድ ሆነው እንደ ሺህ›› መታገል የቻሉት ብርቅዬ ወኪሎቻችን ናቸው። አዎን! ወኪሎቻችን አንድ ሆነው እንደ ሺህ ታግለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ላይ የተሰነዘረውን ዱላ ብቻቸውን በማእከላዊ ተጋፍጠውታል፡፡ አቋማቸውን ለማስለወጥ፣ ቅስማቸውን ለመስበር እና ተስፋቸውን ለማጨለም ታቅዶ የደረሰባቸው ኢሰብአዊ ጥቃት ሳይበግራቸው ከብረት ጀርባ ሆነው አቋማቸውን ለህዝብ ይፋ አድርገዋል፡፡ ስቃዩን እየተሰቃዩለት ላለው የኢትዮጵያ ሙስሊምም የእንኳን አደረሰህ መልእክት አድርሰዋል፡፡ ፅኑ ሆነው ፅናትን አስተምረውናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጠንካራ ዲፕሎማሲና ዉስጣዊ ሰላም እጅግ አስፈላጊነት

ፅናት ሰላማዊ ትግል ግቡን ይመታ ዘንድ ትልቁ መስፈርት ነው። በዓለም ዙሪያ ግባቸውን መምታት የቻሉ ሰላማዊ ትግሎች አመታትን የወሰዱ፣ የታጋዮችን ፅናት የፈተኑ እና አሜኬላቸው የበዛ ነበሩ። የእኛ የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ትግልም ከዚህ የተለየ ሊሆን እንደማይችል መገመት ይቻላል። የትግሉን የመጨረሻ ፍሬ ለማየት ምናልባትም የትውልድ ቅብብሎሽን የሚፈልግ ሊሆን ይችላል፡፡ እኛ ግን እንደ አላህ (ሱ.ወ) ፍቃድ በቅርቡ ድላችንን እንደምናየው ተስፋ እናደርጋለን።

ሁላችንም ራሳችንን እንጠይቅ… ‹‹እንደ ታጋይ በዚህ ትግል ውስጥ ማበርከት ከምንችለው አስተዋፅኦ ምን ያህሉን አበርክተናል? ትግሉን እስከ ድል ደጃፎች ድረስ በፅናት ለመቀጠል ዝግጁነታችን ምን ይመስላል? በትግሉ ዙርያ ምን ያህል የመረጃ ልውውጦችን እናደርጋለን?››

እኒህን እና መሰል ጥያቄዎችን ራሳችንን እየጠየቅን እኛም እንደወኪሎቻችን ሁሉ ሺህ ሆነን እንደ አንድ ከመታገል በዘለለ አንድ ሆነን እንደ ሺህ የምንታገልበትን እና የድሉን ጊዜ የምናቃርብበትን መንገድ ማየት ያስፈልገናል።
ትግላችን በአላህ ፈቃድ እስከ ድል ደጃፎች ድረስ ይቀጥላል!
ድምጻችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

2 Comments

  1. እናንተ የትውልዱ ኮከቦች እንደ ቃላችሁ ከሙሉዑ ኢትዮጵያዊ ጨዋነትና ከተቋምነት አብነታችሁ ጋር መሆነችሁ ጭብጥ ነው። ታኮራላችሁ! ጽናቶች!

    እግዚአብሄር ይስጥልኝ!

  2. I appreciate your endurance. Hope we orthodox will join you soon. What yot have done is inspirational

Comments are closed.

Share