” ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዛብሔር ዘርግታለች ፣ ሤጣናትም በፈጣሪያችን ቁጣ ይመታሉ ።  ይላል የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ። “

ሲና ዘ ሙሴ

የዛሬዎች የኢትዮጵያ ገዢዎች ከቀድሞዎቹ ያልተማሩ በመሆኑ ፣ በዚህ በ11ኛው ሰዓት ለመማር ና ከዘረኝነት አስተሳሰብ ተመልሰው ፣ ዓለማቀፋዊ ህሳቤን በመንግስታቸው ውስጥ ካላነበሩ ፣ ፍፃሚያቸው ከቀኃሥ ፣ ከደርግ እና ከህወሓት ውድቀት እጅግ የከፋ ይሆናል ።

ቀኃሥ (   ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ) ” ዙፋኑን እና መንግሥታዊ ሥርዓትን አጣምሬ የህዝብን ነፃ አእምሮ ተቆጣጥሬ ፤  አገርን  ከሰማይ በታች አስተዳድራለሁ ። ወይም  ገዝቼ ዘለዓለሜን እኖራለሁ ።  ” በሚል ገደብ  በሌለው የሥልጣን ጥማት ፣ እስከ እርጅና ዘመናቸው   ” ሰልጣን ወይም ሞት ! ” ብለው ሲንገዛገዙ ፣  60 ባለስልጣናቶቻቸውን ( በውስጣቸው ታላላቅ ምሁራን አሉበት ።) በሐሰተኛ ዘዴ ጠርተው  ካሰራቸው በኋላ ፣ እዛው እስር ቤት ውስጥ እንዲረሸኑ አደረጉ ። እራሳቸው ቀኃሥ በትራሰሰ ታፍነው ወይም ታንቀው ተገደሉ ።  ከንጉሱ ና ሹመኞቻቸው  ውጪ ደርግ በእጅ ብልጫ ና በነፃ እርምጃ  ሞት የፈረደባቸው በሺዎች የሚቆጠሩ መሆናቸውን ታሪክ ዘግቦታል ።

ደርግ ከጅምሩ ፣ ለሚሊቴሪው ጥቅም የተቋቋመ የወታደራዊ ኃይል ስብስብ ቢሆንም ፣ በህቡና በግልፅ የተቀላቀሉት ምሁራን ፣ የደርግን የጥቅም ጥያቄ ወደ ” ዙፋን ግልበጣ ” አሸጋገሩት ።

” ቁማር ጫዎታ ተጫውቼ

አጨብጭቤ ወጣሁ ተበልቼ ።

ምንኛ ዕድሌ በሰመረ

ዘውዱን ገልብጨው በነበረ ። ”

በምሁራን ደጋፊነት  ዘውዱ ተገለበጠ ። ቁማሩ በደርግ ተበላ ። ዘውድ የመገልበጥ ቁጭት ተሳካ ። …

እናም ኢትዮጵያችን በማሌ  ማርክሲዝም ና ሌኒንኢዝም  ሪዮት መምራት ጀመረች ። ብዙ በስሜት የተነዱ ተግባራት ብቻ ሣይሆኑ ከፍተኛ የልማት ተግባራትም  በአሥራሰባት ዓመት ያልተቋረጠ ጦርነት ውስጥ ደርግ ቢያከናውንም ምስጋና አላገኘም ። በ17 ዓመቱ  በአሜሪካኖች ቀተቀነባበረ ሤራ ተገፋ ። መንጌ ወደ ዙምባብዌ ወታደራዊ ተሰደዱ ። የደርግ መንግስት ተንኮታኮተ ።

…የደርግ መንኮታኮት ፣ ትልቁ ሰበብ የሰሻሊዝም ካምፕ መፈረስ ነው ። ዕድሜ ለጎርቫቾቭ ። ሶቬት ህብረትን 17 ቦታ ሲያሸነሽኗት  ፣ ጎን ለጎን  የወደፊት የኢትዮጵያ 77 ቦታ ሽንሸና ንድፍ እየተሰራ ነበር ። በአሜሪካና በአውሮፓ ቱጃሮች ። ደርግ እንደ ዋዛ ከግዙፉ ጦር ሠራዊታችን ጋር   ተንኮታኮተ ።  የጠላቶቻችንን አንጀት ራሰ ። አርበኞቹ ኢትዮጵያውያን እርር ጭስስ አሉ ።

