አማሪካ ነው የምኖረው (ሄኖክ የሺጥላ)

ሄኖክ የሺጥላ
አሜሪካ ነው የምኖረው። የወሩ መሃል ላይ የምድር ገነት፣ የወሩ መጨረሻ ላይ ተደበቅ ተደበቅ የምታስብል ሀገር ። በአሜሪካ ብዙ የሚማርኩ ነገሮች አሉ ፣ ውበታቸውን በብር እንጂ በብዕር ለመግለጽ የሚዳግቱ። የአንዳንድ ፎቆች ርዝመት ጫፋቸውን ልታይ ከሞከርክ ወደ ሁዋላህ ትወድቃለህ። ግድቦቻቸው ድንቅ ናቸው፣ ግን አንዳቸውም በቦንድ ግዥና ክፍያ አልተገነቡም፣ ምክንያቱም የእድገት እንጂ የፍርሃት ውጤቶች ስላልሆኑ። ሙሁሮቻቸው ለችግር መፍትሄ ማፍለቅ የሚችሉ ናቸው፣ ምክንያቱም ከችግር ለማምለጥ ሳይሆን የሚወዱትን የተማሩ፣ አልመውና ተልመው የሚጉዋዙ ስለሆኑ። በአማሪካ ልጅን መምታ ( መቅጣት) አይቻልም፣ ጥፋቱን ታስረዳዋለህ ፣ እድለኛ ከሆንክ ይሰማሃል ፣ እድለኛ ካልሆንክ ሊቭ ሚ አሎን ይልሃል፣ (ምን ታመጣለህ ?!) ፖለቲከኛ ካልሆንክ እና ዘዴኛ ከሆንክ ፣ ኢትዮጵያ ወስደህ ፣ በደንብ አድርገህ ገርፈህ ልታመጣው ትችላለህ፣ ግን እንደኔ ውጤት ቢስ ፖለቲከኛ ከሆንክ ምንም ምርጫ የለህም ፣ እንደፈረደብህ ስታር ባክስ ሄደህ ላቴ ታዝና ላቴው ላይ ታጉረመርማለህ።
አማሪካን የሴት ልጅ እጅግ የተከበረች ነች፣ የሰላሳ ዓመት ትዳርህን በሶስት ቁጥር ባንድ ሌሊት ልታፈርሰው ትችላለች፣ መኖር ከፈለክ አርፈህ ትቀመጣለህ ፣ አለበለዚያ ዕጣ ፈንታህ የፓፒዮን ነው የሚሆነው፣ ( ማለቴ እስር ቤት ገብተህ በረሮ ስንት እግር እንዳለው ፣ በደቂቃ ምን ያህል እንደምጉዋዝ ፣ ኩራታም መሆን አለመሆኑን፣ እና ወዘተ በቂ ጊዜ ስለሚኖርህ በደንብ ትረዳለህ ። በረሮ ስል የአገሬ ስደተኛ ከሽሮና በርበሬ ቀጥሎ በህገወጥ መንገድ ወደ አማሪካ የሚያስገባው በረሮን ነው። በነገራችን ላይ ሁሉም ኢትዮጵያዊ አማሪካ እንደገባ ቀድሞ የምረሳው ነገር ቢኖር ጡር ነው የሚባለውን ነገር ነው ፣ ምክንያቱም እዚህ አገር ጡር የለም ፣ አይ አለ ብለህ ከደረቅህ ግን ሞክረው ዋጋህን ታገኛለህ ። የዚህ ሀገር ምግብ በተባለለት ጊዜ ካልተመገብከው ጡር ሳይሆን ጦር ነው የሚሆነው። የ ትራፊክ ( የመንገድ ) ስርዓቱ የሚማርክ ነው፣ ጠብቀህ ታሳልፋለህ፣ ጠብቀህ ታልፋለህ። እንዲህ እንደኔ የጋዝ ወረፋ ሲሰርቅ ላደገ ሰው በጣም አስቸጋሪ ቢሆንም ፣ “ሲስተሙ እስኪገባህ ነው አይዞህ” ብለው ያጽናኑሃል። አማሪካ ተስፋ በገፍ የሚነዛባት እና የሚቸበቸብባት ሀገር ናት ።
