January 5, 2015
13 mins read

Health: ብስጭት ይታከማል ወይ?

angry face

‹‹ከሁለት ዓመት በፊት በደረሰብኝ ከባድ የመኪና አደጋ ምክንያት በቀኝ እጄና እግሬ ላይ የእንቅስቃሴ ችግር ቢፈጠርብኝም ከቀን ወደ ቀን ግን የእጆቼ መስለል እና መቅጠን የህሊናዬን እረፍት የነሳኝ ስለሆነ አፋጣኝ ምላሻችሁን በመስጠት ከሀሳብ የምፀዳበትን ምክር እንድትለግሱኝ እጠይቃለሁ፡፡

በ2001 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኬሚስትሪ ዲፓርትመንት የአራተኛ ዓመት ተመራቂ በነበርኩበት ሰዓት የመመረቂያ ጊዜዬን በጉጉት በመጠበቅ ላይ ሳለሁ በድንገተኛ የመኪና አደጋ የከፍተኛ ጉዳት ሰለባ ሆኛለሁ፡፡ በሰዓቱም እጅግ በማዘንና በመከፋት ይህችን ዓለም በክፉኛ ምሬት ያዘንኩባት ወቅት ብትሆንም የነበረኝን የትምህርት ጊዜ ግን በማጠናቀቄ ለፈጣሪዬ ምስጋናን ከማቅረብ አልቦዘነኩም፡፡ ሙያውን በተመለከተ ብቻ ሳይሆን ከዚህ ጋር በተያያዘም የስነ ልቦና ምክር እንድትሰጡኝ ከአደራ ጭምር አሳስባለሁ››

ኤኬ

 ማንም ሰው በህይወት ዘመኑ ሲኖር የዛሬን እንጂ የነገን ስለማያውቅ በደረሰብህ ጉዳት ያሳለፍከውን የህይወት ውጣ ውረድ እንደ ችግር ብታየው ነገ ግን ከፊትህ ያለውን በመልካም እና በጥሩ በማሰብ ራስህን ማፅናናት ግድ ይልሃል፡፡ በዚህም ምክንያት ለአንድ ወር ከአስራ አምስት ቀን በሆስፒታሉ መኝታ ክፍል የህክምና አገልግሎት በማግኘት ያሳለፍክ ቢሆንም በተመላላሽ ህክምና ደግሞ ለስድስት ወራት ያህል እንደቆየህ የላክልን መረጃ ያሳያል፡፡ ነገር ግን በተደረገልህ ቀዶ ጥገና ምክንያት በጤንነትህ ላይ የፈለከውን ያህል ለውጥ ባለማየትህ ሙሉ በሙሉ ደስተኛ አለመሆንህን ያሳያል፡፡ ምናልባትም በቀዶ ጥገና ጊዜ በተፈጠረ የኦፕሬሽን ስህተት ላልተለፈገ ጉዳት ተዳርጌ ይሆን ወይ? በማለት ኦፕሬሽን ካደረገ የህክምና ባለሙያ ጋርም በነበረህ የመጨረሻ ቀጠሮ ላይ ውይይት እንዳደረግህ ብትገልፅልንም ከሐኪምህ የተሰጠህን መልስ ግን በውሉ አላሳወቅከንም፡፡ ከቅርብ ወራት ወዲህ ደግሞ የሽንትና የሰገራ መውጫ ሰዓት የሚሰማኝን ስሜት ማወቅ እየተሳነኝ አይነ ምድሬንም ሆነ ሽንቴን በመፀዳጃ ቤት መጠቀም እስከማልችልበት ድረስ ደርሻለሁ ብለኸኛል፡፡ ምናልባትም ይህ ሁኔታ ለህሊና ረፍት ማጣትህ ትልቁን ድርሻ ይይዛል ብለን እንገምታለን፡፡ ኤኬ የመኪና አደጋ ከደረሰብህ በኋላ ለምን ያህል ጊዜ የህክምና እርዳታውን ሳታገኘ ቆይተሀል የሚለው ጥያቄ በእኛ በኩል ወሳኝ ጥያቄ ነው፡፡ ምክንያቱም አደጋ እንደደረሰብህ የሚፈልገውን ምርመራ ሁሉ ተደርጎ የቀዶ ጥገና ስራ እንኳን የሚያስፈልግ ከሆነ በወቅቱ ማድረግ በቀጣይ የሚኖረውን ለውጥ የተሻለ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ ያለበለዚያ የተፈለገውን ያህል ውጤት ማግኘት አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ በአከርካሪ አጥንት (spinal cord) ወይም በአንጎላችን (Brain) አካባቢ የሚፈጠረው አደጋ ከነርቭ ጋር የተያያዘ ስለሚሆን የሰውነት ክፍላችንን ማዘዝና መቆጣጠር ይችላል፡፡

ይሄ የሰውነት ክፍልም የቀዶ ጥገና የሚደረግበት ወቅት ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚጠይቅ መሆኑ ከኦፕሬሽን በፊት ሰፋ ያለ ዝግጅት ይደረጋል፡፡ በቀኝ በኩል የእጅህና የእግርህ ክፍል በፈለከው መልኩ አለመታዘዝ ከነርቭ ጋር የተያያዘ ጉዳትን የሚያመላክት ቢሆንም ሐኪምህ በሚሰጥህ ምክር ግን ህክምናህን በአግባቡ ከተከታተልክ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ትችላለህ፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜም የመስለልና የመቅጠን አይነት ምልክት በተጎዱት የሰውነት ክፍሎቼ ላይ ታይቷል ብለህ የምታምን ከሆነ ግን ዛሬ ነገ ሳትል ወደ ሆስፒታሉ በመሄድ እንደገና መታየቱ ወደ ፊት ሊመጣ የሚችለውን የባሰ ችግር መቀነስ ያስችላል፡፡ ከእንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የሰውነት ማፍታቻ ሊሆን የሚችል ግብአቶችንም በባለሙያ ትዕዛዝ ሙሉ በሙሉ የምንጠቀም ከሆነ ከዕድሜ መግፋት ጋር ተያይዘው የሚፈጠሩትን የአላስፈላጊ የሰውነት መላሸቅን መቋቋም እንችላለን፡፡

ፊዚዮቴራፒ (physiotherapy) ህክምናም ከእንደዚህ አይነት አደጋም ሆነ ህመም ጋር ሊከሰት የሚችል የጤና ችግርን ማዳን ወይንም የጉዳት ደረጃውን መቀነስ ያስችላል፡፡ የህክምና ክትትሉ እንዳለ ሆኖ ግን በተጨማሪነት ለአራት ዓመታት የለፋህበትን የትምህርት ውጤት በስራ ተግብሬ ሀገሬንም ሆነ ራሴን አሁን ላለሁበት የጤንነት ሁኔታም ልጠቅም እችላለሁ ወይ የሚለው የሁለተኛ ጥያቄ ነው፡፡

