Health: ድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያስፈልገው በሽታ ምንድን ነው? – (ከህክምና ባለሙያ ጋር የተደረገ ውይይት)


‹‹ዕድሜዬ በ30ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ የሚገኝ ነው፡፡ የስራ ሁኔታዬ ከቢሮ ጋር የተያያዘ በመሆኑ መቀመጥ አበዛለሁ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ምክንያቱን ባላውቀውም በስራ ላይ እያለሁ በድንገት ፋታ የማይሰጥ ህመም ይሰማኛል፡፡ ከዛሬ ነገ ይሻለኛል ብዬ ብጠብቀውም ህመሙ ከመባባስ በስተቀር ይሄ ነው የሚባል መፍትሄ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ የህመሙ ፋታ አለመስጠት ስጋት ውስጥ ሲጥለኝ ወደ አንድ የጤና ተቋም በመሄድ ምርመራ አደረኩኝ፡፡ የምርመራውን ውጤት የተመለከተው ሐኪም ግን አስቸኳይ ቀዶ ህክምና ያስፈልግሻል ብሎኛል፡፡ ድንገተኛ ፋታ የማይሰጥ ህመም ድንገተኛ ቀዶ ህክምና ለሚያስፈልገው በሽታ ምልክት ይሆናል? ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚዳርጉ በሽታዎች የትኞቹ ናቸው? እነዚህ በሽታዎች ከቀዶ ህክምና ውጪ ሌላ የህክምና መፍትሄ የላቸውም?››
አለምፀሐይ ልዑል

ወ/ሮ አለምፀሐይ ያነሱት ጥያቄ መሰረታዊና በየትኛውም የጊዜ አጋጣሚ ማንኛውም ሰው የሚገጥመው ጤና ነክ ችግር ነው፡፡ በተለይም እስከ አርባ ዓመት ዕድሜ ባለው ጊዜ ውስጥ ሰዎችን ለዕድሜ ልክ ጉዳት፣ የሆስፒታል አልጋ ይዞ ለመተኛትና በመጨረሻም ለሞት የሚያደርሱ የጤና ችግሮች አሉ፡፡ እነዚህም ደግሞ ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያጋልጡ በሽታዎች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
አዲስ አበባ በሚገኘው ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል እ.ኤ.አ ከ2002 እስከ 2006 የተደረገ አንድ ጥናት እንዳመለከተው 9.991 ህሙማን አልጋ ይዘው ተኝተዋል፡፡ ከእነዚህ ህሙማን ውስጥ 71 በመቶዎቹ የቀዶ ህክም ቀጠሮ ወስደው አልጋ የሚይዙ ናቸው፡፡ 29 በመቶ የሚሆኑት ግን ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና ወደ ሆስፒታሉ የሚመጡ እንደሆነ ተረጋግጧል፡፡ ከዚህ የጥናት ውጤት ስንመለከት በቀዶ ህክምና ከሚመጡ አብዛኛው ህሙማን በመደበኛ ቀጠሮ የሚመጡ ናቸው፡፡ ጥናቱ ከሞት መጠን ጋር ሲያያዝ ግን ውጤቱ ተቃራኒውን ነው የሚያመለክተው፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የጥናቱ ዘገባ አልጋ ይዘው ከተኙ ህሙማን መካከል 694ቱ ወይም 65 በመቶዎቹ ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የመጡ ህሙማን ናቸው፡፡ ይህ የሞት መጠን ከዓለም አቀፉ ሁኔታ ጋር ሲነፃጸር የሀገራችን ከፍተኛ ብልጫ እንዳለው የጥቁር አንበሳ የአምስት ዓመቱ ሆስፒታል ተኮር ጥናት አሳይቷል፡፡ ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚደርሱ የጤና ነክ ችግሮች የትኞቹ ናቸው? ያለቅድመ ዝግጅት የሚደረግ ቀዶ ህክምና በአብዛኛው የሚመለከተው ማንን ነው? ምክንያቱስ? ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያጋልጡ በሽታዎች ሲከሰቱ የሚታዩ ምልክቶችስ የትኞቹ ናቸው? በእነዚህና ተያያዥ ጥያቄዎች ዙሪያ አንድ የጠቅላላ የቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት ሐኪም ምላሽ ሰጥተውናል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: ስንፈተ-ወሲብ መንስኤዎቹን እንዴት መለየት ይቻላል?

