የሕግ አምላክ የሞተባት አገር፤ በሕገ መንግሥት ሳይሆን በወያኔ የጫካ ሕግ ለሃያ ዓመታት (ያሬድ ኃይለማርያም)

ያሬድ ኃይለማርያም

ከብራስልስ፣ ቤልጂየም

ሚያዝያ 23፣ 2006

ለከት ያጣው የወያኔ ጭካኔ እና የማይነጥፈው የሕዝብ ትእግስት ኢትዮጵያን ወዴት እየወሰዷት እንደሆነ አገሪቱ ዛሬ ያለችበት ውጥንቅጥ ሁኔታ በግላጭ ያሳያል። በመግደል አባዜ የተለከፉት የወያኔ ተጋዳላዮች ዛሬም መግደላቸውን ቀጥለዋል። ለይስሙላ በወረቀት ላይ የሰፈረው ሕገ-መንግስት እና በውስጥ የያዛቸው መሰረታዊ የሆኑ የሰብአዊ መብቶችና ነጻነቶች ለወያኔ ተጋዳላዮች ምናቸውም እንዳልሆነ በተደጋጋሚ እያሳዩን ነው። በአገሪቱ ውስጥ ያለው የሕግ ማእቀፍ (አንዳንዶቹ ሕጎች በራሳቸው የማፈኛ መሳሪያ ተደርገው የተቀረጹ መሆኑ ሳይረሳ) ለወያኔ ተጋዳላዮችና ተራ ካድሬዎች ሳይቀር ምናቸውም አይደለም። ሲሻቸው ይገድላሉ፣ ያፍናሉ፣ ይሰውራሉ፣ ባደባባይ ይደበድባሉ፣ ሺዎችን በየማጎሪያው ያሰቃያሉ፣ ያዋርዳሉ፣ ቅጥ ባጣ መልኩ ይሞስናሉ፣ ይሰርቃሉ፣ ይዘርፋሉ፣ ያስፈራራሉ፣ ሴቶችን ይደፍራሉ፣ ህዝብን ያሸብራሉ፣ ምኑ ቅጡ።

እንግዲህ የሕግ አምላኩ ሲሞት ሥርዓት አልበኝነት ይነግሳል፤ ዘራፊዎች ይበራከታሉ፣ ገዳዮች ባደባባይ ገድል ይጥላሉ፣ ሙሰኞች አገርን እና ሕዝብ ይቆጣጠራሉ፣ የአገር ሃብት ያሸሻሉ፣ በድሆች ጉሮሮ ላይ ቆመው በሃብት ይጨማለቃሉ። በዚህ ላይ ጎጠኝነት ሲታከልበት መላ ቅጡ ይጠፋል። ብዙዎቹ እየከሰሙ ያሉ አገሮች (failed states)እየተባሉ በየጊዜው የሚጠቀሱ አገሮች በእነዚህ ችግሮች ውስጥ የሚማቅቁ ናቸው። ወያኔም ለኢትዮጵያ የዋለላት አንዱ ትልቁ ነገር ከእነዚህ አገሮች ተርታ እንድትሰለፍ ማድረጉ ነው። እንደ ታላቅ ስኬት የሚቦተለክለት የዛሬዋ የኢትዮጵያ ልማት ውስጡ ሲገባ ላዩ አሮ ውስጡ ሊጥ እንደሆነ ዳቦ ስለመሆኑ ምንም ጥናትና የተለየ ምርምር ሳይጠይቅ 95% የሚሆነውን የአገሪቷን ሕዝብ ኑሮ ማየት በቂ ነው። አንጻራዊ በሆነ መልኩ በወያኔ ዘመን የመጀመሪያዎቹ አሥር አመት ውስጥ እንኳን የኢትዮጵያ ሕዝብ ያገኛቸው የነበሩትን እንደ መብራት፣ ውኃ፣ የጤና አገልግሎትና ሌሎች መሰረታዊ ፍላጎቶቹ ዛሬ ተነፍጓል። የደብል ዲጂት ልማታዊነት ነጠላ ዜማዎች በወያኔ እና ባጫፋሪዎቹ የአለም አቀፍ ‘የልማት’ ተቋማት ጆሮዋችን እሲደነቁር በሚዘፈንበት በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ አስከፊ በሆነ የኑሮ ዋስትና ማጣት ውስጥ ሆኖ የመከራ እንቆቆውን እየተጋተ ይገኛል። የእነዚህ የመሰረታዊ አቅርቦቶች በዚህ ደረጃ ላይ አቆልቁሎ መገኘት አንኳን የቀለም አብዮት፤ ሌላም መገለጫ የሌላቸው አመጾችንና እልቂትን ቢወልድና በአገሪቱን ወደ ከፋ ብጥብጥ ቢከት የሚገርም አይደለም። ይሁንና እንደ ወያኔ ያለ ክፉ፣ መረን የማያውቅ እና ጨካኝ ሥርዓት እድለኛ ሆኖ ሆደ ሰፊ፣ የማይቻለውን ሁሉ የሚችል፣ ጨዋና ታጋሽ ሕዝብ ሲጋጥመው ጭካኔውን እያበረታ፣ የአፈና ሰንሰለቱን እያጠበቀ፣ አባላቱን በአሃብት እያሞሰንነና እያጎለበተ ይንሰራፋል። የአገር መፍረስ ወይም አደጋ ላይ መወደቅ የራሳቸውን ጥቅም አደጋ ላይ እስካልጣለ ድርስ ግድ የማይሰጣቸው ጎጠኛ ፖለቲከኞችም በደሃው ሕዝብ ላይ ይሰለጥኑበታል፤ ይሰይጥኑበታልም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያና ጎሳነት (በአልማዝ አሰፋ - ዘረ ሰው)

