ሰልፍ ወጥተን ይሄን ሰውዬ ሀይ ማለት አለብን – በቀለ ገብርኤል

ጥያቄ አለኝ፣ መልስ እሻለሁ።

#image_title

“…ሰልፍ ወጥተን ይሄን ሰውዬ ሀይ ማለት አለብን። ለውጥና ሽግግር መጠየቅ አለብን…”5/13/23 P2P

“…አብይ አህመድ ከስልጣን ይውረድና ሁሉን አቀፍ ሽግግር ይፈጠር…” 5/9/23 P2P

“…ይህ ሰው ስልጣን መልቀቅ አለበት። ሽግግር ይመጣ ዘንድ የአብይ ዘወር ማለት ወሳኝ ጉዳይ ነው። በተለይ የዚህ ሰው ማህበራዊ ፍልስፍናው አደገኛ ነው።” 5/6/23 – P2P

ከላይ የተጠቀምኩትን ጥቅስ የወሰድኩት፣ በተለያየ ጊዜ “ፒ ቱ ፒ” (People to People) የተባለ ድረ ገጽ ላይ ጽሀፋቸውን ከሚያስነብቡት ከአቶ ገለታው ዘለቀ ተከታታይ ጽሁፍ ላይ ነው። መቼ እንደታተመ ቀኑን፣ ወሩን ና ዓመተ ምህረቱን ጠቅሻለሁ።

በቀጥታ ለሳቸው ያልመለስኩት፣ ተመሳሳይ ሃሳቦችን በሌላ ጽሑፍ ስላነበብኩ፣ ሁሉም እንዲሳተፍና ያለወኩት ነገር ካለ እንዲያሳውቊኝ፣ እግረ መንገዴንም “የሽግግር መንግስት” የሚለው፣ እውነት ለአገራችን በአሁን ሰዓት ትልቅ መፍቴ ነው? መርጫ በተካሄደበት ሀገር፣ መራጩ ህዝብ መሪውን በመረጠበት ሰዓት፣ የሽግግር መንግሥት አስፈላጊነቱ ለማነው? የሽግግር መንግሥት መደረግ አለበት የሚሉ፣ ወክልናውን ከማን ነው ያገኙት? ያለ ህዝቡ ፍቃድ የሚሰራ ሥራ ህጋዊ ነው ወይ? ሌሎችም ተመሳሳይ ጥያቄ ይኖራል ብዬ ስለማስብ ማብራሪይ ካለ ቢሰጥበት ምልካም ነው እላለሁ።

 

ወደ ዋነው ጉዳዬ ልግባ…

“ስልጣን መልቀቅ አለበት፣ ሁሉን አቀፍ ሽግግር ይፈጠር” የሚለውን ጽሑፍ ሳነብ፤ ለመረዳት በጣም ያስቸግረኛል። ምክንያቱም አንድ መሪ በህዝብ ከተመረጠ፣ ተወደደም ተጠላም የህዝቡ ድምጽ መከበር አለበት። ሌላው ቢቀር ጥሩም ሰራ መጥፎ – መሬት ላይ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ይወስናል – የምርጫውን ዘመን መጨረስ አለበት። እንዲያው ይሁን እንኳን ቢባል፣ ሥልጣን ይልቀቅ የሚለውን ጥያቄ ማንሳት ያለበት መራጩ ህዝብ ነው። ካልሆነም፣ የመረጥነው መሪ ምንም ነገር አልሰራልንም ቢሉ እንኳን፣ ህዝቡ በሚቀጥለው ምርጫ ድምጹን ይነፍጋል። ምን አልባት ከተሳሳትኩ እታረማለሁ፣ መራጩ ህዝብ ለማንም ግለሰብም ይሁን ቡድን መንግሥትን አውርዱልኝ ብሎ ውክልና የሰጠ አይመስልኝም። የለም! ወክሎናል የምንል ካለን ያንን ብሰማ ደስ ይለኛል። መራጩ ህዝብ የሚያውቀው የመረጠውን መሪ በቻ ነው፣ ታዲያ የሽግግር መንግስቱ ለማነው? ለህዝቡ እንዳይባል፣ ህዝቡ አውቆና ወዶ የመረጠው መሪ አለ፣ እንዲያው ይሁን እንኳን ቢባል፣ በህጋዊ መንገድ የተመረጠውና አገሪቷን የሚያስተዳድረውን መሪ ወረዳ እንበል፣ ከዚያስ? ውክልና የሌለው፣ በህዝቡ ያልተመረጠ፣ እንዴት ነው አገር የሚያስተዳድረው? በጉልበት? በማስፈራራት? ይህ ደግሞ

