ኢትዮጵያ እውነተኛ ልጇን አጣች

ብዙ የውጭ ሃገር ሰዎች ሃገራችንን ይወዳሉ። ከነዚህ ውስጥ አንዱ የኦስትርያ ተወላጅ የሆነው ካርልሃይንዝ ቦይም(Karlheinz Böhm ) ነበር። ነገር ግን ካርልሃይንዝ የዓለም ዜጋ(Weltbürger) ነኝ ብሎ ነበር የሚያምነው። ቢሆንም ካርልሃይንዝ 2003 የኢትዮጵያ የክብር ዜግነት ተቀብሏል።

ይህንን ታላቅ ሰው ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት ኢሊባቡር ውስጥ ጉመሮ ሻይ ተክል መጥቶ በነበረበት ወቅት ነው። በዚያ ወቅት የተነገረን የፊልም ተዋንያን መሆኑን ብቻ ነበር። ጀርመን ከመጣሁበት ቀን ጀምሮ ስለዚህ ሰው ደግነት በሰፊው ልረዳ ችያለሁ።

ካርልሃይንዝ በተወለደ በ86 ዓመቱ ያለፈው ሐሙስ ሌሊት ሳልዝቡርግ – አውስትሪያ ውስጥ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

ካርልሃይንዝ በኦስትርያ፣ በጀርመን እና በሲዊዘርላንድ የተከበረ የፊልም ተዋንያን ነበር። ካርልሃይንዝ የታወቀው ንጉስ ፍራንዝ( Kaiser Franz Joseph) ሆኖ በሠራው ፊልም ነበር። ከዛም በኋላ በተከታታይ ብዙ ፊልሞች ሰርቷል። ይህ ሰው በፊልም ታዋቂነቱ ሳያግደው ፣ የተንደላቀቀው ኑሮው ሳያጓጓው የሃገራችንን ሕዝብ ኑሮ እዛው እየኖረ ሕዝብን መርዳት የወሰነው 1976 ኬንያ ውስጥ ሆኖ ስለ አፍሪካ ችግር ባወቀበት ወቅት ነበር።

በጀርመን፣ በኦስትሪያና በስዊዘርላንድ ለሦስት ሃገሮች በሚተላለፈው የቴሌቪዥን የውድድር ፕሮግራም (“Wetten, dass..?”) ላይ በ1981 በእግድነት ቀርቦ ከሕዝቡ ጋር የውድድር ሃሳብ ያቀርባል ። በአፍሪካ ለደረስው ችግር እርዳታ የሚሆን ይህንን የቴሌቪዥን ፕሮግራም ከሚመለከተው ሕዝብ አንድ ሦስተኛው . . . አንድ የጀርመን ማርክ ወይም አንድ የስዊስ ፍራክ ወይም 7 የኦስትሪያ ሽልንግ ከሰጠ ችግሩ ባለበት ቦታ ሄጄ እረዳለሁ ብሎ ይወዳደራል።

ካርልሃይንዝ ምንም እንኳን በሚሊዮን የሚቆጠር እርዳታም ቢያገኝም የተከታተለው ሕዝብ አንድ ሦስተኛው የተወዳደረበትን ገንዘብ አልሰጠም። በዚህ ምክንያት ውድድሩን ያሸንፍና ወደ አፍሪካ መሄድ ግዴታው አይሆንም። ቢሆንም ግን ይህ ታዋቂ የፊልም ሰው ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በዓላማው በመጥናት የተንደላቀቀውን ኑሮውን እርግፍ አድርጎ በመተው ኢትዮጵያ ውስጥ የችግረኛውን ኑሮ እየኖረ እርዳታውን ለመስጠት ወሰነ። ከ1982 ጀምሮ ከፊልም ስራው ተለያይቶ በእርዳታው ላይ ብቻ አተኮረ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ተገዳድለህ መፍትሄ አታመጣም   (ወለላዬ ከስዊድን)

ካርልሃይንዝ “ሰው ለሰው“ . . . “Menschen für Menschen” የሚባል ድርጅት አቋቁሞ ከ1981 ጀምሮ እርዳታ ሲደርግ ቆይቷል። እዛው ሃገራችን ውስጥ ካርልሃይንዝ ከወይዘሮ አልማዝ ጋር ተጋብቶ ይኖር ነበር። ወይዘሮ አልማዝ ካርልሃይንዝ ከታመመበት ጊዜ ጀምሮ የእርዳታ ድርጅቱን ሲመሩ ቆይተዋል። ካርልሃይንዝ 7 ልጆች ሲኖሩት ሁለቱ ከወይዘሮ አልማዝ የተወለዱ ናቸው።

ለካርልሃይን ቤተሰቦች መጽናናትን እመኛለሁ።

በዚህ አጋጣሚ የድረገጽ ባለቤቶች የዚህን ታላቅ ሰው ፎቶ በመለጠፍ ለሃገራችን ብዙ ላገለገለው ሰው ሃዘናችንን እንድንገልጽ ታደርጉልን ዘንድ በትህትና እጠይቃለሁ።

http://www.dw.de/the-two-lives-of-karlheinz-böhm/a-17672792

በልጅግ ዓሊ – ፍራንክፈርት – 30.05.2014

5 Comments

  1. ጊዜውን ገንዘቡን ህይወቱን ለተራቡ ለተጠሙ ለተቸገሩ ኢትዮጵያውያን አሳልፎ የሰጠ ደግና ሩህሩህ ሰው ነበር፣ኢትዮጵያውያን የገዛ ወገኖቻችን ከመሬት እያፈናቀሉ ለአመታት የኖሩበትን ቤት በቡልዶዘር እያፈረሱ ጎዳና ላይ እየጣሉ ለውርጭ ለጸሃይ እና ለጅብ እያጋለጡ ወገናችንን ሲዘርፉ ስለፍቅር ብሎ የሚወደውን ሞያውንና ሀገሩን ጥሎ ወገኖቻችንን የታደገ ድንቅና ታላቅ ሰው ነበር፣ ኢትዮጵያውያን መቼም መቼም ልንረሳው የማይገባን ነው፣እግዚአብሄር ለእኛ ላደረገልን ውለታ በመንግስተ ሰማይ ይክፈልልን።ለልጆቹና ለባለቤቱ መጽናናትን ፈጣሪ አምላክ ይስጥልን፥አሜን

Comments are closed.

Share