ዶክተር ሀ፡- መደበኛው የቀዶ ህክምና አገልግሎት ህሙማን ቀደም ብለው ሰፋ ያለ ምርመራ፣ በቂ ዝግጅት አድርገውና ቀጠሮ ወስደው ሲመጡ ነው የሚሰጣቸው፡፡ ድንገተኛ የቀዶ ህክምና የምንለው ግን ከመደበኛው የተለየ ነው፡፡ ህሙማን አጠቃላይ ህይወታቸውን በአደጋ ላይ በሚጥሉ በሽታዎች ከተያዙና ያለ ዝግጅትና ቀጠሮ የሚካሄድ መደበኛ ያልሆነ የቀዶ ህክምና አይነት ነው፡፡ ድንገተኛው የቀዶ ህክምና ለማን ነው የሚያስፈልገው የሚለው ጥያቄ ሰፊ ምላሽን የሚሻ ነው፡፡ ነገር ግን ከሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ምላሹን ለማየት እንሞክራለን፡፡
ከህፃናት ብንጀምር የልብ፣ የሰገራ መውጫና የመሳሰሉት ጤና ችግሮች ሲከሰቱ መደበኛ ባልሆነ ቀዶ ህክምና መፍትሄ ለመስጠት ጥረት ይደረጋል፡፡ በማንኛውም ሰው ላይ የቃጠሎ አደጋ ሊደርስና አደጋው የደረሰው በአፍ፣ በብልት፣ በመታጠፊያ፣ በአይን አካባቢ ከሆነና ቃጠሎው የደረሰው በህፃናት ላይ ከሆነ ቀዶ ህክምናው በፍጥነት እንዲሰራ ይደረጋል፡፡ በሌላ በኩል በአደጋም ይሁን በኢንፌክሽን፣ በዕጢና በመሳሰሉት ምክንያቶች ከፍተኛ ሊባል የሚችል የመተንፈሻ አካላት ህመም፣ የልብ ህመም፣ የህብለሰረሰርና የአጥንት መመታት ሲከሰት እንደዚሁም የደም ቧንቧዎች መስፋት አልያም የመጥበብ ሁኔታ ከተፈጠረ ድንገተኛ ቀዶ ህክምና ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ባሉ ሌሎች አካል ክፍሎች የመቀጥቀጥ (ከፍተኛ ጉዳት) ሲደርስ፣ በመኪና፣ በጥይት መመታትና በስለት የመወጋት አደጋ ከተፈጠረ ህሙማኑ በህይወትና በሞት መካከል ትግል ገጥመው የሚመጡ ስለሆነ በፍጥነት የቀዶ ህክምና ተደርጎላቸው መፍትሄ (ፋታ) እንዲያገኙ መደረግ ይኖርበታል፡፡

ጥያቄ፡- አንተነህ የተባለ አንባቢ ዕድሜው 29 ነው፡፡ ባለትዳርና የአንድ ልጅ አባት ነው፡፡ ‹‹የትርፍ አንጀት አለብህ ተብያለሁ በድንገት ቀዶ ህክምና ካላደረግክ ሐኪሞች ትሞታለህ ብለውኛል›› ይላል፡፡ ከአደጋዎች በተጨማሪ ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያጋልጡ በሽታዎች ካሉ ዋና ዋና የሚሏቸውን ብናያቸው፡፡
ዶክተር ሀ፡- መደበኛ ያልሆነ የቀዶ ህክምና የሚያስፈልጋቸው ውስጣዊ ህመሞች ስንል ሀይለኛና በፍጥነት ከቁጥጥር ውጪ የሚወጡ ማለቴ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ህመሞች በተለይ የሚከሰቱት በጨጓራ፣ በቆሽት፣ በሐሞት ቀረጢት፣ በትንሹ እና ትልቁ አንጀት አካባቢ የሚከሰት ነው፡፡ ለህመሞቹ መከሰት የየራሳቸው መንስኤ እንዳላቸው ይታመናል፡፡ በድንገተኛ ቀዶ ህክምና ለመጋለጥ የሚያስችሉ መንስኤዎች የሚከተሉት ዋና ዋና የሚባሉት ናቸው፡፡
– የቆሽት ኢንፌክሽን
– ከማህፀን ውጭ እርግዝና ሲፈጠር፣ የኦቫሪ መጠምዘዝ፣ ኦቫሪ ውሃ ሲቋጥርና ሲፈነዳ እንዲሁም የማህፀን ቱቦ ኢንፌክሽን ሲከሰት ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና ያጋልጣል፡፡
– የትንሹም ሆነ ትልቁ አንጀት መዘጋት
– የጨጓራ በአንድ በኩል መቀደድና መድማት
– የሐሞት ከረጢት ኢንፌክሽን
– የትርፍ አንጀት ኢንፌክሽን በተለይም የመቀደድ ችግር ከተፈጠረ
– የአንዱ የአንጀት ክፍል ግድግዳ እንደ ከረጢት ወጣ ሲል በተጨማሪም በኢንፌክሽንና በሌሎች ምክንያቶች ሲጠቃ
– የአንጀት መታጠፍ ወይም መጠማዘዝ ሲፈጠር ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና ይዳርጋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  Health: በኢትዮጵያ ቪያግራ ገበያ ደርቷል፤ * የቪያግራ ተጠቃሚዎች ሊያውቁት የሚገቡ እውነታዎችና ጥንቃቄዎች

