አሳማ ቢን ላደን ማን ነው?

(ከዳን ኤል ገዛኸኝ) የኒውዮርኩ መንትያ ህንጻዎች የሽብር ጥቃት ጠንሳሽ (ማስተር ማይንድ) ኦሳማ መሃመድ ቢን ላዲን በእለተ ሰንበት እሁድ ሌሊት ነው ከፓኪስታን ዋና ከተማ አቦታባድ በ61 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትጘኘው የምቾት ከተማ ሜይ 1 ቀን 2011 ዓ.ም መገደሉ በአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማ የተገለጠው።

ለመሆኑ ኦሳማ ቢን ላደን ማነው?

ከደቡባዊቷ የየመን ከተማ ሃድራሞት በመነሳት ነበረ አንድ ህይወቱን በድህነት የሚመራ ሰው ወደ ሳኡዲ አረቢያ የተሻገረው። ጊዜው በ1930 ነበር። ያ ሰው ህይወቱን በሳኡዲ አረቢያ ጅዳ የወደብ ከተማ በማድረግ ኑሮውንም በግንባታ የቀን ሰራተኝነት መምራት ያዘ። ያንን የግንባታ የጉልበት ስራ መተዳደሪያው አድርጎ በመያዝም ሞያው የሚጠይቀውን እውቀት እየቀሰመ ቆየ። ከብዙ ጥረት በሁዋላ ያ ሰው የተዋጣለት የኮንስትራክሽን ባለሞያ ከመሆንም አልፎ የራሱ ድርጅት በማቁዋቁዋም የህንጻ ተቁዋራጭ ሆነ።

በተለይም ወደ ባለሃብትነት በተሸጋገረበት የሳኡዲ አስተዳዳሪ በነበረው የንጉስ ሳኡድ የአገዛዝ ዘመን ለንጉሳዊው ቤተሰብ የቅርብ ሰው ለመሆንም ቻለ። እናም ንጉሱ ቤተመንግስታቸውን ለማሳነጽ ሲነሱ የኮንትራቱን ስራ ሙሉለሙሉ በመረከብ ስራውን በብቃት ተወጣ። ባቀረበውም ዝቅተኛ የንጉሱን ካዝና በማይጎዳው የኮንትራት ክፍያ ንጉሱ በጣም ሊረካ ቻለ። ንጉሱም ሆነ ቤተሰቡ በዚህ ተቁዋራጭ እምነታቸውን ጣሉ። በዚህ አላበቃም ከንጉስ ሳኡድ በሌላ ጽንፍ ካለው የንጉስ ፋይሳል ወገንም ቢሆን ጥሩ የሚባል ግንኙነት መፍጠር የቻለው ይኽው የተቁዋራጭ ድርጅት ሁለቱ ንጉሳውያን ቡድኖች ወደጦርነት ሲገቡ የተቁዋራጩ ሰው ሚናውን ለይቶ ለንጉስ ሳኡድ መውደቅ ለንጉስ ፈይሳል የሱዲን አስተዳዳሪነት ስልጣን መጨበጥ አይነተኛ ሚና መጫወቱ ይነገራል።

የዚህ ዝነኛ ተቁዋራጭ ባለቤት የኦሳማ መሃመድ ቢን ላዲን አባት መሃመድ አዋድ ኦሳማ ቢን ላዲን ነበሩ። እናም ንጉስ ፈይሳል ስልጣን ሲቆናጠጡ ምንም እንኳን መንግስታቸው በካዝናው በቂ ሃብት ባይኖርም በሃገሪትዋ በሚገነቡ የግንባታ ስራዎች ውስጥ የሃገሪቱ ዜጎች በአነስተኛ ክፍያ የስራ እድል እንዲያገኙ በማድረግ መንግስቱ የህዝብ ድጋፍ እንዲያገኝ ሚናው ከፍተኛ ሲሆን….የሳኡዲም መንግስት በሃገሪቱ የሚካሄዱ ግንባታዎችን አብዛኛውን ለኦሳማ ቢን ላዲን አባት ለመሃመድ አዋድ ቢን ላዲን ሰጠ።

