ላለፉት ሁለት ዓመታት ገደማ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን ሲሰሩ የቆዩት አቶ ታዬ ደንደአ ታሰሩ

የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ የነበረዉ ታዬ ደንደአ በህግ ቁጥጥር ሥር ዋለ

ታህሣሥ 2/2016 (አዲስ ዋልታ) የፀጥታና ደኀንነት የጋራ ግብረ ኃይል ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን በላከዉ መግለጫ እንዳስታወቀዉ፤ በህግ ቁጥጥር ስር የዋለዉ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ የነበረዉ ታዬ ደንደአ ከለውጡ በፊት የኦነግ አባል የነበረና በእስር ቤት የቆየ ሲሆን፤ የለውጡ መንግስት ባደረገለት ምህረት ከማረሚያ ቤት ተለቆ በተሰጠዉ እድል በተለያዩ የክልል እና የፌደራል መንግስት የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ሲሰራ ነበር ብሏል።

ይሁን እንጂ ታዬ ደንደአ ከህዝብና ከመንግስት የተሰጠዉን ኃላፊነት በተለይም ደግሞ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ሆኖ ሰላምን ለማስፈን መሥራት ሲገባዉ፤ በተቃራኒዉ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከሚንቀሳቀሱ ፀረ-ሰላም ኃይሎች ጋር በመተሳሰር ለጥፋት ተልዕኮ በህቡዕ ሲሰራ ተደርሶበታል ብሏል መግለጫዉ።

መግለጫዉ አያይዞም በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች በንፁሃን ዜጎች ላይ ሲፈፀሙ በነበሩ የሽብር ተግባራት በተለይም ደግሞ ከእገታ ጋር በተያያዘ እጁ እንዳለበት የተደረሰበት መሆኑን አስታዉቋል።

ይህንን እኩይ ዓላማ ሲያራምድ የነበረዉ ተጠርጣሪ ታዬ ደንደአ፤ በመንግስት ቁጥጥር ስር ሊዉል እንደሚችል ሲገምት ታጋይ ለመምሰል በራሱና በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገጾች አፍራሽና ፀረ ሰላም ፅሁፎችን፣ ንግግሮችንና መግለጫዎችን በማን አለብኝነት ሲያስተላልፍና ሲሰጥ ቢቆይም ከተጠያቂነት ማምለጥ ባለመቻሉ በጋራ ግብረ ኃይሉ በቁጥጥር ስር መዋሉን መግለጫዉ አመልክቷል።

በተጨማሪም የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መግለጫ እንደገለፀዉ፥ ታዬ ደንደአ መንግስታዊ ኃላፊነቱን ተቀብሎ እየሰራ በነበረበት ወቅት መንግስታዊና የፓርቲ መዋቅሩን በሴራ ለመናድ በህቡዕ እንቅስቃሴ ሲያደርግ መቆየቱን በመረዳት ያላሰለሰ ጥናትና ክትትል ሲደረግበት ነበር ብሏል፡፡

በተደረገው ክትትልም ታዬ ደንደአ ከኦነግ ሸኔ አመራሮችና በሽብር ወንጀል ከተጠረጠሩ ጽንፈኛ ኃይሎች ጋር ትስስር በመፍጠር መንግስትን በአመጽ፣ በሽብርና፣ በትጥቅ ትግል ለመጣል ሲያሴር እንደ ተደረሰበት መግለጫዉ ጠቁሟል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሀጂ ሙፍቲ መልእክት

ተጠርጣሪዉ ታዬ ደንደአ በህግ ቁጥጥር ሥር በዋለበት ወቅትም በመኖሪያ ቤቱ ዉስጥ በተደረገ ፍተሻ፤ ግለሰቡ በህቡዕ ለሚያደርገዉ ፀረ-ሰላም እንቅስቃሴ ሲገለገልባቸዉ የነበሩ የተለያዩ 9 ሞባይሎች፣ 4 ላፕቶፖች፣ 3 አይፖዶች፣ በርካታ ፍላሾች፣ 4 የተለያዩ ተሸከርካሪ ሰሌዳዎች እና ልዩ ልዩ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች፣ ክላሽንኮቭ ጠመንጃና ሽጉጦች ከመሰል ጥይቶች ጋር እንዲሁም የኦነግ ሸኔ አርማዎችና በተለያዩ ግለሰቦች ስም የተዘጋጁ የኦነግ ሸኔ መታወቂያዎች፣ ሰነዶችና ማስታወሻዎች እንደተገኙ ግብረ-ኃይሉ በላከው መግለጫ አረጋግጧል፡፡