አምባገነንት አይሆንም? ህዝቡ ለስንት ዓመት ሲታገል፣ መስዋዕትነት ሁሉ ሲክፍል የነበረው፣ ድምጹን በሽግግር መንግሥት ስም ለመቀማት አይመስለኝም፣ ህዝቡ ለኔ ይጠቅመኛል፣ ይበጀኛል፣ ሊያስተዳድረኝ ይችላል፣ አመነዋለሁ፣ ብሎ ከጧት አስከ ማታ ጸሐይ፣ ብርድ፣ ሳይል፣ ለረጅም ሰዓት ተሰልፎ የመረጠውን፣ እንደማክበር፣ ፈጣሪ እንዲህ ዓይነቱን ጊዜ – የጥይት ድምጽ ሳይሰማ፣ ኮሮጆ ሳይሰረቅ፣ በሰላም ወጥቶ፣ በሰላም የሚፈልገውን መርጦ፣ በሰላም ቤቱ መግባቱ – ተመስገን የሚያሰኝ ነው። እኔ በበኩሌ ይሄን ቀን በማየቴ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ። ሌላው ቢቀር፣ (እንደፈለገን መናገር መብታችን ቢሆንም) ህዝቡ የመረጠውን መሪ ማንጓጠጥ፣ መስደብ፣ ከቤተ መንግሥት ጎትተን እንወጣለን ማለት፣ ለመረጠው ህዝብ ትልቅ ንቀት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያዊ ጨዋነትም አይመስልኝም።

ሀሉም የራሱ ምልከታና ነገሮችን የሚያይበት መንገድ የተለያያ ስለሆነ፣ ለኔ ትልቊና ዋናው ጥያቄ መሆን አለበት ብዬ የማምነው…

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን ሲመጡ የተረከቡት አገር በምን ሁኔታ ላይ ነበር? ለማነጻጸርም እንዲመች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሌላ ፓርቲ ወይም ሌላ መሪ ሥልጣን ይዞ ቢሆን፣ ጠቅላይ ሚኒሰትሩ ካደረጉት ውጪ ምን የተለየ ሥራ ይሰራ ወይም ትሰራ ነበር? አለ ከተባለ አንድ ሁለት ሶስት እየተባለ ቢብራራ ደስ ይለኛል።

እውነቱን እንነጋገር ከተባለ… አሁን በሥልጣን ላይ ያሉት የአገር መሪ በጠመንጃ አፈ ሙዝ ነው ሥልጣን የያዙት? ህዝቡ ፈልጎና ወዶ አይደለም የመረጣቸው? የህዝቡ የመመረጥና የመምረጥ መብቱ መጠበቅ የለበትም? ከተመረጡ በሗላ የሥልጣን ጉዟቸው አልጋ በ አልጋ ነበር? በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ጦርነት አልነበረም? አገሪቷ አለኝ ያለቻቸው ጦር መሣሪያ (85%) ጁንታ በተባለው ቡድን አልተወሰደም? መወሰድ ብቻ ሳይሆን፣ የሰሜን ዕዝ ጦር በተኙበት አልተጨፈጨፉም? በአጋሪቷ በተለያየ ክልል ሽምቅ ተዋጊዎች፣ በውጪ ሃይል እየታገዙ መሰረታዊ ልማት ላይ ጉዳት አላደረሱም? ባንክና ሌሎቹን ንብረቶች አልዘረፉም? ዘረኞችና ጽንፈኞች መጤ እያሉ ህጻናትን፣ እናቶችን፣ አረጋዊያንን፣ በሜንጫ ና ስለት ባለው ነገር አልጨፈጨፉም? ከመኖሪያ ቄያቸው አላሳደዷቸውም? ሙስና ውስጥ ካላይ አስከ ታች ባለሥልጣናት አልተዘፈቊም? ዳኛው ሌብነት ውስጥ አልተሰማራም? ግጭት ፈጣሪዎቹ፣ ጽንፈኞቹ በመንግሥት መሥሪያ ቤት ውስጥ የሉም?

