ከመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የተላለፈ ጋዜጣዊ መግለጫ “ሕዝባዊ አንድነት ለነፃነት

ለአለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት የሕዝብን መብት በመቀማትና አፍኖ በሥልጣን ላይ የሚገኘው የህወሃት/የኢህአዴግ መንግሥት ዜጐች በአገራቸው ውስጥ በመዘዋወር ሰርተው እንዳይኖሩ ያገደ ብቻ ሳይሆን በተወለዱበትና እየኖሩበት በአለው ቀያቸውም የገዠው ፓርቲ አባል ካልሆኑ ወይም ደግፈው ካልቆሙ ይሰደዳሉ፣ ይበታሰራሉ፣ ይደበደባሉ፤ በተለያዩ ምክንያቶችም ንብረታቸውን ይቀማሉ፡፡ የተቀዋሚ ፖለቲካ ድርጅት አባል ከሆነ ደግሞ ጫናው ምን ያህል እንደሆነ መገመት ይቻላል፡፡ በዚሁ መመሪያቸው መሠረትም በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች በሚገኙ የመኢአድ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ከፍተኛ የሆነ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመባቸው ይገኛል፡፡ ከሰብአዊ መብት ጥሰቶች መካከልም ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህልም፡-


1. በደቡብ ክልል በሰሜንአሪ ወረዳ በጉዛ ዚፍቲ ቀበሌያት የሚኖር ሕዝብ ሕገ-መንግሥታዊ መብቻውን ተጠቅመው በመኢአድ ጥላ ሥር ስለተደራጀና ጽ/ቤት ስለከፈቱ ብቻ ሦስት (3) አመራሮቻቸው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ፍትህም ተከልክለው ሰሚ አካል ሊያገኙም አልቻሉም፡፡


2. በጐፋ ልዩ ዞን የሚገኙ የመኢአድ አመራሮችና አባላት ሕገ-መንግሥታዊ መብታቸውን ተጠቅመው ስለተደራጁ ብቻ ከፍተኛ ድብደባና እስር ደርሶባቸዋል፤ የፓርቲው መታወቂያቸውንም እንዲነጠቁ ተደርጓል፡፡ በአሁኑ ጊዜም አስራ ሁለት (12) የመኢአድ አባላት በሳውላ ማረሚያ ቤት በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡


3. በደቡብ ክልል በደራሼ ልዩ ወረዳ የመኢአድ የወጣቶች የአመራር አባል በጩቤ ተወግተው ለፍትህ አካላት አቤት ቢሉም መልስ አጥተው በችግር ላይ ይገኛሉ፡፡
4. በአማራ ክልላዊ መንግስት በአንካሻ ወረዳ የሚገኙ የመኢአድ አመራር በኢህአዴግ ካድሬዎች ተደብድበው በሕክምና ላይ ይገኛሉ፡፡ ከትናንት በስቲያ ማለትም ሚያዚያ 22 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ በጐንደር ከተማ በመንግሥት ታጣቂዎችና በሕዝቡ መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት የብዙ ዜጎች ሕይወት እንዲጠፋ ሆኗል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብዙ ዜጎችም ከቤታቸው እየታፈኑ ወደ አልታወቀ ቦታ እንዲወሰዱ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሰንሹ የጦርነት ጥበብ ላማራ ሕዝባዊ ግንባር፤ ማጥቃት መከላከል ነው


5. በተለያዩ ኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች በመማር ላይ የሚገኙ ተማሪዎች ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር በአደረጉት ግጭት ምክንያት ብዙ ዜጎች ሕይወታቸውን አጥተው፤ ብዙ ንብረትም ወድሟል፡፡


ይህ የሚያሳየን የህወሃት/ኢህአዴግ መንግሥት የማስተዳደር ስልት ችግሩን በዘዴ በመፍታትና በማግባባት ሳይሆን ኃይልን በመጠቀም ላይ ብቻ ያተኮረ መሆኑን ነው፡፡
በአጠቃላይ እንደዚህ ያሉ የከፉ የሰብአዊ መብት ረገጣ አገር ተረካቢውን ወጣት ምሁር ኢትዮጵያውያን አገራቸውን ጥለው እንዲሰደዱ አድርጓቸዋል፡፡


ስለዚህ የመላው ኢትዮጰያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን በመቃወምና ከተበዳዮች ጐን የቆመ መሆኑን ለማሳየት “ሕዝባዊ አንድነት ለነፃነት” በሚል መሪ መፈክር በመላ አገሪቱ ሕዝባዊ ንቅናቄ ለመፍጠር ከዜጎች ጐን የቆመ ድርጅት መሆኑን ለማሳየት ሰላማዊ ሰልፎችን አዘጋጅቷል፡፡ በዚሁ መሠረትም እሁድ ግንቦት 3 ቀን 2006 ዓ.ም በጐፋ ልዩ ዞን በሳውላ ከተማ ከፍተኛ ሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ አድርጓል፡፡


ስለዚህም የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለነፃነት ሲል ከጐናችን እንዲሰለፍ ታላቅ ሕዝባዊ ጥሪ ያስተላልፋል፡፡
አንዲት ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

Share