ከዚህም ባሻገር በብርበራ ወቅት በመኖሪያ ቤት ውስጥ በሶስት መታወቂያዎች የሚጠቀም አንድ የኦነግ ሸኔ አባል ተደብቆ መገኘቱንና በቁጥጥር ሥር መዋሉንም መግለጫዉ ጨምሮ ገልጿል።

ታዬ ደንደአ በተመደበበት ከፍተኛ የመንግስት ስልጣን ላይ ሆነ በተደጋጋሚ መንግስትን ገዳይና ጨፍጫፊ እያለ ሲወቅስ የሚደመጥ ቢሆንም፤ በተግባር ግን ከሽብርተኞች፣ ጽንፈኛችና ነፍሰ ገዳዮች ጋር የጥፋት ትስስር የነበረው ራሱ መሆኑ በተደረገ ክትትል መረጋገጡን የጋራ ግብረ ኃይሉ መግለጫ ጠቁሟል።

በመጨረሻም በመንግስትና በፖርቲ መዋቅር ዉስጥ ሆነዉ በተመሳሳይ እኩይ ዓላማ በተሰማሩ አካላት ላይ በጥናት የተመሰረተ ጥብቅ ክትትል የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል እያደረገባቸዉ እንደሚገኝና እንደአስፈላጊነቱ የሚወሰዱ ህጋዊ እርምጃዎችን በተከታታይ ለህዝብ ይፋ የሚያደርግ መሆኑን መግለጫዉ አስታዉቋል።

የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል

ታህሳስ 2/2016 ዓ.ም

 