ተጨማሪ ያንብቡ:  እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልፈለጉት መጠን… ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው - ሰርፀ ደስታ

እንደዚያ የተዳከመች፣ በዘር የተከፋፈለች፣ የተዘረፈች፣ እንደ ትሗን ደሟን እየመጠጡ፣ እንጡራ ሃብቷን ሙልጭ አድርገው ወስደው፣ ባህር ማዶ ገንዘባቸውን እያሸሹ፣ ነገር ግን ኢትዮጵያ ለማለት የተጸየፈ መሪ የነበራት አገር አልነበረችም? ሌሎችም ለመንገርም ለመስማትም አጻያፊ ድርጊት ሲፈጸምባት የነበረች አገር፣ የፈለገው አዲስ መንግሥት ቢመጣ፣ የፈለገው መሪ የሥልጣን ወንበር ላይ ቢቀመጥ፣ የ 27 ዓመቱን ሰቆቃ በሁለት በሶስት ዓመት መቀየር ይቻላል? ችግሩ የትየ ሌሌ ነው፣ ከየት ነው የሚጀምረው? መንግሥት ወደ ልማት ገባ ሲባል፣ በሸርና በሴራ የታወቀው ጅንታ፣ ከጦሩ በዘረፈው፣ ከባድና ቀላል መሣሪያ አገሪቷ ሰላም እንዳታገኝ፣ በየቦታው ጦርነት ይጀምራል፣ የ አገሪቷ ባጀት ለምን ይዋል? ለጦርነት፣ ለልማት፣ ለጤና፣ ለትምህርት…

 

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ይልቀቊ፣ ጊዚያው መንግሥት ይቋቋም ለምትሉ፣ ከተፈቀደልኝ ጥያቄ ልጠይቅ…

እንበልና እናንተ የምትደግፉት ፓርቲ ወይም የመረጣችሁት ጠቅላይ ሚኒስተር የ አገር መሪ ሆኖ ቢሆን፣ አሁን ካሉት ጠቅላይ ሚኒስተር በተለየ መንገድ ምንድነው የሚያደርገው? በሌላ አነጋገር፣ ጅንታው ከሥልጣን ከወረደ በሗላ የመጀመሪያ ሥራው የሚሆነው ወይም የሆነው አገር ማፈራረስና መልሶ ሥልጣን እጁ ውስጥ ማስገባት ነው። እናንተ የተለየ መሪ ስለመረጣችሁ፣ ጅንታው ከመተንኮስ ዝም ይላል? መርሳት የሌለብን፣ አገሪቷ አለኝ የምትለውን ከ 85 % ያላነስ ጦር መሣሪያ በእጁ አስገብቷል፣ አስቀድሞ የተዘጋጀበትና የነደፈው ሃሳብ ስለሆነ፣ አሁን ከተመረጠው የ አገር መሪ፣ ሌላ ተመርጦ ቢሆን፣ የሰሜን ዕዝ ጦርን ከመጨፍጨፍ ወደ ሗላ የሚል ይመስላችሗል? ወይስ ሌላ መሪ ስለተመረጠ፣ ትንሽ ስራውን እስኪያውቅና እስኪለማመድ ጊዜ እንስጣው የሚሉ ይመስላችሗል?