በሳኡዲ አረቢያ ንጉስ ፈይሳል መልካም ፈቃድም የሃገሪቱ የስራ ሚኒስትር በመሆን ሹመት ተቀበለ።በማስከተልም በ1969 ከደረሰበት የእሳት አደጋ በሁዋላ በድጋሚ የታነጸውና ሙስሊሞች በተለየ አይን የሚያዩትን የአል-አቅሳ መስጊድን አነጹ። ቀጥሎም መካ መዲና የሚገኘውን ታላቁን መስጊድ በማነጻቸው የቢንላዲን ቤተሰብ በአለም በሚገኙ ሙስሊሞች ዘንድ ከፍተኛ ትኩረት እና አድናቆትን አተረፉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአማራና አፋር ክልል ሕወሓት ሽንፈት እንደደረሰበትና ውጊያውን መቋቋም እንዳቃተው ዶ/ር ደብረጺዮን በቁጣ ተናገሩ

ሃያሁለት ጊዜ ያገቡት የኦሳማ ቢን ላደን አባት ከሃምሳ ሁለት ልጆቻቸው መካከል መሃመድ ኦሳማ ቢን ላደን ሰባተኛው ልጃቸው ሲሆን ከአስረኛ ሚስታቸው ከሶሪያዊቷ ሃሚዳ የተወለደው ኦሳማ ለእናቱ ብቸኛው ወንድ ልጃቸው ነው። ይሁንና ኦስማ የአስራ ሶስት አመት ልጅ ሳለ አባቱ መሃመድ አዋድ ቢን ላደን በሂሊኮፕተር ድንገተኛ አደጋ ከዚህ አለም በሞት ተለዩ።

መሃመድ ኦሳማ ቢን ላደን በሳኡዲ አረቢያ ሪያድ ከተማ ማርች 10 ቀን 1958 ተወለደ። ይሁንና ገና እንደተወለደ አባት እና እናቱ በመለያየታቸው ሳቢያ እናቱ ቢን ላደን ግሩፕ በተሰኘው የአባቱ ኩባንያ ውስጥ ይሰራ የነበረ መሃመድ አል-አታስ የሚባል ሰው በማግባትዋ ሳቢያ ከሶስት እህትና ወንድሞቹ ጋር በእንጀራ አባት ቤት ለማደግ እንደተገደደ ነው አሳምሮ እንደሚያውቀው የሚናገረው የ አል-መዲና ጋዜጣ አዘጋጅ ካልድ ኤም ባታሪፍ ምስክርነቱን ሰጥቷል።

ኦሳማ ገና ተማሪ ሳለ ከሚከታተለው መደበኛ ትምህርቱ ባሻገር የሙስሊም ወንድማማቾች አባል በመሆኑ የተነሳ ኢስላማዊ ሃይማኖት ርዕዮተ-አለም እና ፖለቲካንም ያጠና እንደነበረ የቅርብ ጉዋደኛው ጀማል ከሊፋ ያስረዳል።

ኦሳማ ከትምህርት አለም በሁዋላ በወጣትነት ዘመኑ የመካከለኛው ምስራቅ አረብ ፔኒንዙዌላ ሃገራትን በተለይም ሶሪያን ተመላልሶባታል። እንደዚሁም ፓኪስታን፣ አፍጋኒስታን፣ ሱዳንን ተዘዋውሮባቸዋል። በአጠቃላይ በስዊዘርላንድ፣ በፊሊፕንስ፣ በለንደን በመመላለስ ህይወቱን አሳልፏል። ለዚህም ይመስላል እንደ አዳም ሮብንሰን ታዋቂ የታሪክ ጸሃፊ አገላለጽ ቢንላደን ሲበዛ የአርሰናል እግር ኳስ ክለብ ደጋፊ መሆኑን የሚናገርለት። ጸሃፊው አዳም በማስከተልም በ1994 ቢን ላደን በሎንዶን ተገኝቶ የአርሰናልን ሁለት ምርጥ ጨዋታዎች መከታተሉን እማኝ ጠቅሶም ይናገራል።

የትዳር ህይወቱም ሲዳሰስ በተለያዩ ጊዜያቶች ከተለያዩ ሴቶች ጋር ትዳር መስርቶዋል። የመጀመሪያ ሚስቱ የእናቱ የእህት ልጅ የሆነችዋን ሶሪያዊትዋን ነጅዋ ጋነምን መርጦ በአስራ ሰባት አመቱ በ1960 አገባ። በአጠቃላይ ሚስቶቹ አራት እንደሚደርሱ የሚናገሩት የሱዳን የቀድሞ አፈ-ጉባኤ ዶክተር ሃሰን አል-ቱራቢ ባለቤት ሚሥስ ዌልሳ አል-ቱራቢ ሲሆኑ “በተለይ” ይላሉ……”በተለይ ሶስቱ ሚስቶቹ እስከ ዩኒቨርስቲ የዘለቀ ትምህርት የተከታተሉ በዲግሪ የተመረቁ መሆናቸውን አስታውሰው እነዚህን ሴቶች ቢን ላዲን ለምን እንዳገባቸው የተናገረበትን ምክንያትም ሲያስታውሱ ምን አልባት የሚያገባቸው ወንድ ሳያገኙ እንዳይቀሩ ይሆናል ሲሉ ግምታቸውን ይናገራሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በእውነት ስለ እውነት ከተነጋገርን ..! ከሁሉም በፊት

