ተባበር ወይንስ ተሰባበር!? (ዋስይሁን ተስፋዬ)

ሰኔ 10 ቀን 2006 እ.ኢ.አ.
ከዋስይሁን ተስፋዬ


በኢትዮጵያ ሃገራችን በፍቅር፣ በመተሳሰብና፣ በመቻቻል ለዘመናት የኖረ ህዝብ እርስ በርሱ በጥርጣሬና በጥላቻ ሲጎሻሸም፤ ቤተሰብ ከቤተሰብ መተማመን ጠፍቶ ግለኝነት ሲነግስ፤ የአብሮነታችን ማሰሪያ የሆነው ፍቅራችን ጠፍቶ አንዱ ብሄር በሌላው ብሄር ላይ ጥላቻን ሲዶልት፤ መከባበራችን ረክሶ አንዱ ሃይማኖት ሌላውን ሲጠራጠር፤ ባጠቃላይ በሃገሪቱ ፍቅር ጠፍቶ ጥላቻ ሲነግስ በማየቴ አዘንኩ። ገዢው የኢህአዴግ ከፋፋይ ሥርዓት የዘረጋው አፋኝ መዋቅር ህዝብ ከጥላቻ ውጪ ሌላ ምንም አይነት መረጃ እንዳያገኝ አፍኖ፤ በሃገሪቷ ሰላምና መረጋጋት እንዳይሰፍን፤ ብሎም ኢትዮጵያዊነት ቀስ በቀስ እየተሸረሸረና እየጠፋ እንደሆነ ሳስተውል ደግሞ ፈራሁ። በአንፃሩ ደግሞ ይህ አደገኛ ሁኔታ ለመናገር በሚዘገንን መልኩ አስከፊ በሆነበት በዚህ የጨለማ ዘመን፤ በተቃዋሚስምራሳቸውንሰይመው ‘እኔካልኩትበላይ ምንም ሊሆን አይችልም’በሚልአምባገነናዊአስተሳሰብ፤ በህዝብ ስምለህዝብነፃነትሳይሆን የራሳቸውንየግልፍላጎትለማሳካትየህዝብንበደልበማባባስ ላይ የተሰማሩ ስብስቦች እንደ አሸን በዝተው ስመለከት ተረበሽኩ። በመሆኑም በሃገራችን በጎ ነገር እንዲሰፍን በመመኘት፤ ያላስተዋለ ተገንዝቦ፣ አይቶ ዝም ያለም የሃገርና የህዝብ ውድቀት ነውና ማፈግፈጉን ትቶ ወደ እውነተኛው የህዝብ ነፃነት መንገድ ይራመድ ዘንድ፤  በዚህች አጭር ፅሁፍ ጥቆማዬን ለአንባቢያን ማቅረብን ፈቀድኩ።