በደርግ እግር የገበሬው ጦር የወያኔ ሠራዊት ቤተመንግሥቱን ተቆጣጠረ ። መንግስቱ ወደ ሐራሬ ሂዶል ሲባልም ፣ ” በየት አቅጣጫ ነው ፤ መንገዱን አሳዩን ። አንገቱን አንቀን ይዘን ፣ ለፍርድ እናቀርበዋለን ። ”  በማለት  ጦር የአራት ኪሎን ነዋሪን  የሐራሬውን መንገድ አሳዩን ሲል ጠየቀ ።

ውሎ ሲያድር ፣ ኋላቀር አስተሳሰቡን ፣ አመለካከቱን ና ድርጊቱን በዘመናዊነት ለመቀየር ጣረ ። እናም ጀግናው ፣ የኢህአዴግ  ሠራዊት የሽግግር መንግሥት አቋቁሞ ፣ ለጥቂት የጥቅም ተጋሪዎች ገነት የመሰለች አገርን ፣ ለብዙሃኑ የኢትዮጵያ ህዝብ  የችግርና የችጋር አገርን ለመገንባት ፣ በብርቱ መጣርን ” ሀ ” ብሎ በ1983 ጀመረ ። ” አንድነት ፣ ፍቅር ፣ መተሳሰብ ፣ ሰው የእኔ ብጤነው ማለትን ፤ ህግን ማክበርና ማስከበር ፣ ጨዋነት ፣ አኩሪው የቤተሰብ ባህል ፣ ጡርን የመፍራት ወይም የልተገባ ነውረኛ ድርጊት በማንም ሰው ላይ ያለመፈፀም ። ወዘተ ። ” ከህዝብ ህሊና እንዲፋቅ ፣ ሰውን በጥርነፋ ( በአንድ ለአምሥት ) እርስ በእርሱ እንዲሳለል በማድረግ የአንድ ክልልን  ህዝብ ከአንድ ፋብሪካ የወጣ የኮካ ጠርሙስ እንዲመስል  በቋንቋና በጎሣ ፋብሪካ ውስጥ አስተሳሰብ እና አመለካከቱ እንዲቀየር በብርቱ ጣረ ።

ተጠራጣሪነትን ፣ ሥግብግብነትን ፣ መከፋፈልን ፣ ዘር መቁጠርን ፣ በጎሣ ማመንን ፣ ቆዳ ማዋደድን ፣ ቋንቋን አምላክ ማድረግን ፣ ” እኔ ሰው ነኝ ። ሌላው ከትል ያነሰ ፍጥረት ነው ። ይኼ የእኔ መሬት ነው ። ሌላው መጤ ነው ።… ” የሚል ህሳቤን የሚያዳብር እና የሚያነበር የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ሥርዓትንም ገነባ ። ልማታዊ እና ኪራይ ሰብሳቢ በሚሉ ቃላት ማደናገር እንደጀመረ ግን ሥልጣኑ አከተመ ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  መርዶ በሞንታርቦ፡ የህወኃት ትሩፋት - በደሳለኝ ቢራራ

ራሱ ኪራይ ሰብሳቢና ራሱ ኢ – ልማታዊ ሥራ እንደሚከውን ተረጋግጦ   ለ27 ዓመት  ከገዛበት ወንበሩ ህውሓት ኢህአዴግ ተሽቀነጠረ ።

የኢትዮጵያ ህዝብ ” አገዛዙ በቀኛ ! ህገ አራዊት አገዛዝ ይውደም ! ”  ብሎ ለለውጥ  ተነሣ ።   ኢህአዴግ በህዝብ በመጠላቱ  እና የቀደመ   ድጋፉ በመመናመኑ ፣ እንዲሁም ዋልታ ረገጡ ፣ የአክራሪ ና የጎሰኞች   ተቃውሞ እያየለ በመምጣቱ በመንግሥት ውሥጥ ሹክቻ ተፈጠረ ። የኢህአዴግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ መንግስት   ለሁለት እና ለሦስት ተሰነጠቀ ። በዋነኝነት የተሰነጠቀው የግንባሮቹ  ” መሪ  ግንባር ” ህውሃት  ነው ። እናም ” ህውሃት የመሰዋት በግ ” ሆነ ።

ህውሃት ተሰዋ ። ከመሪነት ወረደ  ።  አራቱ ግንባሮች በኦሆዴድ ዋና ተዋናይነት የኢትዮጵያን ህዝብ በቅንነት በማገልገል ለዴሞክራሲያዊ ለውጥ እናበቃዋለን አሉ  ። ጠ/ሚ እንዲሆኗቸው  አብይ አህመድን ( ዶ/ር ) ሊቀመንበራቸውና ጠ/ሚ አደረጓቸው ።