እናንተ የምትደግፉት መሪ ሥልጣን ስለያዘ ጅንታው ወደ ዋናው ከተማ ከመገስገስ ይቆጠባል? አሁን ካሉት የአገሪ መሪ ሌላ ሥልጣን ይዞ ቢሆን፣ ምዕራባዊያን ጁንታውን ከመርዳት ይቆጠባሉ? ሌላና የተለየ መሪ ቢሆን፣ ጁንታው ሰሜን ሸዋ ሲደርስ፣ ስልጣኑን ለምክትሉ ሰጥቶ ወደ ጦር ሜዳ ይሄዳል? ምዕራቢያዊያንና አሜሪካኖቹ አገር ለቃችሁ ውጡ እያሉ በማዕቀብና በመግለጫ ቢያጣድፉ፣ አሁን ያሉት የአገር መሪ ካደረጉት ውጪ ሌላ መሪ ቢሆን ምን ነበር የሚያደርገው? ይሄ ቁልፍና የአገርን ዕጣ ፋንታ የሚወስን ነው።

በአገር ወሰጥ ያሉት ነጻ አውጪ ነን የሚሉትና በየቦታው እየዞሩ ሰው የሚያፈናቅሉትንና የሚገድሉትን የመሪነት ዕድል ብታገኙ ምንድነው የምታደርጉት? መጀመሪያ በታንክና በሮኬት እያታጀበ ወደፊት የሚገሰግሰውን ጅንታውን ነው የምትፋለሙት ወይስ በየመንደሩ እየተሽሎከለኩ ነጻ አውጪ ነን የሚሉትን ነው የምትዋጉት? መርሳት የሌለብን ወደ 85% የሚሆነው የአገሪቷ የጦር መሣሪያ በጅንታው ተዘርፏል።

እኚህ መሪ ምንድነው ማድረግ ያለባቸው? ሚዛናዊስ መሆን የሚችሉት አንዴት ነው? ጦርነት አያለ፣ አገሪቷን በሰላም ማስተዳደር እንዴት ነው የሚቻለው? ክልሉን ለጽንፈኞች ጥሎ የተቀረው ህዝብ ላይ ማተኮር? ጽንፈኞቹ አገር ጦርነት ላይ ስላለች፣ ለጊዜውም ቢሆን አደብ እንግዛ ይላሉ? እኚህ ጠቅላይ ሚኒስተር ወደ ሥልጣን ሲመጡ፣ የገጠማቸው ችግር ቀላል ነው አይባልም፣ ግን እንደዘያም ሆነው፣ ባገኙት ቀዳዳ፣ መሰራት ያለበትን ሰርተዋል፣ የአባይ

ግድብ ተጠናቋል፣ የተለያዩ ፕሮጄክት ተጀምረው ብዙ ዝርፊያ የተካሄደባቸው፣ እሳቸው ወደ ሥልጣን ከመጡ በሗላ የተጠናቀቁ ፕሮጄክቶች በጣም ብዙ ናቸው፣ ነጮቹ የፈለጋቸውን ያህል ቢያስፈራሩም፣ ማስጠንቀቂያ ቢሰጡም፣ ማዕቀብ ቢጥሉም፣ ከአቋማቸው ፈቀቅ አላሉም። ይባስ ብለው ጁንታውን በተለያየ ቴክኖሎጂ እያገዙ ወደ መሀል ሀገር ለማምጣት ቢሞክሩም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣናቸውን ለምክትላቸው በመስጠት፣ ወደ ጦር ግንባር በመዝመት፣ መመሪያ እየሰጡ፣ ጅንታው በመጣበት እግሩ እንዲመለስ አድርገዋል። ጁንታው ሶስት ጊዜ ጦርነት ቢጀምርም፣ በመጨረሻ በመከላከያና በክልል ጦር ድባቅ በመመታት፣ ጦርነቱ ተጠናቋል።

 

ይሄ ሁሉ የሆነው እንግዲህ አገሪቷ በውስጥም በውጪም እንደ ድፎ ዳቦ ከላይና ከታች በእሳት እየተለበለበችበት ባለበት ወቅት ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማራ ሕዝብና የአጭቤ ዜናው አባት አማራጠሉ ቢቢሲ