ኦሳማ በአብዛኛው የሚታወቁ መረጃዎች ሚስቶቹ አራት መሆናቸውን በስፋት ሲዘግቡ አምስት ሚስቶች እንዳሉትም ደግሞ ይታመናል። በሌላ በኩል በጠቅላላ ሃያ ልጆች እንደወለደም አንዳንድ ጸሃፊዎች ያስረዳሉ። ከመጀመሪያዋ ሚስቱ ነጅዋ ጋነም አስራ አንድ…..ከሁለተኛዋ ሚስቱ ከዲጃ ሸሪፍ ሶስት….ከሶስተኛዋ ሚስቱ ኬሪያ ሳብር አንድ…..ከአራተኛዋ ሚስቱ ሲሃም ሳብር አራት……ከመጨረሻዋ እና አምስተኛዋ ሚስቱ አመል አል-ሳዲህ ደግሞ አንድ ልጅ ወልዶዋል። ይሁን እና ከሴፕቴምበር 11 2001 በሁዋላ ግን ልጆቹ በሙሉ ወደ ኢራን መጓዛቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ይሁን እና ከልጆቹ መሃከል በተለይ አብዱላህ ቢን ላደን…ሳኡድ ቢን ላደን….ኦማር ቢን ላደን…..ሃምዛ ቢን ላደን ከአባታቸው ፍላጎት እና ሃሳብ ጋር የተቆራኘ ፍላጎት እንዳላቸው ሲነገር በሽብር ተግባር ፈጸሙት የሚባል የጎላ ታሪክ ግን የላቸውም።

በተለያዩ ጊዜያቶች የሳይኮሎጂ ምሁራኖች በኦሳማ ቢን ላዲን ህይወት ዙሪያ ተጨባጭ መረጃዎችን ለማግኘት ጥረት ቢያደርጉም የተሳካላቸው ጥቂት ነገሮቹ ናቸው። ከዚያ ውስጥም በተለይ ከአረባዊው ጋዜጣ ጋር በብዙ ቅድመ-ሁኔታ የታጠረ ቃል-ምልልስ ያደረገችውና ራስዋን ለመደበቅ ስትል ኤስ በሚል መጠሪያ ራሷን የደበቀችው የቀድሞ ሚስቱ ስትናገር “ብዙ ጊዜ በሌሊት አምሽቶ ወደቤት ይመጣል ከዚያም ሰው እንዲያነጋግረው አይፈልግም….ለብቻው ጥቂት ይጋደማል ቀሪውን ሌሊት ለብቻው ሆኖ ሲያስብ እና ሲያሰላስል ይቆያል….እንቅልፍ የለውም እንቅልፍ ለማግኘት ብዙ ይሰቃያል…..ካልሆነም እንቅልፍ እንዲወስደው የእንቅልፍ ኪኒን ይወስዳል….ያም ቢሆን አይሳካለትም። በተረፈ በአፍጋኒስታን ካንደሃር ውስጥ ሁለት ሚስቶች…ካቡል አንድ ሚስት እንደዚሁም ቶራቦራ ተራራ ዋሻ ውስጥም አንድ ሚስት እንዳለችው አውቃለሁ። ከምግብ እርጎ እና ዳቦ ማር ያዘወትራል…..በህይወቱ ውስጥ የተጸናወተው የእንቅልፍ ማጥት እና የኩላሊት ህመም በስተመጨረሻ ለአካላዊ መዳከም አድርሶት ነበረ” በማለት የምታውቀውን ለአልመጀላ ጋዜጠኛ አጫውታለች።

ኦሳማ ቢን ላደን በህይወቱ የቀሰመው ሃይማኖታዊ ርዕዮት ሙስሊም ያልሆኑትን ሁሉ ለመግደል ሲዝት እና እሱ እንደሚለው ግን በርካታ ሙስሊሞች ቢቃወሙትም ከቅርብ ጉዋደኛው የግብጹ ኮማንዶ ዶክተር አይመን አል-ዘዋሂሪ ጋር በመሆን THE INTERNATIONAL ISLAMIC FRONT FOR JIHAD AGAINST JEWS AND CRUSADERS የሚል ቡድን አቋቁሞ ሲንቀሳቀስ የምዕራቡ አለም ሚዲያዎች እና ዘጋቢዎች ምንም ትኩረት አልሰጡትም ነበረ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በኢትዮዽያ ‹‹ግብረ ሰዶማዊነት›› ስር ሰዷል - (ከዳንኤል ክብረት)