ሁላችንም እንደምናውቀው የኢትዮጵያ ህዝብ ደህንነትና የሃገሪቱ ህልውና በኢህአዴግ መንግስት በጎ ፍቃድ ብቻ የሚወሰን መሆኑ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ግልፅ ነው። በመሆኑም መንግስት እንዳሻው ሃላፊነት በጎደለው አካሄድ ህዝብን ለዘመናት ሲያፈናቅል፤ ንጹሃን ዜጎችን መጥፎ ስም በመስጠት ባልሰሩት ሃጥያትና በተፈበረከ የሃሰት ውንጀላ በየእስር ቤቱ እንዲማቅቁ ሲያደረገ፤ የሃገሪቱን መሬት በፈቀደው መልኩ ለባእዳን ሃገራት ሲያድልና ሲሸጥና ብዙ ሌሎች በደሎችን በህዝብና በሃገር ላይ በተደጋጋሚ ሲፈፅም ማየት የተለመደ ሆኗል። በኔ አስተሳሰብ ኢህአዴግ ይህንን ማድረግ የቻለበት ዋንኛው ምክንያት የሚዲያ ተቋማትን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር በመቻሉ ነው። በሃገራችን የሚገኙት መንግስታዊ የሚዲያ ተቋማት የኢህአዴግን የዘረኝነት ፖሊሲ ብቻ በመስበክ በተለይ ወጣቱ ትውልድ ስለ ሃገሩ አንድነት፣ ስለ ህዝቧ ፍቅርና፣ በሃገሪቱ ስላሉት የተቃዋሚ ድርጅቶች እንቅስቃሴ እንዳይሰማና እንዳያውቅ በማድረግ አስተሳሰቡ ከአካባቢው የማያልፍ ጠባብ አድርጎታል። ለዚህም በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል በዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሲተውኑት ያየነው ትእይንት አይነተኛ ምስክር ነው። ለአንድ ሃገርና ህዝብ የወደፊት አቅጣጫና ህልውናን በመወሰኑ ረገድ ሚዲያ እጅግ ወሳኝ ድርሻ አለው።ኢህአዴግ በሚቆጣጠራቸው የሚዲያ ተቋማት የሚያሰራጨውን የዘረኝነትና የእርስ በርስ የጥላጫ መርዝ በመቋቋም የነፃነት ትግሉን ወደፊት መግፋትና ለውጤት ማብቃት የሚቻለው፤ ኢህአዴግ እየፈፀማቸው የሚገኙትን በደሎች ከማጋለጡ ባሻገር፤  ህዝቡ በተቃራኒው ስለአንድነትና ፍቅር እንዲሁም ስለተቃዋሚዎች በቂ እውቀት እንዲኖረውና፣ ልዩነቶቻቸውን አጥብበው በጋራ እንዲሰሩ የሚገባውን ጫና እንዲያደርግ፣ አልያም የመረጠውን መቀላቀል ይችል ዘንድ ሁለገብ መረጃዎችን በስፋት ለህዝብ ለማድረስ የሚሰራ የሚዲያ ተቋም መገንባት ሲቻል ብቻ እንደሆነ ይሰማኛል። በተለይ እንደ ኢህአዴግ የሚዲያ ጠላት በሆነና ህዝብን በዘር፣ በጎሳ፣ በሃይማኖት፣ ከፋፍሎ የእርስ በርስ ጥላቻና ቂም ለማስፋፋት ታትሮ በሚሰራ አረመኔአዊ አገዛዝ ስር ለወደቀ ህዝብ ነፃ የመረጃ ስርጭት እጅግ አስፈላጊ ነው።  

ተጨማሪ ያንብቡ:  የእስረኛው ‹‹ጋዜጠኝነት›› ሌላ ፈተና - በጽዮን ግርማ

ሁላችንም እንደምናየው የኢትዮጵያ ህዝብ በአሁኑ ወቅት የተቃዋሚ ቡድኖች ከመጠን በላይ በመብዛታቸው ምክንያትና መረጃ በብቃት ስለማይደርሰው፤ የድርጅቶቹን አላማ፣ ግብ፣ ራእይ፣ በጎ ጎኖችና ግድፈቶች፣ እንዲሁም ሌሎች ልዩነቶቻቸውን በቅጡ መለየት ተስኖት፤ ምኑን ከምኑ፣ የትኛውን ከሌላኛው መለየት ባለመቻሉ ግራ በመጋባቱ ‘የነፃነት ትግል የውሸት፤ ፖለቲካ አይንህ ላፈር’ በሚል የተሳሳተ አስተሳሰብ ተወስኖ፤ የሚደርስበትን ችግር ለማስቆም በጋራ ከመታገል ይልቅ በዝምታ መቀመጥን መርጦ ይገኛል። በመሆኑም የተቃዋሚ ድርጅቶች ያለ ህዝብ ተሳትፎ ብቻቸውን ሲያጨበጭቡ ይታያሉ።   