እናንተ የመሪነቱን ዕድል ብታገኙ፣ መከላከያውን፣ የአየር ሃይሉን በጦርነት መሃል አንዴት ነው የምታዘምኑት? ድሮን የተባለውን ቴክኖሎጂ ታስገቡ ነበር? የአገሪቷ መሪ ብትሆኑ ጦር ሜዳ ትዘምቱ ነበር? እናንተ ያዋቀራችሁት ካቢኔ፣ በጀርባ ሄዶ ከጽንፈኞች ጋ ቢቧደን፣ ተባብሮ ቢያስጠቃ፣ መጤ እያሉ ለሚያሳድድቱ ድጋፍ ቢያደርግ፣ መጤ እያሉ ለሚጨፈጭፉት እንዳይያዙ ቢያስመልጥ፣ ምንድነው የምታደርጉት? እናንት ብትሆኑ ሥልጣን ወዲያው እንደተረከባችሁ፣ ወደ ጎረቤት አገር እየሄዳችሁ ጥሩ ግንኙነት ታደርጉ ነበር? – ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሚተቹበት አንዱ፣ ሥልጣን እንደያዙ ወደ ጎረቤት አገር በመሄዳቸው “የጫቊላ” ሽርሽር ላይ ናቸው እየተባሉ ሲተቹ ነበር። እስኪ ከጁንታው ሥልጣን ወሰዳችሁ ቢሆን ኖሮ ምንድንነበር የምታደርጉት? የተጣሉትን የእምነት አባት፣ ለብዙ ዓመት የተለያዩትን፣ በተለያየ አገር የሚኖሩትን ታስታርቊ ነበር? እናንተ በምትጓዙበት አውሮፕላን አሳፍራችሁ ይዛችሁ ትመጡ ነበር? በተለያየ አገር እየዞራችሁ እስረኞች እንዲፈቱ ታደርጉ ነበር? እስረኞቹን በራሳቸሁ አይሮፕላን አሳፍራችሁ አብራችሁ ትመጡ ነበር? ከጎረቤት ሀገር ከኤርትራ ጋ እርቅ ትፈጥሩ ነበር? መሀል ከተማን አስውባችሁ፣ ብዙ የሥራ ዕድል ትከፍቱ ነበር? ገበታ ለአገር እያላችሁ በየክልሉ ትልልቅ ፕሮጄክቶች ታስጀምሩ ነበር?

እናንተ ብትሆኑ፣ በጣም አስከ አፍንጫው የታጠቀ፣ ከባድ መሳሪያ ያለው፣ ሮኬት ሁሉ ወደ ጎረቤት አገርና ጎረቤት ክልል ማስወንጨፍ የሚችል የወንበዴ ብዱን በእብሪት ጦርነት ከፍቶ ወደ ፊት ሲገሰግስ፣ በሌላ ክልል ያለ ጽንፈኛ ደግሞ እንደ ሽምጥ ተዋጊ፣ ሲለውም እንደ ነጻ አውጪ ነኝ የሚል ዘረኛና ጽንፈኛ፣ ፈት ለፊት ሳይሆን፣ በድብቅ፣ የጦር መሳሪያ የሌለውን ምስኪን ህዝብ – ህጻናት፣ እናቶች፣ አረጋዊያንን – ሲገድል፣ ሲጨፈጭፍ ምንድነው የምታደርጉት? ከባድ መሳሪያ ያለውን ጥላችሁ በየመንደሩ የሚሽለኮለኩትንና አካባቢውን ሰላም የነሱትን ታሳድዳላችሁ? ወይስ ለጊዜውም ቢሆን፣ ታንክና ሮኬት የያዙትን ትፋለማላችሁ? እስኪ የናንተ የጦር ፕላን ምንድነው ነበር የሚሆነው? ጦርነት አይጀመር