የቀድሞዋ ሶቭየት ህብረት በ 1979 አፍጋኒስታን ላይ ያደረገችው ወረራ የኦሳማን ታሪክ ለወጠው።

ከሙስሊም ወንድሞቹ ጋር በሚያንቀሳቅሱት ድርጅት የሚያካሂዱት ዘመቻ ያልጣማት ሳውዲ ካገር ካባረረችው በኋላ ብቸኛ መጠጊያ ያደረጋት ሱዳን የነበረች ሲሆን እንቅስቃሴው ያልጣማት አሜሪካ በጀመረችው ጸረ-ኦሳማ ዘመቻ ሳቢያ ካገርዋ እንዲወጣ ሱዳን ከማስገደዷ በፊት የሳኡዲ መንግስት በተለይ ደግሞ አጎቱ ለስድስት ጊዜ ያህል ወደ ሱዳን በመመላለስ ወደሃገሩ ተመልሶ ቢዝነሱን እንዲቀጥልና ወደ ሰላማዊው ህይወቱ እንዲመለስ ብታስለምነውም በጅ ባለማለቱ የተነሳ ሳኡዲ ዜግነቱን እንደሰረዘች አበሰረች።

ቢን ላደንም ከሱዳን በመውጣት ሶማሊያ እና ፓኪስታንን ቤቱ አድርጎዋቸው ቆየ። በዚህ ወቅት አስገራሚ ነገርም ተከስቷል። ኦሳማን አይን ውስጥ የከተተቸው አሜሪካ በቀዝቃዛው ጦርነት ከሶቭየት ህብረት ጋር በነበራት ቅራኔ ሳቢያ አስበውት ይሁን ሳያስቡት ኦሳማ እና አሜሪካ በአንድ አላማ ላይ ተገናኙ። ዓላማውም በሶቭየት ህብረት ለተወረረችው አፍጋኒስታን ድጋፍ በመስጠት ነበር። ይሁንና በዚያን ጊዜ ቢን ላደን ወደ አፍጋኒስታን የተጉዋዘው ለሙጃሃዲኖች በገንዘቡ የሎጀስቲክ ድጋፍ ለማድረግ የነበረ ሲሆን ከተለያዩ ሙስሊም ሃገራት ድጋፉን አሰባስቦ ሙጅሃዲኖች አፍጋኒስታናውያን ሶቭየትን በአይቀጡ ቅጣት ከድንበራቸው እንዲያባርሩ ታላቁን ሚና ተጫወተ።

ከዚህ ጊዜ በሁዋላ ነበረ በቢን ላደን የሚመራው አል-ቃይዳ የአሜሪካና የምዕራባውያን አገሮች ሃይላት ላይ ፊቱን በማዞር በይፋ ጦርነት ያወጀው። እናም እንደ ሳኡዲ አረቢያው የ 1995 እና በአፍጋኒስታን የቢን ላዲን ቡድን ሃላፊነቱን ያልወሰደበት ግን የሱ ጥቃት እንደሆነ የተነገረለትን የ1996 ከባድ ጥቃት ተፈጸመ። ከዚያም በኬንያና በታንዛኒያ የአሜሪካ ኤምባሲዎች ላይ ጥቃት ፈጸመ። በኢንዶኔዥያ ቫሊ ጥቃት የየመኑ የመርከብ ላይ ፍንዳታ ሁሉ በኦሳማ ቢን ላደን መሪነት ተፈጸሙ የተባሉ ዋና ዋና ዎቹ ጥቃቶች ናቸው። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ አሜሪካ በቁጥር አንድ አሸባሪነት ኦሳማን ስትፈልጋው ኖራ እንደገና በመስከረም 11/2001 የኒውዮርኮቹ መንትያ ህንጻዎች እና የፔትታጎኑ ጥቃት በቢን ላደን ጠንሳሽነት ተፈጸመ። አሜሪካም ስታድነው ከርማ ባለፈው ሜይ 1 ቀን 2011 ኦሳማ ቢን ላደን በ53 ዓመቱ በአሜሪካ ባህር ሃይል አልሞ ተኳሾች መገደሉ ተነገረ። የኦሳማ ታሪክም አበቃ!

(Daniel Gezahegn, Admas Radio, Atlanta)

Share