ጥያቄ፡- ቀደም ሲል ወ/ሮ አለምፀሐይ የተባሉ አንባቢ ‹‹ድንገተኛና ፋታ የማይሰጥ ህመም ድንገተኛ ቀዶ ህክምና ለሚያስፈልገው በሽታ ምልክት ሊሆን ይችላል ወይ?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ዶክተር ሀ፡- ጠያቂዋ እንዳሉት ፋታ የማይሰጥ ህመም ለቀዶ ህክምና የሚዳርግን ህመም ጠቋሚ ምልክት የሚሆንበት አጋጣሚ አለ፡፡ ነገር ግን አጣዳፊ ህመም ብቻ ነው ከመደበኛ ውጭ የቀዶ ህክምና ለመፈፀም የሚያስገድደው፡፡ ፋታ የማይሰጥ ህመም ነው ማለት እንዳልሆነ መገንዘቡ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በርካታ ምልክቶች አሉ፤ ለድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያደርስ የጤና ችግር መከሰቱን ከሚጠቁሙ ምልክቶች መካከል የሆድ ህመም ቀዳሚው ነው፡፡ ህመሙ ድንገተኛ ሊሆን ይችላል አሊያም ደግሞ ቀስ ብሎ የሚመጣ ይሆናል፡፡ ማንኛውም የሆድ ህመም በድንገት ተከስቶ ከስድስት ሰዓት በላይ ከቆየ ድንገተኛ የቀዶ ህክምና የሚያስፈልገው የጤና ችግር ሆድ ውስጥ መከሰቱን ይጠቁማል፡፡ በሌላ ገጽ ደግሞ ከስድስት ሰዓት በታች ቆይቶ የሚተው ህመም ከሆነ ቀዶ ህክምና የሚያስፈልገው በሽታ ሊሆን እንደሚችል መገንዘብ አስፈላጊ ነው፡፡