እሳቸውም   እኛ ነበርን አሸባሪ ከእንግዲህ ሣናጣራ አናስርም ። ቶርቸር አንፈፅምም ። የማሰቃያ ካፕ አንገነባም ። ወዘተ ። ” መግለጫ ሰጡ ። …

ከዛስ ፣ ከዛማ ፣ ሰነባብተው ፣ ጠ/ሚሩ በራሳቸው መንገድ ” ብልፅግና ” የተሰኘ ፓርቲ መሠረቱ ። በፓርቲው ምሥረታና ሂደት የነበረውን ድራማ ፣ ብዙ ስለተባለበት  ለታሪክ እንተወው ።

ዛሬ ብልፅግና በምናብ ደረጃ እንጂ በኢትዮጵያ ምድር   በተግባር እንደሌለ  እያየን ነው ።

ያለው ብልፅግና ሳይሆን የብልግና ሥርዓት ነው ። በዓለማዊ ነገሮች ፣ በፖለቲካ ጉዳዮች ፣ ጥንብ በሆነው ዘረኝነት  ሰበብ ፣ ኢትዮጵያዊያን ከቀደመው ኢህአዴግ በባሰ መልኩ ፣ ከንቱ መሰዋትነት እንዲከፍሉ ያደረገው ብልፅግና የተሰኘ ፓርቲ ነው ። ዛሬ ደግሞ መላው የኦርቶዶክስ ምዕመናንን ለማጋጨት በመንፈሳዊ ቤት ውስጥ ሤጣናዊውን ዘር ለማብቀል  ቆርጦ ተነስቷል ። ሰውነት እንዲጠፋ እና ጥንቡ ዘረኝነት እንዲፋፋ እና ህዝብ እርስ በእርሱ እንዲጫረስ መንገድ እየጠረገ ነው ።

ይኽንን ዳቢሎሳዊ ድርጊት ፣  ከአክሱም እሰከ ሞያሌ፤ ከሙስታሂል እስከ ጉባ ። ከጨው ባህር እሰከ ዳሎል  … ። ከኦጋዴን እስከ መተከል። ከቦንጋ እሰከ ወለጋ ። …ከአዲስ አበባ እሰከ ድሬደዋ ።  ከጅማ እሰከ ቴፒ ። ከአርባምንጭ እሰከ ጎጀብ ። ከባህር ዳር እሰከ ሑመራ ። ወዘተ ። ያለ የኦርቶዶክስ አብያተ ቤተክርስቲያን ምዕመን ሁሉ ተቃውመውታል ።  የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አባቶችም ጥንብ በሆነው ዘረኝነት ኃይማኖትን  ለመክፈል የተደረገውን ጥረትን አውግዘዋል ።  ቅዱስ ሲኗዶስም መንግስት መራሹን የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ደም ሥር ቆራጩን ” የኃይማኖት ፖለቲከኞችን ” ስብስብ ወደ አቶነት አውርዷል ። የሚከተላቸውንም አውግዟል  ። በዚህም ህዝበ ክርስቲያኑ በእጅጉ ተደስቷል ።…

የህዝበ ክርስቲያኑ ደስታ ግን ዘላቂ አልሆነም ።  ሤጣን ይኽቺን በአንድነቷና በአቃፊነቷ የምትታወቀውን ፣ ለጎሣና ለነገድ ደንታ የሌላትን ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ማፈራረስና ህዝቡ በእምነቱ ተስፋ እንዲቆርጥ  ማድረጉን በጠብመንጃ እየተገዘ ቀጥሏል ። ይኽ ጠመንጃ የያዘ ኃይል  እየተባበረ ያለው ከቅዱስ መንፈስ ጋር ያለመሆኑንን ህዝበ ክርስቲያኑ አውቋል ። የመነኮሱ ፣ ዓለምን የተለዩ ቅዱስ ግለሰቦች የመሳሪያ እጀባ አያስፈለጋቸውም ። ከኒኩለር እጅግ በጣም የሚበልጥ ኃይል ያለው እግዚአብሔር ጠባቂያቸው መሆኑንን አሳምረው ያውቃሉና ። …

ይኽንን ክፉ ፣ አሳፋሪ ድርጊትን በህዝበ ክርስቲያኑ ላይ እየፈፀመ የሚገኘውን ፣ የሤጣን ሠራዊት   ፈጣሪያችን  በቅርቡ እንደሚቀጣው አምናለሁ  ። የዚህ እኩይ  ሠራዊት  ተባባሪዎችም ፣ ዘግናኝ ቅጣቱ አይቀርላቸውም ።

ህዝብ የሰጣቸውን የማገልገል ሥልጣን በተገቢው መንገድ ሣይጠቀሙበት በመቅረት የቤተክርስቲያን አባቶችን እንዲሰቃዩ ያደረጉት ሁሉ ፣ ተገቢውን ቅጣት በቅርቡ እንደሚያገኙ አልጠራጠርም ። አገርን እና መንግስትን በፈጣሪ ፈቃድ ፣ በታላቅ እምነትና ፀሎት  ያቆየች ፣ ጥንታዊት ኦርቶዶክሳዊ ቤተክርስቲያን  ከፍሎ ፣ ለራሱ የክፋት ዓላማ ሁለት ፖትርያርክ መመስረት ፣ መንግስት   አገርን ለማፍረስ ቆርጦ መነሳቱን  ያመለክታል ። ” ሆሆ !!ዴድ !! ሸኔ  ! አበልፃጊው  ! ” ( እየዘረፉ ፣ እየገፈፉ ፤ እያፈኑ እና ከሚሊዮን እሰከ 200ሺ እየተቀበሉ የበለፀጉ ዕድሜ ለአብልፃጊው መንግስታችን ስለሚሉ  ነው ፣ አበልፃጊው የተባለው ፣ ብልፅግና ። )   መንግስት ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሕዝበ ክርስቲያን በጰራቅሊጦስ መንገድ ሲሄዱ፤ ፓትርያርክ፤ ሊቃነ ጳጳሳት፤ መነኮሳትና ቀሳውስት በሳጥናኤል መንገድ ነጎዱ (ከቀሲስ አስተርአየ ጽጌ)

“ሆሆ !!ዴድ !! ” እነዚህ የተወገዙ እና አቶ የተባሉ ግለሰቦችን አክብሮ ሆቴል እስቀምጦ በመቀለብና  በጠመንጃ በማስጠበቀ ፣ ህዝበ ምዕመኑን የተወገዙ ተራ ሰዎች መሰቀል እንዲያሳልሟቸው ፤  የእምነት አባቶች እንዲሆኑት ወደ አድባራቱ በአጀብ መውሰድ ፣ ለፈጣሪያችን ለእግዛብሔር ስድብ ነው  ። እናም ይኽቺን የተቀደሰች ቤተክርስቲያን ማፍረስ እንደማይቻል በማይመረመር ችሎታና ኃይሉ ያሳያቸዋል ።

ይኽቺ ቤተክርስቲያን ፈረሰች ማለት አገር ፈረሰች ማለት ነው ። በበኩሌ ይኽ መላቅዱሱ የጠፋበት መንግስት ” በሬ ካራጁ እንደሚውል ዓይነት አደገኛ ጫዎታ  ሥለሚጫወት ከአገራችን በፊት የሚፈርሰው እራሱ ነው ።

በተቋም ደረጃ ያለን አማኝ ሁሉ ፣ በሆሆ ዴድነት ጨፍልቄ ፣ ያንን ትንታግ መከላከያ ሠራዊት ሳይቀር  ፣    እሳት የታጠቀውን ሁሉ ፤ ብዙሃኑንን   ኦርትዶክሳዊ ፣  በሆሆዴድነቴ  ፣ ” በቡድን ሃሳብ  ብቻ እቆጣጠረዋለሁ ። ” ብሎ የሚያስብ ከሆነ ፣ በዘግናኝ ሁኔታ የሚፈርሰው ፣ የሚነደው ፣ የሚቃጠለው  የመንግስትን ስልጣን የያዘው እና ግብረ አበሩ ሁሉ ይሆናል ።

ዛሬ መንግስትና ህዝብ ሆድና ጀርባ ናቸው ። የቱንም ያህል ኢህአዴግአዊ / አንድ ለአምስት ካድሬአዊ ስብከት በካድሬ ደረጃ ፣ አበል እየተከፈለ ቢያካሂድ ብልፅግና የህዝብን ልብ ወደራሱ መመለስ ከቶም አይችልም ።

ከእንግዲህ ባለሥልጣናት ( ቁርስ ፣ እራት ምሳችሁ ከባለአምስት ኮኮብ ሆቴል የሆነ ፣  እርስ በእርሳችሁ  ትጫረሳላችሁ እንጂ ህዝብ ለእናንተ ለግብዞች ሥልጣን ሲል በሞኝነት ፣ በየዋህነት ፣ በጅልና በጅላፎነት  አያልቅም ። ) እወቁ ፣ የትም ክልል ውስጥ ያለ ህዝብ የእምነቱን ነፃነት ፣ በገዛ እጁ ለማግኘት  እንደሚንቀሳቀስ እወቁት ።  …

ሰው እኮ የፈጣሪ ሥራ ነው ። የማያምን ፣ ፀረ እግዚአብሔር ሁሉ ፣ ይኸንን እውነት ከወዲሁ ይገንዘብ ። በግል የማሰብ ችሎታ ምን እንደሆነ የዘነጋም ፣  ከነ ጀነራል ሠዓረ አሳዛኝ አሟሟት ቀጥተኛ መልዕክቴን ይረዳ ።

እያንዳንድሽ ከኢንጅነር ሥመኘው እስከ አምባቸው መኮንን እና ጀነራል አሳምነው ድረስ ብቻ ሣይሆን ፣ በሥልጣነ ዘመንሽ በፈሰሰው የንፁሐን ደም በፈጣሪ ፊት  ተጠያቂ ነሽ ። በሰው ላይ ጨለማን ተግን አድርገሽ  ግፍ ስትሰሪ ያየ ዓምላክ ” እንዲሁ አፉ ይለኛል ፣ ባላየ ላሽ ይላል ” ብለሽ በእምነተ ቢስነት አትገበዢ ። ዘግናኝ ፍፃሜሽ በደጅሽ ነው ።

ልብ በሉ እኔ እያስፈራራሁ አይደለሁም ። እኔ እንደ ” ሲናው ሙሴ የፈጣሪ መልዕክተኛ ነኝ ። ” የታጠቀ ዜጋ አእምሮ ያለው መሆኑንን በቅንነት ላሳስብህ ነው ።  ከአባትና ከእናት መወለዱን እና ዘመደ ብዙ መሆኑንም ፈፅሞ  መርሳት የለብህም ። ጠመንጃ እንደያዝና በጠመንጃው ምን ማድረግ እንደሚችል ተረዳ ። በአእምሮው ጎዳ ሁሌም የሚያብሰለሰለው አንተን የኢትዮጵያ መሪ ስለሆንክ አንተን  ስለመታደግ ፣ ስለአንተ ሲል ህይወቱን ስለመስጠት ብቻ አይደለም የሚያስበው  ። ከዜጎች ፣ ከአባቶቹ ፣ ከእናቶቹ ፣ ከወንድሞቹ ፣ ከእህቶቹ  ዘወትር በሚሰማው ብሶት የተነሳ ፣ አንድ ቀን ፣ ” ይህ ነው የህዝቤ አንድነት ነቀርሳ ፣ ለምን እሱን ወደ ሲዖል ሸኝቼ ሥሜን በታሪክ አሥጠርቼ አላልፍም ? ሞት እንደሆን ለሁላችንም የማትቀር ፀዋ ናት ። ” ብሎ ቃታውን ሊስበብህ ይችላል ። የሰውን አእምሮ እንደ ግልህ ሮቦት ልትቆጣጠረው አትችልምና  !

ተጨማሪ ያንብቡ:  የመደብ ወይስ የብሄር ጭቆና?! (ከአብርሃ ደስታ)

መቆጣጠር የምትችለው ፣ ግኡዛኑን የቅስቀሣ ና የፕሮፓጋንዳ መሣሪያዎችህን እና ቱሉትላ ወይም ለፍላፊ ዶሮ የሆኑ ካድሬዎችህን ብቻ ነው ። ” እንደአንተ ምሳ ሳትበሉ የምሳችሁን  ቆጥቡ ። ለማለት ወደኋላ አይሉምና ! ምሳ ሁሌም የሚያበላ ደሞዝ ነው እንዴ መምህሩ ሲጀመር ያለው ? ዛሬ አንድ ሽሮ ፣ በደረቅ እንጀራ  ስንት ነው ?  … ። ጉሮሮው ለሚነድ አስተማሪ አንድ ሌትር  ውሃ ለአራት ፔሬድ ይበቃዋልን ? አንተ እዚህ ተማሪ ወደቀ ። ሾቀ ። ትላለህ የሾቀ አስተማሪ የሾቀ ተማሪ ነው የሚያመርትለህ ። አሥተማሪነት ላብህን ብቻ የምታንቆረቁርበት ሙያ አይደለም ። የዘወትር የአእምሮ ትጋትን እና ጤነኛ አእምሮን ይጠይቃል ።

ይኽን መሠፈርት የሚያሞሉ የበቁ ፣ በእውቀታቸው የማይታሙ ሥንቶች ናቸው ? ከግማሽ በላይ ከተማሪው ያነሰ ዕውቀት ያላቸው አስተማሪ ተብለውልናል ። በቋንቋ አጥር አይደለም እንዴ ምድረ ማይም በኦሮሚያ የመንግስት ትምህርት ቤቶች ማይምነትን እያስተማሩ ያሉት  ። ማትስ ፣ ኬሚስቲሪ፣ ባዮሎጂ ፣ ሂስትሪ ፣ ኢኮኖሚክስ ወዘተ። ድብልቅ ቋንቋ የሚናገሩ ልጆችን ( ተማሪዎችን ) ለማስተማር የግድ ኦሮምኛ ማወቅ የቅጥር መስፈርት በመሆኑ ቋንቋውን እንደ ፒኤችዲ በመቁጠር በዜጎች ላይ ጢባጢቤ ይጫወታሉ ። ። እልም ያለው መሃይም በጮርቃዎቻችን ላይ እንዲቀልድ  በአስተማሪነት እንዲቀጠር ሽፋን የሰጠው ይኼ ጥንብ የሆነ ዘረኛ ሥርዓት አይደለም እንዴ ?

ወዳጄ ቀልድህን አቁም ። ምን ያልጨመረ ነገር አለ በኢትዮጵያ ? ርካሽ የተባለው ሙዝ እንኳን አንዱ 10 ብር ሆኗል  ። ከአምስት ብር ወደ አሥር ብር ማደግ ማለት ምንማለት ነው ? ኢኮኖሚስቶችን ጠይቅ ።

ወዳጄ  የቴሌቪዥን  ጣቢያዎችህን በፈለከው መንገድ በውሸት ሰበካ ፣ ለእኩይና ሠናይ ፍላጎቶችህ መገልገያ ልታድርጋቸው ትችላለህ ። ሆኖም ነፍስ ያላቸው ማሰብ የሚችሉ ሰዎችን ሁሌም ከእኔጋር በባርነት ይኖራሉ ብለህ እንደ ግኡዝ ካሰብክ ተሳስተሃል ። በውድም ሆነ በግድ ፣ መንግስት ስለሆንክ ብቻ  ምሁራንንም ሆነ ማይማንን ፣ በአውቅልሃለሁ እና  በአውቃለሁ ባይነት  ልታወራቸው ፣ ጥያቄያቸውን ፣ በመምህር አብራራውነት ልትመልስላቸው   ፤ አይንህን በማጉረጠርጥ ፣ እጅህን በማወናጨፍ ፣ የነኤዞፕን ተረት ልተርት እና ከአለቃ ገብርሃነ እበልጣለሁ ልትላቸው ትችላለህ ። እነሱም በህሊናቸው እየሰደቡህ ወይም አድናቆት እየቸሩህ ሊያዳምጡህ ይችላሉ ። ሆኖም ማወቅ ያለብህ እንደመንግስት የሰራኸው ፣ የህዝብን ሰላም እና ፀጥታ የማስከበር አንዳችም ተጨባጭ ሥራ ባለመኖሩ በህዝብ ልብ ውስጥ ከመንግስትነት ወርደሃል ።

የኢትዮጵያ መንግስት ምድር ላይ በተግባር የለም ። ያለው የትግሬ ፣ የኦሮሞ የአማራ ፣ የሶማሌ ፣ የጋምቤላ ፣ የሲዳማ ፣ ወዘተ ። የሚባል ፣ ከፊደራሉ መንግስትና ከተካዮች ምክር ቤት አቋም ውጪ ህዝብን ቁም ሥቅል የሚያሳይ መንግስት ነው ያለው ። ዛሬም ፣ ቤተሰባቸውን መምራት የማይችሉ ግለሰቦች ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ከፍተኛው አመራር ፣ ህዝብን እንዲያስተዳድሩ ሥልጣን ሰጥተሃቸዋል ። ዛሬ ደግሞ በኃይማኖቱ ጣልቃ በመግባት ከቀኖናው ና ዶግማው ውጪ በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ላይ ሌላ ፓትርያርክ በመሾም ቤተክርስቲያኗን በዓለማዊ መንገድ ለመምራት ቆርጠው የተነሱ አይነኬዎች በሥርህ በቅለዋል ። ዓለማዊ ፀረ ክርስቶሶች በኢትዮጵያ እንዲነግሱ ከለላ እየሰጠሃቸው ነው ። በእግዚአብሔር ሥራ ጣልቃ በመግባት ። ደፋር ነህ ።  ። ይኽ ድፍረትህ  የሚያጣለህ ሰውን ከፈጠረው ዓምላክ  ጋር ነው ። ይኽ ቀጥታ እግዚአብሔርን መዳፈር ነው ።  ይኽ የግብዞች ድፍረት የሚያስከትለው ቁጣ ለፃድቃንም እንደሚተርፍ እወቅ ። … ፈጣሪያችን መድሃኒያለም ሆይ አስበን ።

1 Comment

  1. እኔን የናፈቀኝ የተዘረጉት እጆቿ መቼ መልስ አግኝተው እንደሚወርድ ማየት ነው። ከአንድ የክፋት ከፍታ ወደ ሌላው ከመሸጋገር በስተቀር ምድሪቱ ያገኘችው አንድም ነገር የለም። አሁን ደግሞ ይባስ ተብሎ በሃይማኖት ሳቢያ ያታግሉናል። በየመድረኩ መግለጫውና ጫጫታው ያደነቁራል። በወያኔው ፍልሚያ ሳቢያ የትግራይ ቤ/ክርስቲያን ከጠላቶቻችን ተለይተን የራሳችን አቁመናል እንዳልተባልን ሁሉ አሁን ደግሞ ኦሮሞው በቋንቋዬ ካልሰበኩና ራሴን የኦሮሚያ ጳጳስ ብዬ ካልሾምኩ ሞቼ እገኛለሁ ማለታቸው የሚያስደንቅ ነገር አይደለም። የየክልሉን መሪዎች ፕሬዚደንት እያልን በዘርና በቋንቋ ዙሪያ አጥር የተበጀላት ሽንሽኗ የሃበሻ ምድር መከራዋ ማባሪያ የለውም። ሲጀመር ሰው በመረጠው ቋንቋ ማምለኩ ማለፊያ ነበር። ግን ሴራው በራስ ቋንቋ ማምለኩ ላይ ሳይሆን ከኋላውና ከፊቱ ያስከተለውና የሚያስከትለው የፓለቲካ አሻጥር ነው። መስቀል በአንድ ኪስ በሌላው ሽጉጥ የሚይዙ ስመ ቀሳውስትና ጳጳሳት ድሮም ነበሩ አሁንም አሉ። የዛሬውን የተለዬ የሚያደርገው ሰልፉ በዘርና በቋንቋ መሆኑ ነው።
    ጠ/ሚሩ ሲናገር የትግራይ ቤ/ክ ተገነጠልኩ ሲል ማንም ምንም ያላለ አሁን በቋንቋዬ ላስተምር ሲል ይሄ ሁሉ ጩኸት ለምን ይሆን ይለናል። የማይረዳው ነገር ግን እርሱ ይህን ባለ ቁጥር የኦሮሞ የመገንጠል ፓለቲካ አራማጆች የልብ ልብ እየተሰማቸው ንጽሃንን ያርዳሉ፤ ቤት ያቃጥላሉ፤ ከእምነት በራቀ መልኩ ራሳቸውን ለግንጠላው ያመቻቻሉ። ሴራው በገሃድ የሚታይ ስለሆነ ዓይንና ጀሮ ያለው ሰው በሚያየውና በሚሰማው ነገር ላይ ዓሊ ማለት አይቻለውም። ለኦሮሞ ነጻነትና እኩልነት የሚፋለም ሃይል ንጽሃንን አያርድም። ሃብትና ንብረትን አይዘርፍም። ግን በብሄር ስም ነጻነት እናመጣለን ያሉ ሁሉ ባርነትን እንጂ ነጻነትን አምጥተው አያውቅም። ይህ እውነት ሲፈለግ የሚገኝ እንጂ ከሚያልፍ ወንዝ የተጨለፈ ወሬ አይደለም።
    የሚያሳዝነው ያኔ ሥፍራ እየተቀያየሩ ሲያጋድሉን የነበሩት (ሩሲያና አሜሪካ) አሁን በአፍሪቃ ቀንድ በኩል ማንዣበባቸው የዓለምን የፓለቲካ ሰልፍ ያሳያል እንጂ አፍቃሪ አፍሪቃ ሆነው አይደለም። በቅርቡ የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ምጽዋ ላይ አርፎ አስመራ ላይ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ የተረዳሁት ያው እንደተለመደው በዚህም በዚያም እያሳበቡ እኛ እንድንጫረስ ትራፊ መሳሪያቸውን እየዘረገፉ የዓለም ፓለቲካ ፓለቲካቸው ማጣጫ ሊያረጉን እንጂ ለሰፊው