በሙስና ተጠርጥረው የታሰሩት ‘‘አያያዛችን ህገ-መንግስታዊ ሥርዓቱን የተከተለ አይደለም’’ አሉ (የፍርድ ቤት ውሎ)

‘‘አያያዛችን ህገ-መንግስታዊ ሥርዓቱን የተከተለ አይደለም’’
ተጠርጣሪዎች
*‘‘እስካሁን ተከሳሽ የሚባል የለም፤ እነዚህ ሰዎች ተጠርጣሪዎች ናቸው’’
ፍርድ ቤቱ
*‘‘በሚዲያ የሚተላለፈው ሪፖርት በቤተሰቦቻችን ላይ ጫና እየፈጠረ ነው’’
ተጠርጣሪዎች
በአሸናፊ ደምሴ
በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የፌዴራሉ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን መርማሪዎች ማጣራት እያካሄዱባቸው የሚገኙት 24 ግለሰቦች የዋስትና መብታቸውን በተመለከተ በትናንትናው ዕለት የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው ውሳኔ ተሰጣቸው።
በትናንትናው ዕለት የኮሚሽኑ መርማሪ በሦስት ክሶች ከፋፍሎ ክስ የመሰረተባቸው 24 ተጠርጣሪዎች በፍርድ ቤቱ የተገኙ ሲሆን፤ ከትናንት በስቲያ በነበረው የቃል ክርክር ወቅት ተነስቶ የነበረውን የዋስትና ጥያቄ ምላሽ ተሰጥቶበታል። በዚህም የፌዴራል ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ሕገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በጠበቀ መልኩ ከምክር ቤት አባልነታቸው መታገዳቸውን የሚያስረዳ ደብዳቤ ሊቀርብ ይገባል ያለው ፍርድ ቤቱ፤ ይህንንም ለማጣራት ለግንቦት 9 ቀን 2005 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል። በመሆኑም በአንደኛ ክስና በሁለተኛ ክስ ስር የተዘረዘሩት ተጠርጣሪዎች በሙሉ ለግንቦት 19 ቀን 2005 ዓ.ም የምርመራው ፈቃድ ፀንቶባቸው የተቀጠሩ ሲሆን፤ አቶ መላኩ ፈንታን ጨምሮ በናዝሬት ጉምሩክ ባልደረቦች ስር የተጠረጠሩት ግለሰቦች ለግንቦት 9 ተቀጥረዋል።
በፌዴራሉ የሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን መርማሪዎች በናዝሬት ጉምሩክ ባልደረቦች ላይ የተለያዩ የኮንትሮባንድ ዕቃዎችን ወደሀገር ውስጥ እንዲገቡ በማድረግ ያልተገባ ሀብት አግኝተዋል ሲል ክሱን የዘረዘረ ሲሆን፤ ከስድስቱ ተጠርጣሪ መካከል ሁለቱ ብቻ ጠበቆቻቸውን ማግኘታቸውን በመጥቀስ ቀሪዎቹ ከጠበቆች ጋር እንዳልተገናኙ በመግለፅ ለፍርድ ቤቱ ያስረዱ በመሆናቸው፤ ፍርድ ቤቱም ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙና ሀሳባቸውን አደራጅተው እንዲቀርቡ በማለት ለግንቦት 9 ቀን 2005 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ፍርድ ቤቱ ከትላንት በስቲያ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ተጠርጣሪዎቹ ለምን ከጠበቆች ጋር አልተገናኙም ለሚለው የፍርድ ቤቱ ጥያቄ በተሰጠው ምላሽ፤ በማረሚያ ቤት የሚገኙ ሰዎች ረቡዕና አርብ ብቻ በጠበቆቻቸው ጋር የሚገናኙበት አሰራር መኖሩ ተብራርቷል። በዚህም ላይ ፍርድ ቤቱ ተጨማሪ ማብራሪያ እንዲሰጠው በመጠየቅ ለግንቦት 9 ቀን 2005 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ፍርድ ቤት ከቀረቡት ተጠርጣሪዎች መካከል አብዛኞቹ በጠበቆቻቸው አማካኝነት ጉዳያቸውን ያስረዱ ሲሆን፤ ስለተከሰስንበት ወንጀል በቅጡ የምናውቀው ነገር የለም። አያያዛችን ህገ-መንግስታዊ ሥርዓቱን የተከተለ አይደለም። ሰሞኑን በሚዲያ እየተነገረ ያለው ነገር ትክክል ያልሆነና የቤተሰቦቻችንን አንገት ያስደፋ ነው ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል።
ፍርድ ቤቱ በበኩሉ ‘‘በምንም መልኩ ቢሆን እስካሁን ተከሳሽ የሚባል ነገር የለም፤ እነዚህ ሰዎች ተጠርጣሪዎች ናቸው’’ ሲል ዐቃቤ ሕግ ክስ ባልመሰረተበት ሁኔታ ተጠርጣሪዎቹ በተሳሳተ ስም መጠራት የለባቸውም ብሏል።