ጥያቄ፡- የጤና ችግሩ የት አካባቢ እንደተከሰተ የሚጠቁሙ ህመም ነክ ምልክቶች ይኖሩ ይሆን?
ዶክተር ሀ፡- ይኖራሉ! ህመሙ ቁርጠት ከሆነና በተወሰኑ ደቂቃዎች እየተመላለሰ የሚመጣ ከሆነ የአንጀት መታጠፍ ምልክት ይሆናል፡፡ ይሁን እንጂ በጊዜው ይታይ የነበረው የቁርጠት ህመም ከተቀየረ የአንጀት መታጠፍ ችግር ከፍ ያለ ደረጃ መድረሱን ወይም ደግሞ አንጀቱ መታመሙን ይጠቁማል፡፡ ሌሎች ችግር ጠቋሚ ህመሞችን ደግሞ በተወሰነ መልኩ ዘርዘር አድርገን ብንመለከታቸው ለጋራ ግንዛቤ ይጠቅማል፡፡
– ህመሙ ድንገተኛ የመውጋት ስሜት ያለው ከሆነ ወይም ህመምተኛውን በድንገት ከእንቅልፍ የሚቀሰቅስ ህመም ከሆነ ጨጓራን ጨምሮ በሆድ ውስጥ የሚገኝ የተለያዩ ቱቦዎች መፈንዳታቸውን ይጠቁማል፡፡
– ህመሙ ከእንበርት በታች ከሆነ ከማህፀን ጋር የተያያዙ ችግሮች መከሰታቸውን ያመለክታል፡፡
– የትንሹ አንጀት መጥበብ ካለ
– ጋዝም ሆነ ሰገራ አልወጣ ካለ እንዲሁም ቁርጠትና ትውከት ከተቀላቀለበት የትልቁ አንጀት በሆነ ምክንያት መዘጋቱን (መታጠፉን ያሳያል)
– በህፃናት ላይ አንዱ አንጀት ወደ ሌላው ሲገባ
– የሆድ መነፋትና የቀዶ ህክምና ታሪክ ያለው ከሆነ
– በሆዳችን (በንፍፊት) አካባቢ የፊኛ መሳሳት ሲከሰት የሆድ ውስጥ ዕቃዎች ይወጣሉ፡፡ ይህም ምክንያት የአንጀት መነፋፋት መከሰቱን ያመለክታል፡፡
– የትንሹ አንጀት መጥበብ ሲኖር
– ሰገራ አልወጣ ካለ ለአንጀት መታጠፍ ምልክት ይሆናል
– ዕጢዎች ሲፈጠሩ
– የመወጠር፣ የማንቆራጠጥና ህመሙ የመመላለስ ባህሪይ ካለው ኩላሊትና ከኩላሊት በታች ያለው ቱቦ ውስጥ ጠጠር መከሰቱን ያመለክታል፡፡
– በደረታችን (በሆዳችን) ውስጥ ድንገት የመቀደድ ስሜት ከተሰማን አንጀት መፈንዳቱን ይጠቁማል፡፡
– ቦታው የማይቀያየር ህመም የሚሰማን ከሆነ እና ቦታው በቀኝ በኩል ከሆነ ትርፍ አንጀት የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡
– የአንጀት ለአንጀት መጣበቅና ክር መሰል ነገር አንጀቱን ሲያንቀው
– ማንኛውም ህመም ማስመለስ ቀጥሎ ከሶስት እስከ አራት ሰዓት በኋላ ከመጣ ትርፍ አንጀትን ያመለክታል፡፡ ነገር ግን ከህመሙ በፊት በቀጥታ ትውከቱ ከጀመረ ምልክትነቱ ለተቅማጥ በሽታዎች ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለብዙዎች ፈውስ እየሆነ ያለ አስደናቂ አገር በቀል የህክምና ጥበብ | ንድራ

ጥያቄ፡- የድረ-ገፅ መረጃዎችን ሳገላብጥ ድንገተኛ ቀዶ ህክምና የሚያስፈልጋቸው ነገር ግን ከምልክታቸው አንፃር ሲታዩ ድንገተኛ ቀዶ ህክምና ከማያስፈልጋቸው በሽታዎች ጋር ተመሳሳይነት ያላቸው በሽታዎች እንዳሉ ነው የተገነዘብኩት፡፡ በዚህ ረገድ ተጠቃሽ ከሆኑ ህመሞች ዋና ዋና የሚባሉትን ማየት ብንልችል?
ዶክተር ሀ፡- አንተ እንዳልከው በርካታ በሽታዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ደም ማነስ፣ አይናችንን ቢጫ የሚያደርግ በሽታ፣ ተቅማጥ፣ የደም በሽታዎች፣ የሣንባ ምች፣ አድሪናል ኢንፌክሽን፣ የልብ ጤና ችግርና ቶንሲል ዋና ዋና ተብለው የሚጠቀሱ የጤና ችግሮች ናቸው፡፡

ጥያቄ፡- ድንገተኛ ቀዶ ህክምና ያስፈልጋቸዋል የሚባሉ ህመሞች ሌላ የህክምና መፍትሄ የላቸውም?
ዶክተር ሀ፡- ህመሞቹ በባህሪያቸው አጣዳፊና በፍጥነት ቀዶ ህክምና ተደርጎ ችግሩን ማስወገድ ካልተቻለ የመጨረሻ ውጤቱ ሞት እንደሆነ ግልፅ ከሆነ ቆይቷል፡፡ በዚህም ሳቢያ አጣዳፊ የሚባሉ ህመሞችን በአግባቡና ጊዜ ወስዶ በማየት የመጀመሪያው መፍትሄ በቀዶ ህክምና ለችግሩ መፍትሄ መስጠት ከአስፈላጊም በላይ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ አጣዳፊም ሆነው ቶሎ ከተደረሰላቸው በህክምና መድሃኒትም መፍትሄ መስጠት የሚቻልባቸው ሁኔታዎች አሉ፡፡ ከሁሉም በላይ ለማንኛውም ሰው መፍትሄ የሚሆነው የራስን ጤንነት መጠበቅ (መከላከል) ነው፡፡ ራስን ከአደጋ መጠበቅ፣ የአመጋገብና የአኗኗር ዘይቤን በማስተካከል አጠቃላይ የጤና ሁኔታን ማሻሻል እንደሚቻል መረዳት ጠቀሜታው ጉልህ ነው፡፡

Share