ከላይ ለመግለጽ የሞከርኳቸውንና ሌሎች መሰል ችግሮችን ለመቅረፍ ዋንኛ መሳሪያው ብቃት ያለው የሚዲያ ተቋም መኖር በመሆኑ የተለያዩ የተቃዋሚ ቡድኖች ተቋማትን መስርተው ሲንቀሳቀሱ እናያለን። ነገር ግን እዚህጋ ሊሰመርበት የሚገባው ጉዳይ ተቋማቱን መመስረት ብቻ ሳይሆን የሚያስተላልፉት የመረጃ ይዘቶችና አይነቶች እጅግ ወሳኝ መሆናቸውን ነው። በኔ እይታ የሚዲያዎች አትኩሮት በተለየ ሁኔታና በስፋት፤ በተቃዋሚዎች መካከል ያሉትን ልዩነቶች፣ የተቃዋሚዎችን በጎ ጎኖችና ግድፈቶች፣ ከገዢው መደብ ጋር ያላቸውን ልዩነቶች በመረጃ ማቅረብ፣  ለሁሉም የፖለቲካ ሃይሎች ያለ አድልዖ እኩል መድረክ የሚሰጡና በሃገሪቷ ታሪካዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ተቃራኒ አመለካከቶች ያሏቸውን ምሁራንንና የፖለቲካ ሰዎችን በማወያየት ህዝብ በስነልቦና በእውቀት እንዲጎለብት በስፋት የሚሰሩ ሊሆኑ ይገባል። ከዚህ መነሾነት ሲስተዋሉ በአሁኑ ወቅት ለኢትዮጵያ ህዝብ እውነተኛ መረጃን ለማስተላለፍ በሚል አላማ ከሚሰሩት የሚዲያ ተቋማት አብዛኛዎቹ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የኢህአዴግን መሰረታዊ አላማዎች ከማስተጋባት ያለፈ የሚጨበጥ ስራ ሲያከናውኑ አይታዩም። በእርግጥ አንፃራዊ በሆነ ሁኔታ ስመለከታቸው እንደ Addis Dimts Radio፣ SBS Australia፣ የVOA እሰጥ-አገባና እንወያይ የራዲዮ ዝግጅቶች ሊመሰገኑ  የሚገባ መሆኑን ለመጠቆም እወዳለሁ። 

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት 60 በመቶ ቡና አብቃይ አካባቢዎች ከአምራችነት ውጭ ሊሆኑ እንደሚችሉ ተመራማሪዎች ይፋ አደረጉ

ከአድማጮችና ከደጋፊዎች ብዛት አንፃር የኢሳት ራዲዮና ቴሌቪዥን ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዝ ስለሚመስለኝ ሃሳቤን ለመሰብሰብ ይሆን ዘንድ፤ ታዋቂ ሰዎችና የፖለቲካ መሪዎች ከአድማጮች ለሚቀርቡ ጥያቄዎች በኢሳት ራዲዮ ምላሽ የሚሰጡበት፤ የ “ጥያቄ አለኝ” ዝግጅት ላይ፤ የኢሳት ቴሌቢዥንና ራዲዮ በማኔጅመንት ዳሬክተሩ በአቶ ነአምን ዘለቀና በጋዜጠኛ ብሩክ ይባስ ትብብር መላሽ የነበረበትን ለሁለት ሳምንታት የተላለፈ ዝግጅት ላይ ከአንድ አድማጭ የቀረበ ጥያቄንና ከኢሳት የተሰጡ መልሶችን እንደምሳሌ ማንሳት አስፈላጊ ነውና ከዝግጅቱ ከታዘብኩት ጥቂት ልበል። እኝህ ኢትዮጵያዊ የኢሳት አድማጭ ለኢሳት ያቀረቡት ጥያቄ ከላይ ካነሳሁት መሰረታዊ ሃሳብ ጋር በፅኑ ስለሚገናኝና አድማጩ ኢሳትን ሊያስገነዝቡ የሞከሯቸው ጭብጦች በአምባገነን ስርዓቶች ለአመታት ሲሰቃይ ለኖረው ህዝብ ነፃነት መጎናፀፍ ጉልህ ሚና ስለሚኖራቸው፤ ጥያቄያቸውም የበርካታ ኢትዮጵያውያንም ጥያቄ እንደሆነ ስለምገምት ለአንባቢያን ጥያቄውን አቀርባለሁ።  