እንጂ አንዴ ከተጀመረ፣ ምን አልባት ብዙ ሰው እንዳይሞት ሊደረግ ይችል ይሆናል፣ ግን በፍጹም ህይወት እንዳይጠፋ ማድረግ ይቻላል? ይቻላል ከተባለ እንዴት? የመትገጥሟቸው አገር የሚያፈርሱ ብቻ ሳይሁን፣ በማዕበል ወጣቶችን አደንዛኝ ዕጽ እየሰጡ የሚያዘምቱ ናቸው፣ መሳሪያ ያልያዙትን በማዕበል ሲመጡ፣ እንደታዘዙት መሳሪያ ቀምታችሁ ተዋጉ የተባሉትን ወጣቶች በያዛችሁት መሣሪያ ትገላላችሁ፣ ለጊዜውም ሆን ታፈገፍጋላችሁ? ምንድነው የምታደርጉት?። የአገሪቷ ጠላት የሚባሉት አገሮች የሾማችሁትን ጠቅላይ ሚኒስትር አገር ለቀው አንዲሄዱ ቢገፋፉ፣ ቢያስፈራሩ፣ በገንዘብ ቢያባብሉ፣ ምንድንነበር የምታደርጉት? ወይስ አሁን እንዳሉት ጠቅላይ ሚኒስተር ወይ ፍንክች ትሉ ነበር። ጠላት ወደ መሀል አገር እየገሰገሰ፣ እየተቃረበ ሲመጣ፣ እውነት የለበሳችሁትን ሱፍ ልብስ አውልቃችሁ፣ ሥልጣናችሁን ለምክትል ሰጥታችሁ ለመፋለም ወደ ጦር ግንባር ትዘምታላችሁ? ወታደሩ የሚበላውን በልታችሁ፣ እንደ ወታደር አፈር ላይ ተኝታችሀ፣ ለሳምንታት አስቸጋሪና አደገኛ የተባለበት ቦታሰ ተቆያላችሁ?።

መረጃ እያቀበሉ፣ በገንዘብ እየረዱ፣ ጽንፈኞች ከተማ ወሰጥ እንዲገቡ እያደረጉ፣ ንብረት የሚያወድሙ፣ ግለሰቦችን የሚያቆስሉና የሚገድሉ ሰዎችን እናንተ ብትሆኑ ምንድነው የምታደርጉት? ይዛችሁ ፍርድ ቤት ማቅረብ፣ በተገኙበት መግደል፣ ዝም ማለት፣ በተጨማሪ የውጪ አገሮች ለአገር በቀል አሸባሪዎች፣ የሚሰጡትን የገንዘብና የጦር መሳሪያ እርዳታ በጦርነት ጊዜ እንዴት ነው የምታስቆሙት? ታንክን የሚያክል ትልልቅ መሣሪያ መሬት ውስጥ እየደበቊ አሳቻ ጊዜ የሚጠብቁትን እንዴት ነው የምትፋለሟቸው? በእርግጥ ብዙ ነገር በጦርነት ወቅት የተፈጸሙ ነገሮች አሉ – ብዙ ሰው ተሰዷል፣ ተገድሏል፣ ሞቷል፣ ተርቧል፣ ይሄ ብቻ አይደለም፣ የጽንፈኞች ጭካኔ እስከ ጥግ ድረስ የታየበት ጊዜ ነበር። እነዚህም ቢሆን በዝርዝር ተመዝግበው እንደተቀመጡ በዜና ማሰራጨ የሰማሁ ይምስለኛል። የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ፣ እጁ ያለበት በሙሉ ህግ ፊት መቅረቡ አይቀሬ ነው።

በአጠቃላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በህዝብ ከተመረጡ በሗላ፣ ጉዟቸው አልጋ በአልጋ አይደለም፣ ነጮች አንደሚሉት “baptism by fire” በፍም እሳት ውስጥ እየተለበለቡ መጓዝ ማለት ነው። አሁን እኮ የተያያዘው፣ የህዘብን ድምጽ ያለማክበር ነው፣ በህዝብ የተመረጠ መንግስትን መፈንቅል መንግስት ካላደረግን ነው፣ እንድ ግልጽ ያልሆነልኝና መረዳት የምፈልገው ነገር ቢኖር፣ ይሄን ያህል ለአገርና ለህዝብ ከተጨነቃችሁ፣ ለምንድነው የራሳችሁን ፓርቲ መስርታችሁ፣ በደንብ ተዘጋጅታችሁ፣ ሃሳባችሁን ሽጣችሁ በምርጫ ለማሸነፍ የማትሞክሩት? አቋራጭ መንገድ ለምን ፈለጋችሁ? እወነት ለህዝቡ ብላችሁ ነው ወይስ ለሥልጣን ሽሚያ? ህዝብ ተገላገልኩ፣ የጥይት ድምጽ ሳልሰማ በድምጼ የምፈልገውን መርጫለሁ ብሎ እፎይ ባለበት ሰዓት፣ ቀኑን ብቻ ሳይሆን ምሽቱን ተሰልፎ የመረጠውን መሪ፣ ሁከትና ረብሻ በማስነሳት፣ ደም በማፋሰስ፣ ሥልጣን ለመያዝ የሚደረገው ሩጫ

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኢትዮጵያን መክሰስ እና መዉቀስ የት ሊያደርስ ?