በኮሚሽኑ መርማሪዎች ሁለተኛ ክስ ስር የፌዴራሉ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስን ጨምሮ ባለቤታቸው ኮሎኔል ሃይማኖት ተስፋዬ እና እህታቸው ወ/ሮ ንግስት ተስፋዬን ከነልጅዋ እንዲሁም ሌሎች በድምሩ 12 የሚደርሱ ተጠርጣሪዎች የቀረቡ ሲሆን፤ የተጠረጠሩበት ወንጀልም ወደሀገር ውስጥ እንዳይገባ የተከለከለን ሲሚንቶ እንዲገባ በማድረግ፣ በኮንትሮባንድ የተሰማሩ ሰዎችን በማገዝ፣ ከተጠርጣሪዎችም መካከል የሁለቱን ክስ የሚደግፉ ሠነዶችን ማሸሽ በሚሉ ወንጀሎች እጠይቃቸዋለሁ ይላል።
አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስ በጠበቃቸው አማካኝነት እንዳስረዱት ‘‘ቤተሰቤ ተበትኗል፤ ልጄ ለትምህርት የሚገለገልበት ላፕቶፕ ተወስዶበታል። ባለቤቴንም ህጉን ባልተከተለ መንገድ ልብስ አስወልቀው ጭምር ፈትሸዋታል፤ ልታሸሽ ነበር ተብሎ የተያዘውም ካርታ ፎቶ ኮፒው መሆኑንና ዋናው በፌዴራሉ ሥነ-ምግባና ፀረ-ሙስና መርማሪዎች እጅ እንደሚገኝም ጭምር አስረድተዋል።
በሌላም በኩል ተጠርጣሪዎቹም በማረሚያ ቤት የተቀበላቸው አያያዝ መልካም አለመሆኑን በመጥቀስ ለፍርድ ቤቱ ያስረዱ ሲሆን፤ ፍርድ ቤቱም ተጠርጣሪዎቹ በማረሚያ ቤት ቆይታቸው ሕገ-መንግሥታዊ መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ሲል ትዕዛዝ ሰጥቷል።
የፌዴራሉ የሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና መርማሪ ቡድን በሙስና ተጠርጥረው ጉዳያቸውን ለፍርድ ለማቅረብ በተሰናዳባቸው 24 ግለሰቦች ላይ ሦስት ክሶችን የመሰረተ ሲሆን፤ በ1ኛ ክስ ስር በእነ አቶ መላኩ ፈንታ መዝገብ ውስጥ የሚገኙት 7 ተጠርጣሪዎች አቶ እሸቱ ወ/ሰማያት፣ አቶ መርክነህ አለማየሁ፣ አቶ አስመላሽ ወ/ማርያም፣ አቶ ከተማ ከበደ፣ አቶ ስማቸው ከበደ እና ዶክተር ፍቅሩ ማሩ ይገኙበታል። እነዚህ ቀረጥና ታክስን በማጭበርበርና አራጣ በማበደር የተከሰሱ ግለሰቦች እንዲቋረጥ በማድረግ ወንጀል ተከሰዋል።
በሁለተኛው የክስ ዝርዝር ውስጥ አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስን ጨምሮ አቶ በላቸው በየነ፣ አቶ ጥሩነህ በርታ፣ አቶ ተስፋዬ አበበ፣ አቶ ነጋ ገ/እግዚአብሔር፣ አቶ ምህረተአብ ካሳ፣ አቶ ሙሌ ጋሻው፣ አቶ አሞኘ ታገለ፣ ኮሎኔል ሃይማኖት ተስፋዬ፣ አቶ ሀብቶም ገብረመድህን እና ወ/ሮ ንግስቲ ተስፋዬን ጨምሮ በመጨረሻ የተቀላቀሉትን 12ኛ ተከሳሽ አቶ ተወልደ ብስራትን ያጠቃልላል። በዚህም ክስ ስር ተጠርጣሪዎቹ ፈፀሙት የተባለው ወንጀል ወደሀገር ውስጥ እንዳይገባ የተከለከለን ሲሚንቶ እንዲገባ በማድረግ፣ በኮንትሮባንድ የተሰማሩ ግለሰቦችን በማገዝ፣ ከተጠርጣሪዎች መካከል የሁለቱን ክስ የሚደግፍ ሰነድ ለማሸሽ ጭምር የሚል ይገኝበታል።
በሦስተኛ ክስነት የተጠቀሰው የናዝሬት ጉምሩክ ባለስልጣናትን የሚመለከት ሲሆን፤ በዚህም ስር አቶ መሃመድ ኢሳን ጨምሮ 6 ተጠርጣሪዎች የተዘረዘሩ ሲሆን፤ እነሱም አቶ ሰመረ ንጉሴ፣ አቶ ዘሪሁን ዘውዴ፣ ወ/ሮ ማርሸት ተስፋዬ፣ አቶ ሙሉቀን ተስፋዬ እና አቶ ዳኜ ስንሻው ይገኙበታል። የተጠረጠሩበት የወንጀል ክስም በኮንትሮባንድ የተለያዩ ዕቃዎች ወደሀገር ውስጥ እንዲገቡ በማድረግና ያልተገባ ሀብትን ማካበት የሚሉት ይጠቀሳሉ።
በትናንትናው ዕለት በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ ወንጀል ችሎት ጉዳዩን ለመከታተል ከተገኘው በመቶዎች የሚቆጠር ሕዝብ መካከል ወደ ችሎት መግባት የቻለው ጥቂቱ ሲሆን፤ በአዳራሹ ጠባብነት ምክንያት በተለይም ጋዜጠኞች ቦታ ሊያገኙ አለመቻላቸው ትኩረትን ስቦ ነበር። አንዳንድ የተጠርጣሪዎቹ ቤተሰቦችም ችሎቱ በሰፊ አዳራሽ ቢካሄድ የተሻለ ይሆን እንደነበር አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።n (ምንጭ ሰንደቅ ጋዜጣ የዛሬ ሜይ 15 2013 ዕትም)
ተጨማሪ ያንብቡ:  የተባሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሀፊው አንቶኒዮ ጉተሬዝ በኢትዮጵያ ጉዳይ የሚደነግጡት መቼ መቼ ነው

2 Comments

  1. ሕገ-መንግስቱ ምን ይላል? የኢህአዴግ አባላት ወደእስር ቤት ከመውረዳቸው ከቀናት በፊት ቡና አፍሉላቸው፤ ፓርቲ ደግሱ ይላል?አንባሰሻ ጋግራችሁ ንፍሮ ቀቅላችሁ ድንኳን ተክላችሁየዕርዳታ ስንዴ ንፊ ይላል? ማንም ሰው ከሕግ በታች እነጂ ከሕግ በላይ አይሆንም ሲል ፓርላማ ቁጭ ብለው የሚገለፍጡትን፡የሚያንቀላፉትን፤ የሚያጨበጭቡትን፤አይመለከትም ይላል? በዚያች ዽሃ ኢትኦጵያ ላይ የኢህአዴግ/ወያኔና አድርባዮቹ..ዲያስፖራ.ቱልቱላዎች የተለየ ዜግነታቸው ከየት መጣ? ?ከእስክንድር ነጋ.ከአንዱዓለም አራጌና ከሌሎችም በእስር ላይ ከሚገኙ ዜጎች ነፍስ ከቤተሰቦቻቸውና ቤተዘመድ ጓደኞቻቸው ድምፅ ሳይሰማ የእነኝህ መቀሳፈትና መቀላመድ ለማን?ለምን? አማራ ቤት አተላ ሲልስ ያደገ ሁሉ በአማራነት ሊነግድ አይገገባውም! ብኤድን የወያኔ ጠርብ ኮብል እስቶን ነው በለው!! አሁንም በውጭ ሀገር በኤምባሲ በኢህአዴግ ድጋፍ ኮሚቴ የተዋቀሩ ሁሉ መገምገም አላባቸው ዲያስፖራው ሳይሰርቅ ኢንቨስተር አይሆንም ሳይሰጥም ይህን ያህል ሊዘባነንም አይችልም።የበሰበሰ የገማ ጋጠወጥ ሥርዓት ሀገር አባላሽቷል ትውልድ አምክኗል በእየዘርፉ ማጣራቱ፣ ማበጠሩ፣መዝራትና መዘረሩ፣በፍጥነት በተቀላጠፈና በተደራጀ መልኩ ይቀጥል በለው!

  2. They were Hodam who now for the Tigres, now let them deal by themselves , who cares about them?

Comments are closed.

Share