የታዋቂ ሰዎችን የዓመት ገቢ ኢትዮጵያ ሆነህ ከሆነ የሰማኸ ፣ በእርግጠኝነት ምን ማለት እንደሆነ እንደማይገባህ ልነግርህ እወዳለሁ። አማሪካ ካጠፋህ ትቀጣለህ ፣ የቤት ኪራይ ሲደርስ ሕጉ ወይ ከፍሎ መቀመጥ ወይ ሆም ለስ ሆኖ በብርድ መቆመጥ ነው። ምርጫው ያንተ ነው። አማሪካ፣ ከጭንቅላትህ በበለጠ ጥርስህን የምትጠቀምበት ሀገር ነው ፣ ባስነጠስክ ቁጥር ይቅርታ የምትጠይቅበት ሀገር፣ ተግባብተህ ለመኖር በምታደርገው ጥረት ሁልጊዜም ” ከየት ነው የመጣኸው? ” በሚል ጥያቄ ንግግሩን የሚጀምር ሕዝብ ያለበት ሀገር፣ አንተ በማግኘታቸው አንጀታቸው ቢያርም ” ስይስ ቱ ምት ዩ ” የሚሉበት ሀገር ። አማሪካ መንገድ ላይ መሽናት አስነዋሪ ነገር ነው፣ ከውሻ ሌላ ይህንን የሚፈጽም ብዙ ግዜ አታይም ፣ ያም ስለሆነ ” መሽናት ክልክል ነው ” የሚል ነገር ተጽፎም አታነብም፣ ካነበብክ ግን በእርግጠኝነት ዋሽንግተን ዲሲ ነው የምትኖረው ማለት ነው።
የ አማሪካ ሕዝብ በጣም በላተኛ ሕዝብ ነው፣ በላኛ ግን አይደልም ። በላ አያውቁም፣ በላ በላ ማድረግም አያውቁም፣ ስልቅጥ ማድረግ ግን ማንም አይስተካከላቸውም። ሸማ በየ ፈርጁ ይለበሳል እንዲሉ አማሪካ እንደ ሸማ ቆዳውን የተከናነበ ሰው የምታይበት፣ ትንፋሹ እስኪያጥረው ድረስ በልቶ ትንፋሹ እስኪያጥረው ድረስ የወፈረ ሰው የሚኖርባት ሀገር ነው።
ሁሉም ነገር “እኔ” ከሚለው ቃል ይጀምራል፣ ሁሉም ነገር ” ለኔ” በሚለው ቃል ይደመደማል፣ በዚህ በምኖርባት አማሪካ። አማሪካ ውሾቹ እጅግ ደስተኞች ናቸው፣ አንዳንዴ ውሻነታቸውን ያውቁ ይሆን እላለሁ። ለምሳሌ የኔው ጎረቤት አንድ ” ቡል ዶግ ” የሚባል ውሻ አለው ፣ ይሄ ውሻ ታዲያ አንገቱ ላይ በዳይመንድ ፈርጥ የተንቆጠቆጠ የፕላትንየም ያንገት አልቦ ( ወይም ድሪ)፣ ለነገሩ ምንስ ብለው ምን ዋጋ አለው ፣ ብቻ ዘናጭ ውሻ ነው። አንድ ቀን እንደውም ወደ ሥራ ለመሄድ እየጠታደፍኩ ሳለ ፣ ” ሄኒ አንድ ነገር ላስቸግርህ ባክህ አለኝ” ደሞ እንኩዋን ለውሻ ሰው ለስንቱ ይቸገር የለ ብዬ ” ምን ልታዘዝ?” አልኩት። ወዲያ ” ባክህ ላይፍ እስ ቦሪንግ ሂር; ደሞ መውለድ አልችልም ፣ እአናት ሀገር አዶብት የማረገው ውሻ ይኖር ይሆን ” ብሎኝ አረፈ። ውሻ ከሆኑ አይቀር እንዲህ ነው። ይህን ስል አሁን ስጋ በሌለበት ዘመን የተፈጠረው ያገሬ ውሻ ትዝ አለኝ። እንደውም አሁን አሁን ያገሬ ውሾች ቬጅተሪያን እንደሆኑ ሰምቻለሁ፣ ለምን አሳይለም እንደማይጠይቁ ግን በፍጹም ሊገባኝ አልቻለም። በነገራችን ላይ አንድ ኤርትራ ልክ ነጻነቱዋን እንዳወጀች አማሪካን ሀገር የመጣ ” ኤርትራዊ ” ባንድ ሬስቶራንት ምግቡን ( ሰላጣና ፓስታ) እየተመገበ ሳለ ፣ አንድ የውጭ ሀገር ሰው ” አር ዩ ቬጅተሪያን? ” በሎ ሲጠይቀው፣ “ኖኖ! አይ አም ኤርትሪያን!” ብሎ መለሰ አሉ። እውነቱን እኮ ነው ገና ከኢትዮጵያ ተላቆ ሳይጨርስ ደሞ ቬጂተሪ የምትባል አገር ” ባርያ” ሊሆን ። ምግቡ ይቀራታል እንጂ እሱ ኤርትራዊ ነው። ለዚያውም ለሰላጣ ? የፓስታውን እንኩዋ እንጃ !
ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ፣ አንድ በጣም የተራበ ጅብ ኢትዮጵያውን ለቆ በፍጥነት ወደ ኤርትራ ይገባል፣ታዲያ አፍታም ሳይቆይ በ በከፍተኛ ፍጥነት ከ ኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ ይመለሳል። እናላችሁ ድንበር ጠባቂዎቹ ነገሩ ስለገረማቸው ያስቆሙትና ” ምነው ተመለስክ አያ ጅቦ፣ ምን አጋጠመህ ?!” ሲሉት ፣ “አረ ምግብ ፍለጋ ብሄድ ሊበሉኝ” አለ አሉ ። ጎመን በጤና ማለት ታዲያ ይሄም አይደል ( ጎመኑም ጠፋ እንጂ !)። በነገራችን ላይ ትግራይን ኤርትራን ያነሳዋል እንዲሉ ፣ አቶ ኢሳይስ አፈወርቂ ዋና ሲዋኙ ሳያስቡት ተናደው ሰምጠው ሊሞቱ ሲሉ ለጥቂት ሕይወት አድን ዋናተኛ ነብሳቸውን ይታደገዋል። ትንሽ እንደተረጋጉም ይህንን ይዳናቸውን ሰው ያስጠሩና ፣ ” ስማ አንተ ለማንምኢሳያስን አዳንኩት ብለህ እንዳትናገር” ይሉታል ። በዚህ ጊዜ ታዲያ ሰውየው ቀበል አድርጎ ” አይ እርሶም እባኮ ለማንም አዳነኝ ብለው እንዳይናገሩ ” አለ አሉ ። ዘ- ይገርም ዘ-ይደንቅ አይደል ታዲያ።
እና አማሪካ ድንቅ ሀገር ነች፣ እያስደነቀች ዕድሜህን የምትሰርቅ ሀገር። አንድ ወዳጄ እንደውም አማሪካ በመጣ በ ወሩ አግኝቸው፣ ” ኑሮ እንዴት ነው ጃል ? ” ስለው ” ሄንሻ ሳልኖር ልሞት ነበር እኮ አለኝ” ። ሳይኖሩ ከመሞት አምላክ ያውጣን  ።
ተጨማሪ ያንብቡ:  “ሣንሞት መቀባበር መቼ ይሆን የሚቆመው?
Share