ለዚህም የአካል ጉዳተኝነት በብዙ አይነቶች ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ እንደ ምሳሌ የእጅ፣ የእግር፣ የማየትና የመስማት መሳን፣ የአዕምሮ ዘገምተኝነት በከፊሉ ሊነሱና ሊጠቀሱ የሚችሉ ሲሆን ከዚህም ባሻገር በህብረተሰቡ ዘንድ ተከስተው የምናያቸው ናቸው፡፡ በአካል ጉዳተኘነት ብቻ ግን ሰው መስራት እየፈለገ ጉዳቱ ምክንያቱ ሆኖብሃል በማለት እራሱን ከስራ የሚያገል ከሆነ ይህ ሰው ከስነልቦና ችግር ጋር በተያያዘ የባለሙያ ምክር አስፈላጊው ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ሲባል ደግሞ የአካል ጉዳተኛ የፈለገውን ስራ ሁሉ መስራት ይችላል ማለት እንዳልሆነ ተገንዝበን ማለፍ አለብን፡፡ የስራህ አይነት ሊሆን የሚችለው በተማርከው የትምህርት ዘርፍ እንደሆነ እንገምታለን፡፡ ስለዚህ የጠቀስክልን የህመም አይነት እና ጉዳት አንተ ካሰብከው አላማና ግብ የሚያስተጓጉል ነገር ስለማይኖው ለስራ አመቺ የሆነ ቦታን መምረጥና ማመቻቸት ጠቀሜታ እንዳለው መንገር እንፈልጋለን፡፡ የሰው ድጋፍ ከመሻት እና የሰውን እጅ ከማየት በራስ ሰርቶ ማደር ጠቀሜታው የጎላ ቢሆንም በአቅምህና በደረጃህ ያሰብካቸውን አላማዎች ሁሉ ለማሳካት ግን ጥረትህ ወሳኘ መሆን አለበት፡፡ የደም ግፊት በሽታ፣ የስኳር በሽታ እና የነርቭ በሽታ ከመኪና አደጋ ያልተናነሰ የአካል ጉዳተኝነት ሊያመጡ ቢችሉም የበሽታውን መንስኤ ግን በወቅቱ ማወቅ ከተቻለና አስፈላጊውን ክትትል ከተደረገ ጉዳቱን መከላከልም ሆነ መቆጣጠር የሚቻልበት መንገድ ይኖራል፡፡ አደጋ በራሱ ህመም ቢሆንም ዘወትር ስለደረሰው ጉዳት የምናስብ ከሆነ ግን የህሊና እረፍትን በማጣት ካሰብነው ግብ መድረስ የማንችልበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ አንድ ሰው የአካል ጉዳተኝነትን በተፈጠሮ ወይም ከውልደቱ በኋላ ባላሰበው ጊዜና ወቅት ሊያገኘው ቢችልም መንፈሰ ጠንካራ በመሆን ግን ሊከሰትበት የሚችለውን ችግር ሁሉ በትዕግስት ማሳለፍ ይችላል፡፡ በአገራችን በመኪና አደጋ የሚከሰተው ቀላልም ሆነ ከባድ የአካል ጉዳት በበሽታ ምክንያት ከሚመጣው የአካል ጉዳተኝነት ይበልጡን ቦታ ይይዛል፡፡ ስለዚህ መስራት ወደ ምትፈልግበት ቦታ እንደልብ በትራንስፖርት ለመንቀሳቀስ የሚያስቸግርህ ባለመሆኑ ለስራህ እንቅፋት ሊሆን የሚችል ነገር ይኖራል ብለን አናስብም፡፡ ከነርቭ ጋር በተያያዘ የሚመጡ የሰውነት ጉዳቶች በወቅቱ የህክምና አገልግሎት ቢደረግባቸውም የለውጥ ሂደታቸውን የሚያሳዩት ግን ቀስ በቀስ ነው የሚሆነው፡፡ እንደሌላው ህመም መድሃኒት ስለተወሰደ ብቻ ብዙውን ጊዜ አፋጣኝ ምላሽ አይታይባቸውም፡፡ በአንጎላችን እና በአከርካሪ አጥንት አካባቢ የሚከሰቱትን የጤና ችግር መለየት የምንችለውም በኤም.አር.አይ (MRI) ወይም ሲቲስካን (CT Scan) በሚባል መሳሪያዎች ይሆናል፡፡ በሀገራችንም እነዚህ ሁለት መሳሪያዎች በግል የህክምና ዘርፍ በሰፊው ይገኛሉ፡፡ በአንጎላችን አካባቢ የሚከሰተው የውስጥ የአንጎል ክፍል እብጠት (Brain Tumoir) ሲሆን በአከርካሪ አጥንት ደግሞ ዲስክ መንሸራተት ነው፡፡ እነዚህ ደግሞ ዋነኛው የነርቭ ስራ መቋረጥን ያስከትላል፡፡

በተለያየ ጊዜ ከሰውነት ጉዳት ጋርም ሆነ ከአየር ንብረት መለዋወጥ ጋር በተያያዘ አንዳንድ የነርቭ በሽታዎች ወቅታዊ የሚሆኑበት አጋጣሚ ስለሚኖር አስፈላጊው ሁሉ ጥንቃቄ መደረጉ ተገቢ ነው እንላለን፡፡

ውድ የመጀመሪያ ተሳታፊያችን ኤኬ በአካል ጉዳተኝነት በኩል ሊነሱና ልንጠብቃቸው የሚገቡ ብዙ ጉዳዮች እንዳሉ መገንዘብ አለብህ፡፡ የአካል ጉዳተኛ በመሆንህ ብቻም በራሱ አንዳንድ ጊዜ የጥቃት ሰለባ የምትሆንበት ሁኔታ ስላለ እንቅስቃሴህን ጥንቃቄ በተሞላበት መልኩ ማድረግ ይገባሃል፡፡ ከዚህም ባለፈ የምትሰራቸው ስራዎች ከጤንነትህ ጋር በአግባቡ ሊዛመዱ የሚችሉ ስለመሆኑ ማሰብ አስፈላጊ ነው እያልን እናጠናቅቃለን፡፡

 

Previous Story

በአፋር ከ40 በላይ የሚሆኑ ወጣቶች የትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ጫካ ገቡ

Next Story

ለመላው የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፥ – ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop