ትግሉ ከቤተእምነቶች በላይ አገር የማዳን ትግል ነው!

 ጥር 29 ቀን 2015ዓም(06-02-2023)

የኦርቶዶክስ ክርስትናና የእስልምና እምነት ተከታዮችን ማዳን ማለት ተቋማቱን ማዳን ማለት ነው።የሁሉም እምነት ተከታይ የሆነው አማራ እንዳይረሳ አደራ!

የዛሬ 48 ዓመት ወያኔ ደደቢት በረሃ ሲገባ ዓላማ አድርጎ የያዘው የእምነት ተቋማትን በተለይም የኢትዮጵያን ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንንና የአማራውን ማህበረሰብ ለማጥፋት እንደነበረ ፣ሥልጣንም ላይ በተቀመጠበት የ17 ዓመት አገዛዙ እነዚህን በጠላትነት የፈረጃቸውን በግልጽና በድብቅ ሲያጠቃ እንደኖረ የሚካድ አይደለም።በእርሱ ጥፋተ እምነት የተጠመቁት አገር ጠል ሃይሎች፣ኦነግና ሌሎቹም ያንን የጥፋት ተልእኮ ተሸክመው በተግባር ሲፈጽሙ አሁን ካለንበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። ባለፉት 32 ዓመታት ቤተክርስቲያን ሲያቃጥሉ፣ምእመናንን ሲያርዱ ኖረዋል።ከማህበረሰብም በኩል በሚከተለው እምነትና በጎሳ ማንነቱ የፈጁትን ዜጋ በተለይም ሊያጠፉት አቅደው የተነሱበትን  የአማራ ተወላጅ በአሃዝ ማስቀመጥ ይከብዳል።የገደሉበትን መንገድም ለመግለጽ ይዘገንናል።

ከአራት ዓመት ወዲህ በኦነግ ኦሕዴድ የተቃጠሉት ቤተእምነቶችና የታረዱት ምእመናን ከሌሎቹ ጊዜያቶች በቁጥርም በመጠንም ብዙ ናቸው።በሁለቱም ቤተእምነቶች ምዕመናን ላይ ከተሰነዘረው የማጥቃት ዘመቻ በዋናነት ሰለባ የሆነው አማራው ክርስቲያንና አማራው ሙስሊም ነው።ይህ የሚያሳዬው እምነቶቹና አማራው የተሳሰሩ መሆናቸውን ነው።አንዱ ከሌላው ተነጥሎ ያልተጠቃ መሆኑን ነው።ቤተእምነቶቹ ካለሰው ወና ቤቶች ናቸው።ሲያስከብራቸውና ሲያከብራቸው  የኖረው  ምእመናኑ በዋናነት የአማራው ማህበረሰብ መሆኑ ሊካድ አይገባም።ለዚያም ነው አገር ለመበታተንና ለማፍረስ በተነሱት ቡድኖችና የውጭ አጋሮቻቸው አማራው እንደ ሃይማኖት ተቋማቱ ለኢትዮጵያ የጀርባ አጥንት ነው፤መጥፋትም አለበት ተብሎ የተፈረደበት።አማራ የኦርቶዶክስና የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ብቻ ሳይሆን የካቶሊክና የፕሮቴሳንትም እምነቶች ተከታይ ነው።አማራውን ለማጥፋት ሲነሱ የነዚህንም እምነቶች  ተከታይ የሆነውን  ለማጥፋት ተነስተዋል ማለት ነው።

የኦነግ ኦሕዴድ አብዛኛው አባልና ደጋፊ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ መሆኑ አይካድም።ኦነግ ኦሕዴድ አማራውንና ሙስሊሙን ብቻ የሚያጠፋ መስሎ ከታዬውና ሃሌ ሉያና አሜን እያለ ካጨበጨበ በራሱ እምነት ተከታይም ላይ የሚፈጸመውን ግፍና  በደል ደጋፊና አበረታታች ሆኗል ማለት ነው።ይህ ደግሞ ከእውነተኛ  የፕሮቴስታንት እምነትና አስተምሮ ያፈነገጠና ሰይጣናዊ ምግባር የተጠናወተው አምልኮ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአገር ወዳድነት ስሜት በጠፋበትና ክህደት በበዛበት አገር ጠንካራ ኢኮኖሚና ማህበረሰብ መገንባት አይቻልም!

ለዓመታት ሲካሄድ የቆዬውን አገርን የማፈራረስ ሴራ ከአምስት ዓመት ወዲህ በማጭበርበር  ሥልጣኑን የተቆጣጠረው  የአብይ አህመድ  አሊ ቡድን የሚመራው የኦነግ ክንፍ በኦርቶዶክስ ተዋህዶና በእስልምና የእምነት ተቋማት ላይ የሚያደርገው ድፍረትና እብሪት የተመላበት ድርጊት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ገደቡን አልፎ በመምጣቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከዳር በነቂስ ወጥቶ በአገር ውስጥና በውጭ አገር ተቃውሞውን በመግለጽ ላይ ነው።የእምነት በተለይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አባቶችና ምእመናን ግንባር ቀደሙን ትግል በመምራት የመስዋእትነት ጽዋን ለመቅመስ ተሰልፈዋል፣ገና ከጅምሩም በመቶ የሚቆጠሩ ወጣቶችና ምእመናን አዛውንቶች የህይወት ዋጋ በመክፈል የሰማእታትነት ክብር ተቀዳጅተዋል።ሌላውም በነሱ ጎዳና ለመጓዝ ቆርጦ ተነስቷል።ላይመለስ ቃል ገብቷል።ይህ ቁርጠኝነትና አብሮነት የሌሎች አገራትን የመንግሥትና የእምነት ተቋማትን ድጋፍና አብሮነት ለመጋበዝ በቅቷል።የሩስያ፣የሕንድ፣የአርመን፣የግብጽና የኤርትራ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያናት ግንባር ቀደሞቹ ናቸው።ይህንን ተከትሎ በአዲስ አበባ የሚገኙት የውጭ አገር  የመንግሥትና የዲፕሎማሲ ተጠሪዎች ለአብይ አህመድ መንግሥት ማስጠንቀቂያና ምክር በመስጠት ዝምታቸውን ሰብረዋል።ይህ ሁሉ ሊሆን የቻለው ሕዝቡ በጽናትና በአንድነት በመቆሙ ነው።እስከዛሬ ድረስ ድምጻቸውን ያላሰሙት ችግሩን ሳያውቁት ቀርተው ሳይሆን የሕዝቡን አለመሰባሰብና ብርቱ ተቃውሞ አለማድረጉን በመመልከት ነበር።መቼም ምዕራባውያን የሕዝብን ስሜትና ጥንካሬ፣እዬተከታተሉ ፣የመንግሥትንም ሁኔታ እዬመዘኑ አቋማቸውን እንደሚቀያይሩ ግልጽ ነው።አብይን አቅፈው፣ ደግፈው፣አሰልጥነው ለሥልጣን እንዳበቁት ከዚያም በተረፈ የፖለቲካ፣የዲፕሎማሲና የገንዘብ ድጋፍ እያደረጉለት መቆዬታቸውን ብናውቅም የአሁኑ ጅዋጅዌ ጨዋታቸውን ቀደም ሲል በምናውቀው እነሱም በማይክዱት መርህ አድርገው የሚመሩበት ‘ቋሚ ወዳጅና ቋሚ ጠላት የለም’ የሚለው እምነታቸው ለአሁኑ የመገለባበጥ አክሮባታቸው  መሠረት እንደሆነ ስለሚታወቅ ሊገርመን አይገባም።የአብይ ቡድን ከውድቀት ካንሰራራ ወይም ተወግዶ  ጠንክሮ ከሚወጣው ጋር አብሮ ላለመሰለፍ ይሉኝታ አያግዳቸውም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  መጪው የኢትዮጵያ አገር አቀፍ እና የወረዳ ምክር ቤት ምርጫ ማስተላለፍ እና የሽግግር መንግስት ማቋቋም ሃሳብ ለማቅረብ

የኦነግ ኦሮሙማው የአብይ ቡድን መሠረቱ ከተናጋ ፊታቸውን ለጊዜውም ቢሆን ወደሕዝቡ ቢመልሱ ሊደንቀን አይገባም።መጠንቀቅ ያለብን ዋናው ጉዳይ የነሱን ጥቅምና ፍላጎት የሚያስከብር፣የሕዝቡንና ያገራችንን ልዑላዊነትና ነጻነት አሳልፎ የሚሰጥ፣ባርያ የሆነ ተረኛ ቡድን እንዳይመጣብን ነው።

በተለይም የሩስያ ከሁሉም ቀድማ በአካል መልእክተኛ ልካ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ መቆሟን መግለጿ እነሱን ያጋለጣቸው ብቻም ሳይሆን ተቀባይነታቸውን የሚያሳጣ ሆኖ ስላገኙት የሚያደርጉት ውድድር እንደሆነም መዘንጋት አይኖርብንም።ማመን የዴሞክራሲ መብት ነው።አማኝን መግደል ዴሞክራሲን መግደል ማለት ነው።ለዴሞክራሲ እቆማለሁ ያለ አማኞች ሲገደሉና ወከባ ሲደርስባቸው ለምን ብሎ መጠዬቅና መቃወም የዴሞክራሲ ብቻ ሳይሆን የሰብአዊነት መገለጫ ነው።

ሌላው ጉዳይ ትግሉ ለኦርቶዶክስና ለእስልምና የእምነት ተቋማት ብቻ ሳይሆን አገር የማዳንም ትግል እንደሆነ ማሰብ ይገባል።ቤተእምነቶች ያለአገርና ምዕመናን ባዶ ቤቶች ናቸው፤አገርም ያለሕዝብ ባዶ መሬት ናት።ስለሆነም ትግሉ የሕዝቡንም ደህንነት ሊዘነጋው አይገባም።አሁን ተጠናክሮ የመጣው ሕዝባዊ ቁጣ በእምነት ተቋማቱ ዙሪያ ብቻ ሳይሆን በምእመናኑ ላይ በተለይም  በአማራው ላይ ያለውንም ማካተት ይኖርበታል። በሃይማኖት ትግል ወይም በሲኖዶሱ ጥያቄ ብቻ ላይ ተወስኖና ተሸፍኖ እንዳይቀር ሁሉም ሊያስብበት ይገባል።አሁንም አማራው እዬተጨፈጨፈ ነው።ህወሃትያውያኑና ኦነጋውያኑ  ትኩረቱ በቤተእምነቱ ዙሪያ ብቻ ላይ ነው በማለት ዋቢና ጠበቃ ያጣ ፣የተረሳ የመሰላቸውን አማራውን እያረዱት ነው።ስለሆነም ቤተእምነቶቹ የሕዝቡን የመኖር ያለመኖር ጥያቄ ከተቋማቸው  መኖር ያለመኖር ጥያቄ ጎን ሊያዩት ይገባል። የአማራው መጨፍጨፍ ከቤተእምነቶች ውድመት ተነጥሎ አይታይም። በመለስተኛ ድል  እረክተው ከወንጀለኛው ቡድን ጋር መደራደር ማለት ደማቸውን ባፈሰሱት ወጣትና አዛውንት ምእመናን ደም ላይ መረማመድ ማለት ነው።ለዘaqi ሰላምና ነጻነትም ኢone ለዘለዓለማዊ ባርነት እጅ መስጠት ማለት ነው።ስለሆነም የእምነት አባቶች ባያደርጉት ይሻላል።እንጓዝበታለን ያሉትን የቀራኒዎን መንገድ ይከተሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  [የለንደኗ ጽዮን ማርያም ቤ/ክ ጉዳይ] - ትግላችን ከሕወአትና ከግብረ-ዐበሮቹ ጋር ነው!

አሁን አጋጣሚውን በመጠቀም ወያኔና ኦነግ በያቅጣጫው ሃይላቸውን አጠናክረው የጥፋት ዘመቻቸውን ተያይዘውታል።ይህ  ችላ ሳይባል የትግሉ አካልና ዓላማ ሊሆን ይገባል። እስከዛሬ ድረስ ድምጻቸውን አጥፍተው የኖሩትና  አሁን  ላይ ለኦርቶዶክስ ተዋህዶ አንገቴን እሰጣለሁ ብለው የተነሱት የኪነት ባለሙያዎችና ምሁራን ለሰው ልጅ ለሆነው፣ኢትዮጵያዊ ወገናቸው ሁሉ  በተለይም ለአማራው ተወላጅ  አጋርነታቸውን  “እኔም አማራ ነኝ !”  በሚለው መፈክር መግለጽ ይኖርባቸዋል።የትግል ግማሽ የለውምና!

የወንጀሉ ሁሉ ተጠያቂ የሆነውን በሥልጣን ላይ ያለውን ጸረ አገርና  ጸረ ሕዝብ ቡድን እንደ መንግሥት ቆጥሮ፣ እውቅና ሰጥቶ ጥያቄ ማቅረብ ትክክል አይደለም።የሚመራበትንም የጥፋት ሰነድ ሕገ መንግሥት ብሎ በመቀበል እዬጠቀሱ መከራከርና ይከበር ማለት ሥርዓቱን አምኖ መቀበል ማለት ነው።ትግሉ እስከ ስርዓቱ ፍጻሜ ድረስ መዝለቅ አለበት።የካንሰርን በሽታ ቀርጠው በመጣል እንጂ በዳበሳ አያድኑትም!የዘር ፖለቲካም ከካንሰር የከፋ በሽታ ነው፤በእርቅና በድርድር አያሻሽሉትም።

ሁለገቡ ትግል ይቀጣጠል! የአማራው የመኖር ጥያቄ የኦርቶዶክስና የእስልምና ተቋማት የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ ነው!!

አገሬ አዲስ

 

 

 

2 Comments

  1. ሰቆቃወ ደጋፊ
    አወይ ፍቅር እውሩ
    አመካኘሁለት እኔ ለነውሩ
    ሰበብ ፈጠርኩለት
    ለመቶ ጉድለቱ
    ሀገርን ቢያወድምም
    ሰበብ ፈጠርኩለት አሁንም ቅድምም
    እሱ አይደለም አልሁኝ
    ባይሰማ ነው አልሁኝ
    ሳይልከኝ ተላክሁኝ።
    ዓይኔን ግንባር ያርገው እያልኩም ዋሸሁኝ
    ዛሬ ራሱ ወጥቶ
    ቀንድና ጥፍሩ በግልጽ እየታየ
    አበደለት ለየ
    የክፋቱ አለቃ የተንኮሉ ጠንሳሽ መሆኑን አሳየ
    የሸፋፈንኩለት መጋረጃ ገልጦ እኔን አጋለጠኝ
    ወዮ ምን ይዋጠኝ!
    ወዮ ጉድ አረገኝ!
    ቸሩ ፈጣሪዬ! ምናለበት ባገኝ?
    ድል ሳይነሳኝ ሃፍረት
    “ይቅር በለኝ ወገን / ማሪኝ እናት ሀገር/ “ የምልበት ድፍረት።
    “የለበትም” እያልሁ ሙግቴን ሳሰማ
    በእሳት የወደመው ያ ሁሉ ከተማ
    አንድ ሚሊዮን ነፍሳት
    የተገበራችሁ ለአውሬው ዙፋን ጽናት
    ሁለት ሚልዮን አማራ
    የተነቀላችሁ ከጎጆ ከአዝመራ
    70 ቢልዮን ዶላር
    የተመዘበረው የሀገር አንጡራ
    ያ ሁሉ ያ ሁሉ
    የተሰራ ወንጀል አምስት አመት ሙሉ
    እኔም አለሁበት እንቅፋት በመሆን ወገኔ ተባብሮ
    የጭቆናን ቀንበር የዝርፊያውን ወጥመድ እንዳይጥለው ሰብሮ
    እና ይቅር በሉኝ ማለት ብፈልግም ተጸጽቼ ከልብ
    የውድመቱ ግዝፈት የእልቂቱ ብዛት ሆኖብኛል ኖራ ሃሞት የሚሰልብ።

  2. ዛሬ እዚህም እዚያም ከሚረገጥ የትኩረቱ መስሂብ ዘርፉ ላይ ሳይሆን አገር የማዳን ተልእኮው አብይን ማውረድ ብቻ መሆን አለበት።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share