ሰሞኑን በአገሪቱ ውስጥ የሚስተዋለው የፖለቲካ ድባብ ወያኔ ከመቼውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ አገሪቱን የሚዘውርበት መሪ ከቁጥጥሩ ውጭ እንዳይወጣ እየተውተረተረ ያለ መሆኑን ነው። ለዚህም ይመስላል ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ ባንዲራና መፈክር ይዘው በተንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት፤ በተለይም የሰማያዊ ፓርቲ አባላትን አስሮ እያሰቃየ ያለው። ለዚህም ነው በማኅበራዊ ድኅረ ገጾች በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የውይይት መነሻ ሃሳቦችን እያጫሩ ሕዝቡ እንዲወያይ ይጋብዙ የነበሩ የዞን 9 አባላትን ለቃቅሞ አጉሮ እያሰቃያቸው የሚገኘው። ይህም አልበቃ ብሎ ባለፉት ሦስት እና አራት ቀናት ውስጥ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄ (ጥያቄያቸው ምንም ይሁን ምን) እያቀረቡ ያሉ የኦሮሚኛ ቋንቋ ተናጋሪ ዩንቨርሲቲ ተማሪች ላይ የተለመደውን የጭካኔ እርምጃ እየወሰደ ያለው። ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን እንደተገለጸው ከሆነ በርካታ ተማሪዎች በታጠቁ ሃይሎች የጭካኔ እርምጃ ለከባድና ቀላል የአካል ጉዳት ተዳርገዋል። በተለይም በአንቦ ከተማ ተማሪዎች በግፍ ተገድለዋል። የወያኔ መንግሥት ሥልጣን ከያዘበት ጊዜ አንስቶ በተማሪዎች ላይ ተደጋጋሚ የጭካኔ እርምጃዎችን ወስዷል። በመላ አገሪቷ በወያኔ እርምጃዎች ከተጠቁት ተማሪዎች ውስጥ ግን ትልቁን ግፍ የተቀበሉት በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ስለመሆናቸው የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን የሚመለከቱ ሪፖርቶች ይመሰክራሉ። በሥራዬ አጋጣሚ እኔም ይህን አረጋግጫለሁ።

ዛሬ ላለንበት ጠቅላላ አገራዊ ክሽፈት፣ ውርደት እና የመከራ ሕይወት ከላይ እንደጠቀስኩት ለከት ያጣው የወያኔ ጭካኔ እና አፈና፤ እንዲሁም የአለማችን ተጭባጭ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን  የማይነጥፈው የሕዝብ ትእግስት እና ዝምታም ትልቁን አስተዋጾ አድርጓል። በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ ተማሪዎች ላይ፣ በጋዜጠኞች ላይ፣ በሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ላይ፣ በተቃዋሚ ፓርቲዎች አባላትና ደጋፊዎች ላይ፤ እንዲሁም በኃይማኖት መሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና በደል በጋራ ልናወግዘው እና ልንታገለውም ይገባል። በፍትሕ እና በኢ-ፍትሐዊነት፣ በጭቆና እና በነፃነት  መካከል ገለልተኛ ሆነው የሚንጠለጠሉበት ገመድ ወይም የሚቆዩበት ደሴት የለም። ፍትሕ ሲጓደል እያዩ እንዳላዩ መሆን በራሱ ኢ-ፍትሐዊነት ነው። መብት ሲጣስ እያዩ እንዳላዩ መምሰል በራሱ የጣሹ ግራ እጅ መሆን ነው። ንጹሃን ዜጎች በግፍ ሲገደሉ፣ ሲደበደቡ፣ ሲታሰሩ እና በሃሰት ክስ እየተፈረደባቸው በእስር ሲማቅቁ እያዩ ገለልተኛ መሆን አይቻልም። የፖለቲካ ገለልተኝነትን እና ለፍትሕ፣ ነጻነት እና ለህሊና መቆምን ባናምታታቸው ጥሩ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከሆነማ መልካም? - ከገዙ በቀለ (ዶ/ር)

 

ለፍትህና ለነፃነት በመቆም የሰውነትም፤ የዜግነትም ግዴታችንን እንወጣ!

http://humanrightsinethiopia.wordpress.com/

3 Comments

  1. ኣቶ ያሬድ፣
    ባብዛኛው እኔም እስማማለሁ በወያኔ ብቻ ሳይሆን ተለጣፌዎችም ብትጠቅሳቸው ለፍትህ ኣልባነት በሃገራችን መልካም መሰረት ይሆናል። በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተለጣፈ ድርጅቶችም እኩል ተጠያቂዎች ናቸው። በውጭ ያለው እርስ በርሱ የሚጠላለፍ፣ በመንደር በዘር ለተሰባሰበ፣ ለስልጣን ኣቃራጭ ሩጫን የሚያምረው ጭምርም ቢሆን እኩል መወቀስ ኣለበት። በስራ ልምድ፣ በትምህርት፣ በጸጋ ወዘተ ስንቶችን እንዳላደረሰች የመካን እናት ሁና፣ ስንቶችን ለእስር ተዳርገው፣ መሬት እየሸጡ፣ ሙስና እና ድህነት በልጽገው፣ ወዘተ ዛሪም ስንቶችን ገደሉ። ሰማያዊ፣ ኣንድነት፣ ዓረና ሌሎችም ኣንተም እኔም ኣንቺም በሃገርና በህዝም ኣልኝታ፣ ህግ የበላይነት እስኪረጋገጥ ድረስ ኣብረን የመስራት ባህል ማሰየት ኣለብን።
    ገብረእየሱስ

  2. Thank you wendme.Ahun yemigermew enesu “ye fiteh samint “blew Sikeldubin endet yegermal ? Oooooooooooooo ere minim efret yelelachew ooofffaaa!

Comments are closed.

Share