5 Comments

  1. ጠ/ሚሩ በነካ እጅ ፕሬዝደንት ሣህለ ወርቅንም ያባራት። ያው እውነት የሚናገሩ ሰዎች እንደማይፈልግ ያኔም አሁንም ያየነው ነው። አሁን ታዬን ማሰሩና የኦነግ ባንዲራ ገለ መሌ ቤቱ ተገኘ ማለቱ ሊበሏት የፈለጓትን አሞራ ጅግራ ናት ይሏታል አይነት ነገር ነው። ሲጀመር የኦነግ ባንዲራ በቤትም ሆነ በውጭም ይዞ መገኘት ወንጀል አይደለም። የኦነግና የኦሮሞ ጠባብ ብሄርተኞች በሽታ እኛ ብቻ ለእኛ ብቻ ማለታቸው እንጂ ባንዲራው ማውለብለባቸው አይደለም። አቶ ታዬ በወያኔ ሃበሳውን የቆጠረ ይኸው ወስላታው የሃበሻ ፓለቲካ አዙሪት ውስጥ ገብቶ አሁን ደግሞ ራሱንና ቤተሰቡን ለዳግም መከራ ዳርጓል። ያኔ ለጠ/ሚሩ ሲዘፈንለት፤ ሰው ሁሉ እንደ ፈጣሪ ሲሰግድለት ተው የሃገሪቱ ችግር ጅምሩ ሳይሆን የሚከፋው መሃሉ ላይ እና ፍጻሜው ነው ብዬ ነበር። ግን ሰሚ የለም። ዝም ብሎ መንጋጋት፤ በስሜትና በቃላት ነጎድጓድ መነዳት ያኔም ያለ አሁንም የሚደርግ በመሆኑ ጠ/ሚሩን ከፈጣሪ እንደመጡ አድርገው ጣኦት ያደረጓቸው ያኔም አሁንም አሉ። እነዚህ ሰዎች የሰው መከራ የማይሰማቸው የራሳቸው ሆድ ከሞላ ዓለም ሁሉ ጠገበ ብለው የሚያወሩ ጊዜው ለዘረፋም ሆነ ለእጅ አዙር ንግድ መንገድ የከፈተላቸው የጊዜው ተለጣፊ የህዝብ ተባዪች ናቸው፡፡
    ከወደ ሰሜን የትግራይ ህዝብና የአማራ ህዝብ ለረሃብ እንደተጋለጠ የዓለም የዜና አናፋሾች አስነብበውናል። ግን በምድሩ ማሳና የእህል ከምር የሚያቃጥሉ ሾተላዪች ባሉበት ረሃብ ሰው ቢገድል ያስገርማል? በጭራሽ! ወያኔ ከተፈጠረ ጀምሮ ለትግራይ ህዝብ መከራና ሰቆቃ እንጂ ሰላምና ጥጋብን አሳይቶት አያውቅም። በትግራይ ምድር ያለው ሁኔታ የዪቱቭ አፍቃሪ ወያኔ እንደሚደሰኩሩት ሳይሆን እጅግ የከፋ ነው። ህዝቡ ከመከራ ወደ መከራ እየተሸጋገረ በለውና በይውን ብቻ ወያኔ እያስተማረ ይኸው እንሆ ዛሬም ለረሃብ አጋልጧቸዋል። የወያኔን መሪዎች እነ ጌታቸው ረዳን ተመልክቶ ረሃብ ትግራይ ውስጥ አለ ቢሉ አይታመንም። ሰርቀውም አሰርቀውም እነርሱ እየደለቡ ነጻ እናወጣሃለን የተባለው ህዝብ ግን ሞትና ረሃብ እየተፈራረቀበት ይገኛል። የአማራው ህዝብ በወያኔ የሶስት ጊዜ ወረራ ተዘርፎና ተጨፍጭፎ አሁን እንሆ የድህነቱ መንግስት ትጥቅ አስፈታለሁ በሚል ሰበብ በየጎራው ይላተማል። በዚህ ሁሉ የሚጎዳው አርሶ የሚበላውና በድህነት የሚማቅቀው ነው። በቅርቡ ብርሃኑ ጅላ የሰጠውን ቃለ መጠየቅ ረጋ ብሎ ቃሉን ብቻ ሳይሆን የሰውየን ገጽታ ከቃሉ ጋር አዛምዶ ለተመለከተ አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ እንዳለ ያመላክታል። በድሮን የራሱን ህዝብ የሚጨፈጭፍ መከላከያ የህዝብ ነው ማለት አይቻልም። ባጭሩ በቋንቋውና በብሄሩ የሰከረ ሁሉ በሚራወጥባት ምድር ሰላም ይኖራል ተብሎ አይገመትም። ብሄርተኞች ትላንትም ዛሬም የሃገራችን ሰላም አደፍራሽና መከራ አዝናቢዎች እንጂ የነጻነት ጮራ ፈንጣቂዎች ሆነው አያውቁም።
    አሁን በአቶ ታዬ ላይ የተደረገው ከሥራ ማሰናበትና እስራት በሌሎችም ላይ በይፋና በሰውር የሚሆን እየሆነም ያለ የግፈኞች በትር ነው። ይህ ሰውን በሌለ ነገር እየወነጀሉ ዘብጥያ ማውረድ፤ መግደል፤ ማሰርና መሰወር በየጊዜው ብቅ ያሉ አለቆቻችን ሁሉ የተጠቀሙበት ሽንፍላ የፓለቲካ ዘዴ ነው። ጠ/ሚሩ በዚህም በዚያም እያማታና በቃላት ጫዋታ ሰውን እየሸነገለ እድሜ ልኩን በስልጣን ላይ መቆየት አይችልም። እውነታው ለኢትዮጵያ ህዝብ ግልጽ ነው። ኑሮው አንገፍግፎታል፤ ስርቁቱ፤ ቅሚያው፤ ሥራ ማጣቱ፤ ከሥራ ያለምንም ምክንያት መባረሩና አሁን በትግራይና በአማራ እንዲሁም በሌሎች የደቡብ የሃገሪቱ ክፍል የተከሰተው ረሃብና መከራ ሰውን አንድ አርጎ በቃን ያንተ መንግስት በማለት የሚነሳበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም። የፋኖ ትግል የዚህ ግፍ ያቀጣጠለው ትግል ነው። የግፈኞች ማብቂያ ሳይታሰብ የሚሆን ነው። ለድህነቱ መንግስትም ማብቂያው ቅርብ እንደሆነ ማሳያው ከጭካኔ ወደ ጭካኔ መሸጋገሩ ነው።

  2. እንኳንስ የአገር በየትኞችም የጋራ በምንለው ጉዳዮች ጉዳይ ላይ ስንነጋገር ከየትኛውም አቅጣጫና ግለሰብ ወይም ቡድን የሚሰነዘሩትን አስተያየቶች እየመረረንም ቢሆን ተቀብሎ እንደ አስፈላጊነቱና እንደ አመጣጡ ከማስተናገድ ይልቅ ከገዛ ራሳችን ፈታኝ ሁኔታ የመሸሽ አባዜ ከተለከፍን አያሌ ዘመናት አስቆጠርን።