የኤርትራ ህዝብ ከምሲን አይተርፈውም። አሜሪካ፤ ቻይና፤ ሩሲያና ሌሎችም አሁን በአፍሪቃ ላይ የሚያሳዪት ትኩረት ከራሳቸው ሃገር ስትራተጂ ጋር የሚጣጣም የፓለቲካ ሸቀጥ ፍለጋ እንጂ ለጥቁር ህዝብ ነጩ ህዝብ ከልቡ አዝኖና አስቦ አያውቅም። አሁን በኢትዮጵያ ውስጥ የምናየው የፓለቲካ መናወጥም መልኩንና አቅጣጫውን እየለወጠ የሚያጣድፈን ከጀርባ የሚጋልቧቸው ሃይሎች ስላሉ ነው። ልብ ያለው ፓለቲካ አቅጣጫ እንደሌለው ንፋስ መሆኑን መረዳት ይኖርበታል። ዛሬ ክቡር ዓላማ ብለው ሰዎች የተሰውበት ነገ የቋሚ ማላገጫና መሳቂያ ይሆናል። እንሟገት የሚል ካለ እስቲ ንገሩኝ የወያኔና የብልጽግና መፋለም ምን አተረፈ? ደግሞስ በደቡብ አፍሪቃውና በናይሮቢው ስምምነት መሰረት የሰላሙ ስምምነት ተፈጻሚነት ይኖረዋል? በጭራሽ! ይህ እንዳይሳካ ከሥር እሳት የሚለኩሱ እጆች ብዙ ናቸውና።
    ዘምኛለሁ የሚለው ግራ የገባው የምዕራቡ ዓለም ጾታውን እንኳን በውል መናገር አይችልም። ያለ የሌለውን በማኘክ በስጋቸው ታስረው ይህንም ያንንም መድሃኒት ያድናል እየተባሉ እንደ አበባ ቆሎ ክኒን የሚውጡ እልፎች ናቸው። The Paradox of Choice በተሰኘው መጽሃፉ ላይ Barry Schwartz የሚነግረን ብዙው ትንሽ፤ ትንሹ ብዙ እንደሆነ ነው። የቁሳቁስ ዓይነት ምርጫ መብዛት ገቢያተኛን ለማዘናጋት የሚደረግ አንድ የsurveillance capitalism ዋንኛ መሳሪያ ነው። ይህ አዘባራቂው የምዕራባዊያን ገቢያ ምርጫ የሰጠ አስመስሎ የስንቱን ሰው ህይወት ያለልቡ እያስኬደው እንደሆነ ለማየት አይቸግርም። ግን ሰው ደስታውን የሚለካው በምንድን ነው? በቁሳቁስ? መልሱን ለእናተ እተዋለሁ
    በፊትም ሆነ አሁን በሃገራችን በእስልምናም ሆነ በክርስቲያኖች መካከል መከፋፈል እንዲመጣና ፊልሚያ ውስጥ እንዲገቡ የሚያደርጉት የጥፋት እጆች ዛሬም አልታጠፉም። በመሆኑም ጊዜ እያለ ችግሮችን ለይቶ መፍትሄ ከተገኘ መፈለግ እንጂ በሆነ ባልሆነው ከራራይሶ መልስ አያመጣም። የችግሩ መፍትሄ ለመሆን ሁላችንም የምንችለውን እናድርግ። መገዳደል፤ የፓለቲካ ሴራ፤ የዘርና የቋንቋ ፓለቲካ ያብቃ። ለዚህ ደግሞ የወያኔውን ህገ መንግስት መለወጥ የመጀመሪያ ተግባር ይሆናል። ክፉዎችን በመለማመጥ ተንኮላቸውን መግታት አይቻልም። በመፋለም እንጂ። ስለሆነም በዚህም በዚያም ያሉ የቤ/ክ መሪዎች ነገርን አለዝበው በመመካከር መፍትሄ ካልሰጡ ችግሩ ውሎ ካደረ ሌላ መልክና ይዘት ይዞ ይመጣልና ውሉ ይጠፋብናል። በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share