ምስጋና ይህን ወሳኝ ጥያቄ ላቀረቡት ለእኝህ ቀና ኢትዮጵያዊ የኢሳት አድማጭ ይድረስና፤ ባይሳካም የጉዳዩን ወሳኝነት ለማሳሰብ አቀራረቡን የበለጠ ግልፅ አድርገው በሁለተኛው ሳምንትም በድጋሚ ጠይቀዉት ነበር።  ወደ ተነሳሁበት ጉዳይ ልመለስና፤  እንደኔ አረዳድ የጥያቄያቸው መንፈስ ይህን ይመስላል፤ “እስካሁን ድረስ የተለያዩ መረጃዎችን ስትሰጡን ኖራችኋል። ነገር ግን የምትሰጡን መረጃዎች የኢትዮጵያ ህዝብን ወደ ድል ሊያበቁ አልቻሉም። ሁላችንም እንደምናየው ወያኔ የሚፈልገዉን ነገር ከማድረግ የሚያግደው ምንም ሃይል ሊፈጠር አልቻለም። የዚህ ዋና ምክንያት ደግሞ የምትሰጡት መረጃ ወያኔ በደሉን ከህዝብ ለመደበቅ የጭቆና ስልቱን በመቀየር ስህተቱን እንዲያርም ከማድረግና ከማገልገል በስተቀር ለህዝብ የረባ ፋይዳ አላስገኘም።  ለወያኔ ደካማ ጎኑን እንደምትነግሩት ሁሉ፤ ለተቃዋሚዎችም ስህተታቸውን እንዲያርሙ እንድታሳስቧቸው ዘንድ፤ ብሎም ተቃዋሚዎች እየሰሩት በሚገኙት በደል ምክንያት ለነፃነቱ ላለመቆም ሳይወድ እንዲሸሽ ለተገደደው የኢትዮጵያ ህዝብ ብርታት እንደሚሆነው በማስገንዘብ ከብዙ አድማጮች አስተያየት ቢሰጣችሁም፤ ተግባራዊ ልታደርጉ አልቻላችሁም። የኢትዮጵያ የተቃዋሚ ሃይሎች ኢህአዴግ ከሚያጠፋው በላይ በኢትዮጵያ ላይ ትልቅ ጥፋት እያደረሱ ይገኛሉ፤ ምክንያቱም እኔ ካልኩት ሃሳብ በላይ ማንም ሊሆን አይችልም ብለው ስለሚያምኑ፤ ልስራ ብሎ የሚመጣውን አንዱ ሲያዳክም፤ አንደኛው ሌላኛውን ሲያጠፋ እያየን እንገኛለን።  ፊትለፊት አምጥታችሁ አገናኝታችሁ በጋራ እንዲሰሩ ልዩነቶቻቸውን ህዝብ አውቆ እንዲፈርድና የመረጠውን እንዲቀላቀል የማትረዱት ለምንድነው?”። 

ተጨማሪ ያንብቡ:  የትግራይ ህዝብ የወያኔ ስርአት ተጠቃሚነው! (አንዷለም አስራት )