    በዚህ በታየ ደንደአ ሰሞነኛ ጉዳይ ላይ የተሰጡትን ሁለት አስተያየቶች ከገፅ ላይ መደምሰስም የዚሁ ክፉ ልክፍታችን አካል መሆኑ ነው።

    ታየን እንደ ሰብአዊ ፍጡር ከነቤተሰቡ እየደረሰበት ያለውን እንግልት ማንም ይፈፅመው ደስታ የሚሰማው ጤናማ ሰው የሚኖር አይመስለኝም።

    እንደ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ሥርዓት አባልነቱና ከፍተኛ ካድሬነቱ ለምን? እንዴት? ከየት ወደየት? ግልፅ ተናጋሪነት በፖለቲካ ጥበብ፣ በፅዕኑ መርህ፣ በማያወላውል ዓላማ፣ በዜጎች ሁሉ የሆነና የሚሆን ዴሞክራሲያዊ ግብ፣ ወዘተ ላይ የተመሠረተ ነው ወይ? ይህ ካልሆነ በግልፅነት ስም ራስን ለገዛ ራስ ጓዶች ጨካኝ ሰይፍ ሰለባ መሆን አጉል የፖለቲካ ጀብደኝነት (unnecessary political adventure)) እንጅ ለእውነተኛው አገራዊ የለውጥ እውን መሆን የሚያግዘው ጉልህ ግብአት የለምና አስተያየቶቻችን ሁሉ “ልክልካቸውን ነገራቸው/ነገረቻቸው እና ዘብጥያ ወረደ/ች” ከሚል ግልብ ስሜት ለመላቀቅ እንሞክር ማለት እንደ የለውጥ አደናቃፊ ወይም እንደ ግለሰባዊ ጥላቻ የሚታይ ሆኖ ከድህረ ገፅ ላይ የሚያስደመስስ ከሆነ እውነትም ከክፉ አዙሪት ለመውጣት ገና እጅግ ብርቱ ፈተና ይጠብቀናል ማለት ነው።