 

ለመረጠው ህዝብ ንቀት ብቻ ሳይሆን ጥላቻም ነው ቢባል ማጋነን ይሆናል?። የሚቀጥለው ትውልድ ከዚህ ምንድነው የሚማረው?

በእርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ካቢኔቸው፣ ምክር ቤቱ ስህተት አይሰሩም ማለት አይደለም፣ መቶ በመቶ ትክክል ናቸው ማለት አይቻልም። የፈለገው ሌላ መሪ ቢመጣ፣ 120 ሚሊዮን ህዘብ ያለበትን ለመምራት፣ ችግሩ የትዬ ለሌ ነው፣ እንኳን ያንን ያህል ህዘብ ላለው አገር ቀርቶ፣ ቤተሰብ ለማስተዳዳር ከባድ ነው። በተለይ አገር ውስጥ ሰላም ያለመኖር ችግሩን እጥፍ ድርብ ነው የሚያደርገው።

 

በኔ እምነት የአንድ ሚሊዮን ዶላር ጥያቄ ነው የምለው…

አይሆንም እንጂ ቢሆን ኖር፣ ወይም እግዚአብሔር አይበለውና ጅንታው ሰሜን ሸዋ (ሸዋ ሮቢት) ደርሶ፣ ከመባረሩ በፊት ወደ ፊት ገስግሶ መሀል ከተማ ቢጋባ ኖሮ፣ ምን ሊከሰት አንደሚችል መገመት አይከብድም – የሚያፈራርሰው ንብረት እንዳለ ሆኖ፣ የሚጠፋው የሰው ህይወት ቀላል ይሆን ነበር? አሁን እንደሚደረገው፣ ሁካታና ግርግር በመፍጠር ወንበሩን ከነሱ እንነጥቃለን ተብሎ፣ ግርግር ይፈጠር ነበር? ጊዚያዊ መንግሥት ይቋቋም የሚለው ድምጽ ይሰማ ነበር? መቼም ለ27 ዓመት የታየ ስለሆነ፣ ያንን የሚሞክር ያለ አይመስለኝም። በእርግጠኝነት የሚሆነው ነገር ቢኖር፣ ማልያ በመቀየር፣ በድጋሜ አድርባይነትን ማሳየት፣ አብሮ መዝረፍና አገር መግደል ነው። አገር ውስጥ ያለው ጋዜጠኛ፣ አክትቪስት፣ የማህበራዊ አንቂ፣ በቲክ ታክ የሚሳደብ፣ ድምጹን አጥፍቶ ጸጥ ነው የሚለው፣ ምርጫ በካርድ የሚባለው የማይታሰብ ነው፣ አንቀጽ 39፣ ወረቀት ላይ እንደተጻፈ ይቀራል፣ ዲያስፖራውም ከውጪ ሆኖ ይታገል አንደሆነ እንጂ፣ ወደ አገር ገብቶ የማይታሰብ ነው።

 

ሌላው ቢቀር፣ የህዝቡ ድምጽ ይከበር፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩም የተመረጡበትን ዓመት ይጨርሱ፣ ከሳቸው የተሻለ እንሰራለን የሚል ካል ተደራጅቶ፣ ሃሳቡን ለሚመርጠው ህዝብ አሰረድቶ ወይም ሸጦ መወዳዳር እንደሚቻል በተለያየ ጊዜ ሲነገር የሰማሁ ይመስለኛል። ብንወዳደርም ማሸነፍ አንችልም ያለን አማራጭ በግርግር፣ በረብሻ፣ መፈንቅለ መንግሥት እናደርጋለን ከሆነ፣ ህዝቡ የነጻነትን ትርጉም ማወቅ ብቻ ሳይሆን በደንብ አጣጥሟል፣ ከካርድ ውጪ አሻፈረኝ የሚል ነው የሚመስለኝ። አለበለዚያ፣ የምትኖረውን ህይወት ከአንተ በላይ እናውቅልሃለን ማለት፣ የስድብም ስድብ ነው። በሌላ ነገር መርዳት ባንችልም፣ መብትህን አንተ አታውቅም ብለን ሙልጭ አድርገን ህዝቡን ባንሰደበው መልካም ነው።