ለጥያቄው በትብብር የሰጡትን መልስ መሰረት በማድረግ ለአቶ ነአምን ዘለቀና ለጋዜጠኛ ብሩክ ይባስ ማሳሰብ የምፈልጋቸው ነጥቦች፤ የእኚህ  አድማጭ ጥያቄ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ጥያከ መሆኑን፣ የተጠየቀው ጥያቄ እርስዎ(አቶ ነአምን) አስረግጠው እንዳስገነዘቡን የኢሳትን ነፃ ሚዲያነት የሚጋፋ ሳይሆን በተቃራኒው ኢሳት እንደ አንድ ለኢትዮጵያ ህዝብ መረጃ ለማቀበል የሚሰራ ነፃ የሚዲያ ተቋም በስፋትና በከፍተኛ ትኩረት ሊሰራበት የሚገባዉን ወሳኝ ጭብጥ የያዘ መሆኑን፣ ለህዝብ ነፃነት የሚበጀው አንድ የተቃዋሚ ድርጅት ትእይንት ባዘጋጀ ቁጥር ብቻ ወይንም ገዢው መንግስት በህዝቡ ላይ በደል በፈጠመ ጊዜ ብቻ የተቃዋሚ መሪዎችኒና ታዋቂ ግለሰቦችን ማነጋገር ሳይሆን፣ የህዝቡን የመረጃ ክፍተት መሰረት ያደረገና ዘላቂነት ያላቸው የተጠኑ ውይይቶችን ለህዝብ ጆሮ ማቅረብ እንዳለበት ለማስገንዘብ የቀረበ መሆኑን አውቃችሁ ግዴታችሁን ለመወጣት ብታተኩሩ መልካም ነው፣ የሚሉ ናቸው።

በዚህ አጋጣሚ የኢሳት ራዲዮና ቴሌቪዥን ገዢው የኢህአዴግ መንግስት በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚያደርሳቸውን በደሎች በማስተጋባት ብሶቱን ለማሰማት እለት ተለት የሚያደርገውን ጥረት ለማድነቅ እወዳለሁ። ሆኖም በኔ እይታ ይህ የኢሳት ራዲዮና ቴሌቪዥን ጥረት ብቻውን፤ ለህዝብ ብሶቱን ከማሰማት ያለፈ አስተዋዕፅዎ ይኖረዋል ብዬ አላምንም። በመሆኑም ኢሳት እንደ ነፃ የሚዲያ ተቋም ህዝቡ በቂ መረጃን አግኝቶ እየደረሱበት የሚገኙትን ከመጠን ያለፉ ችግሮች ለማስቆምና፤ ብሎም ለነፃነቱ በጋራ ትግሉን ይቀላቀል ዘንድ ለማስቻል፤ የህዝብ ብሶትን ከማሰማት ባለፈ እጅግ በጣም ብዙ መስራት የሚጠበቅበት መሆኑን በማስገንዘብ፤ የህዝብ ነፃነትን  እውን ለማድረግ በሚደረገው ትግል ላይ እንደ ሚዲያ ሃላፊነቱን ለመወጣት መጠነ ሰፊ የሆነ የዝግጅትና የአቀራረብ ለውጥ ማድረግ እንደሚኖርበት ጥቆማዬን አቀርባለሁ።

ይህን ሃሳብ ሳካፍል ፅሁፌን ያየ ያነበበ የኢትዮጵያ ልጅ ሁሉ፤  እኔ የተረዳሁትን ተረድቶ መፍትሄውን እንዲፈልግ፤ አልያም ሃሳቤን ለማካፈል የሞከርኩት ነፃሚዲያያጎናፀፈኝንእድል’ተጠቅሜ ነውና፤ ከተሳሳትኩ የመታረም መብቴ የተጠበቀ መሆኑን እንዲረዳልኝ እጠይቃለሁ። ስለሆነም የኔ ማጠቃለያ የነፃ ሚዲያዎች ትኩረትና የአንባቢያን ጠቃሚ አስተያየት እንደሚሆን በእጅጉ ተስፋ አደርጋለሁ።

ቸር እንሰንብት

ከዋስይሁን ተስፋዬ

ttwasyhun@gmail.com

 

1 Comment

  1. ጥሩ ተደርጎ የተከሸፈ ጽሁፍ ነው:: ሊያስተላልፍ የታሰበውም መልዕክ ጊዜያውና አንገባጋቢ ነ :: ነገር ግን ጸሃፊው በተለይ ኢሳት ቢያደርገው ብለው የተመኙትና ያሳሰቡት ኢሳት ካለበት የገንዘብና የሰው ሀይል እጥረት ጋር ቢያገናዝቡት መልካም ነበረ::

Comments are closed.

Share