  3. TG – ዛሬ ነው እንዴ የሃበሻ ፓለቲካ የክፋት ጥግ የተገለጠልህ/ሽ? አብረው መክረው አይደል እንዴ በጎን በኩል ምክሩን ለገዳይ አካፍለው ጓዶቻቸውንና ወገኖቻቸውን አስገድለው እነርሱ ተሿሚ የሆኑትና የሚሆኑት። በየድህረ ገጽ አጸያፊና ዘር ተኮር ጽሁፎች ይወጣሉ፤ ይለጠፋሉ። በየስርቻው የተሸጎጠው የዘረኛ መንጋ በቋንቋውና በክልሉ ተሳክሮ የህዝባችን ጥቅል ገመናና ረሃብ ማየት ተስኖታል። ያኔ ድሮ ሰው ሰው እያለ አበው እንዲህ ብለው ነበር። ” በየወገንህ ቢሉት የመቶ ዓመት ቆዳ ገቢያ ወቶ ቆመ”። ምድሪቱ የድርቡሾች ከሆነች ቆይቷል። በዚሁ ሳቢያ የተሳከረው የሃበሻው ፓለቲካ አንዴ ፓርቲ ነኝ ብሎ ብቅ ሲል ሌላ ጊዜ ሲፈራርስ እያየን ነው። በሃበሻ ምድር ፍትህ ኖሮ አያውቅም። ነበርና አለ የሚሉ ካሉ መሟገት ይችላሉ። ለሃገር ለወገን የሚያስቡ በዘርና በቋንቋ ያልተሰለፉ ሰዎችን ቀድመን የምናጠፋ አመድ አቃፊዎች ነን። ይህ ግልጽ ያልሆነለት ሰው በህልም ዓለም የሚኖር ነው። ትላንት በትግራይ ተወላጆች አሁን በአማራ ተወላጆች ላይ ያለው ወከባና አፈሳ አልፎ ተርፎም ግድያ ሆን ተብሎ በጥናት የሚደረግ እንጂ ነሲባዊ ወይም ግብታዊ ድርጊት አይደለም። ጣሊያን ሁለት ጊዜ ኢትዪጵያን ሲያጠቃ እንደ ቀንደኛ ጠላት የፈረጀው አማራንና የኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያንን ነው። የጥላቻውም ምክንያት ሁለቱም የኢትዮጵያን አንድነትና የህዝቦቿን ልዕልና ስለሚሹ ነው፡፡ ይህን የድርቡሽ አሰራር እንዳለ በመሰልቀጥ ክፋትን በህዝቦች መካከል የዘራው ሻቢያ ነው። በተደጋጋሚ እንዳልኩት ይህ ጨካኝ ድርጅት ወያኔና ኦነግን ከዚሁ የክፋት ጽዋ ጋታቸው። ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ እንዲሉ ይኽው እነዚህ ሁለት ድርጅቶች የድርቡሾች ሁሉ ቆንጮ በመሆን ሃገሪቱን ያምሳሉ። ግን በጊዜ ሂደት ለሚነጋው ይነጋል። ሻቢያ፤ ወያኔ፤ ኦነግና ሌሎችም ጠባብ ብሄርተኞችና ጠበንጃ አምላኪዎች በጊዜው ይከስማሉ። ለመሸበት እንደ ጨለመ ይቀራል። ሞትም እፎይታ በሚሆንበት ሃገር ላይ ተኖረ ተሞተ ለውጥ የለውም። መታሰር፤ መፈታት፤ ተመልሶ መታሰር፤ ትላንት ታይቶ ዛሬ ሞተ፤ ሞተች መባል ሃበሻው የተለማመደው ነገር ነው።
    አቶ ታዬ ድሮም በወያኔ ጊዜ ያሻቸውን የሚናገሩ ለቆሙበት ዓላማ ወደ ኋላ የማይሉ አሁንም በድህነቱ መንግስት ላይ ያቀረቡት የሰላ ትችትና ዘለፋም ያው ዘብጥያ አስወርዶ ቤተሰባቸውን ለመከራ ዳርጓል። ይህ ነው እንግዲህ የእኛ ሃገር ነገር ሰውን ማሰቃየት፤ ቤተሰብን ማበራየት ክርስቲያን ነኝ ድአ አደርጋለሁ እያሉ በበደል ላይ በደልን መከመር። በአቶ ታዬ እስር እፎይ እሰይ የሚሉ ሁሉ የፓለቲካ ክርፋታቸው ሰማይ ደርሶ መልስ ያጣ የቁም ሙታኖች ናቸው። ሰው የሆነ ሁሉ በማንም ሰው መከራና ሞት ደስተኛ ሊሆን አይገባም። ግን ሃበሻ አይደለን አንድ ሰው ሆነን ብዙ ባህሪ የተላበስን ጉዶች ነን። ምህረት ያምጣልን። እናም ወገኔ አስተያየትህ እዚህ ሆነ ሌላ ቦታ ባይለጠፍ አትዘን። ነገም ሌላ ቀን ነውና እስካለን እንበርታ! እውቁ ገጣሚና ደራሲ ከበደ ሚካኤል ከጻፉት አንድ ስንኝ ወስጄ ሃሳቤን እዘጋለሁ።
    በዘመን ግስገሳ እድሜአችን ተማርኮ
    ያለፍነው እኛ እንጂ ጊዜ አይደለም እኮ።

  4. ጎበዝ የጻፍነውን ምነው አነሳችሁብን? ታየ መታሰሩ ታየነቱን አይለውጠውም እኮ ወደ ኋላ የጻፈውን መመልከት ነው እስር ቤትም ሁኖ ከአቋሙ ፈቀቀ አላለም፡፡ ከጁዋር መሃመድ የተለየ የሚያደርገው ምን ተገኝቶበት ነው? በስሜት አንነዳ እንጅ ግለሰቡ የሃገርና የአንድነት ጠንቅ ነው አብይ ስላሰረው ብቻ የኢትዮጵያ ወዳጅ ተደርጎ መሳል የለበትም፡፡ ነገ በቀለ ገርባንም የአንድነት ሃይል ነው ልንለው ነው? አብይ፤ጁዋር ሽመልስ፤በቀለ፤መራራ፤ሌንጮ፤ዳውድ፤…. መልካቸው እንጅ ስራቸው አንድ ነው አደባባይ ያልወጡ ውስጥ ለውስጥ የሚሰሩ ጭራቆችም አሉ ተው አትበሉን እንናገርበት፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share