 

ሌላ ግርም የሚለኝ…

እንዲያው ስታስቡት፣ ጠቅላይ ምኒስትሩ፣ አሁን በዚህ ሁሉ እሳትና መከራ አልፈው፣ ላይ ታች ብለው፣ ሌላው የሥልጣን ወንበሩ እንዳይቀማ እዚያው ቢሮው ሙጭጭ ሲል፣ እሳቸው ለዚያ ደንታ ሳይሰጣቸው፣ ሥልጣናቸውን ለምክትላቸው ሰጥተው፣ የህይወት መስዋዐትነት ለመከፈል ጦር ሜዳ መሄዳቸው፣ ከራሳቸው ሕይወት አገራቸውን ያስቀደሙ አይመስላችሁም? ህዝቡ ረጅም ሰዓት ተሰልፎ ድምጽ የሰጣቸውን፣ ሥልጣን ልቀቊ ቢባሉ የሚለቊ ይመስላችሗል? የህዝቡንስ አደራ እንዲህ በቀላሉ የሚያስነኩ ይመስላችሗል? የህዝቡ አደራ ብቻ ሳይሆን፣ ጊዜያዊ መንግሥት ይቋቋም የሚሉት ምንም የህዝብ ውክልና የሌላቸው፣ ራሳቸውን በራሳቸው የመረጡ መሆኑ እሱ ራሱ አግራሞትን የሚጭር ነው። ይሄ ብቻ ሳይሆን፣ አካሄዳቸውም በብልጠት የተሞላ ይመስላል። ለአገር አደገኛ ናቸው የተባሉትን ከተፋለምክልን፣ ሰላም ካወረድክ በሗላ፣ ከዚህ በሗላ ሥልጣኑን ስጠንና እኛ እንምራው ማለት ጮሌነት ነው የሚመስለኝ።

 

እስኪ ጥያቄዬን ለየት ባለ መንገድ ልጠይቅና ጽሑፌን ላብቃ…

እንዲያው እንበልና ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ውጪ ሌላ ፓርቲ አሽንፎ ቢሆን፣ የተመረጠው መሪ ጊዜውን ወይም ተርሙን ሳይጨርስ፣ ሌላ ተቀናቃኝ ቡዱን መጥቶ ያለ ምርጫ ሥልጣን ልቀቅ ቢል፣ ሥልጣኑን ይለቃል? በተጨማሪ ፓርቲው ሥልጣን ላይ እያለ፣ ሌላው ቡድን ጊዚያዊ መንግሥት ይቋቋም ቢል፣ የፓርቲው መልስ ምንድነው የሚሆነው? በፍቃደኝነት ሥልጣን ያስረክባል? ወይስ በሚቀጥለው ምርጫ ካሸነፋችሁ ሥልጣኑን እንለቃለን ነው የሚለው?

 

ከአክብሮት ጋራ

በቀለ ገብርኤል

እሑድ ግንቦት 6 ቀን 2015 ዓ.ም (5/13/23)

1 Comment

  1. You assumed so much in your writing. There was no proper election as it was done in the middle of a hot war. It was done on purpose for psychosocially benefit his party. Even then there was no competition in the largest state, Ormomia in addition to around 96 seats still open due to security. He also pretend to go to war to take the credit for himself. I know it was good for the moral of the troops but he was not in danger as he never lead a troop at that time or in any other time. What I heard was that he worked in communication in the past. At that time he had to make decision whether from office or from some hiding place as he is a commander in chief. The most important factor is he is not trust worthy as his statements from time to time oppose to each other. So I don’t see him as a legitimate leader.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share