ምድራዊ እረኛ ያጣች ሃገረ ኢትዮጵያ!!

የሰማዩ ፣ የምድሩ ፣ ከምድር በታች ያለው ፣ የውቂያኖሱ ና የሕዋው ሀሉ እረኛ እግዚአብሔር አብ ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ መሆኑ የማያወላውል ነውከላይ በተዘረዘሩት  አምላክ  በልኩ ሰፍቶ በፈጠራቸው ስፍራዎች ሁሉ የሚኖሩት በእሱ አምሳል የተፈጠረውን ሰው ጨምሮ እንስሳትን አዕዋፋትን ፣ አራዊቶችን ወዘተ አቅፎ ፣ ደግፎ ፣ የሚመግበውን አየመገበ፣ የሚያጠጣውና እያጠጣና እስትንፋሰ ሕይወትን ሳይቀር አብርክቶ እያኖረን ያለው ወደር የማይገኝለት አልፋና ኦሜጋ አምላካችን ነው። ክብር ለሱ ይሁን።

ለዚህ ወደር የማይገኝለት ወለታው ለበዛ አምላክ  “ አምላክ እረኛየ ነው አምላኬ እረኛየ ነው” ብለን አክብረን ብናመሰግነው ቢያንስበት እንጂ አይበዛበትም ። በምድር ደግሞ ይመቻችኋል ፣ ይምራችሁ ፣ ፍትህንና ርትህን ያስከብርላችኋል ብሎ ከሰው መካከል መርጦና በእጅ ቀብቶ እረኛ መሪዎችን አምላክ ይሾምልናል ፣ ያሰማራልናል። ሹመት ከእግዚአብሔር ነውና ።

ይህን እንደመግቢያ ካልን ዘንዳ በሃገረ ኢትዮጵያ ላለፉት በተለይ የሰው ልጅ የጋርዮሽ ህይወትን አውልቆ ጥሎ የግል ሃብት ማፍራት ከጀመረ ፣ የመደብ ልዮነት ፣ የበላይና የበታችነት ከተፈጠረ ጀምሮ መዋቅራዊና መዋቅራዊ ባልሆነ መልኩ ጭቃ ሹሞችን ፣ አስተዳዳሪዎቹን፣ መሪዎቹና መንግስትን እንደመንግስት እየተዋቀረ ሃገራችን የተጓዘችብትን የመንግስት ሥርዓቶች ገረፍ ገረፍ አርገን እንዳስስ።

ከአክሱም  ፣ ከዛግዌ ዘመነ መንግስት ከዛም የከተማ ስልጣኔ አሻራ ከተጣለበት የጎንደር መንግስታት መዋለ መዝገብ ጀምሮ እንደሚያሳየው በዛ ያሉ የመንግሥታት ስርዓቶችንና  የሃገር መሪዎችን አይተናል።

የሁሉ ህግጋት መነሻ የሆነውን መፅሃፍ ቅዱሱን ፣ ቁርሃኑን፣ ቶራውንና ፍትሃ ነገሥቱን መሰረት ተደርጎ በተለያየ ጊዜ በቅብሃትም ይሁን በኃይል የሰው ልጅ እንዳይበደል ፣ ሃብቱ እንዳይዘረፍና በሰላም ወጥቶ እንዲገባ በዘመኑ የነበሩ መንግስታት እስከ ስህተታቸው የተቻላቸውን ሁሉ አድርገው አሻራቸውን ጥለው አልፈዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብሔር፣ መንግሥትና ሕዝብ - የፖለቲካ ግብ ማሰለጫ ግንዛቤነታቸው

በተለይ በጎንደር ነገስታት ዘመነ መንግስታት ከሶስት መቶ ዓመታት የንግስና ዘመን እስከ የአንድነት ቀንዲል ከሆኑት የዐፄ ቴዎድሮስ የአገዛዝ ዘመን ድረስ የነበረውን የመንግስት ስርዓት ሂደት አካተን ስናይ ከአርባ ስምንት በላይ የሃገር መሪዎች ተፈራርቀው ሃገረ ኢትዮጵያን አስተዳድረዋል ፣ መርተዋል። እነዚህ መሪዎች የአምላክ ቅብሃትን የተላበሱ ስለነበሩ አብዛኞቹ ሃገረ ኢትዮጵያን በሰላም እየተተካኩ  በማስተዳደራቸው በሕይወት ካለፉ በኋላ  አዕፅመ አካላቸው ሳይቀር በሙዚየም ፣ በየገዳማቱና በየቤተክርስቲያናቱ በክብር ተቀምጠው ይጎበኛሉ ፣ በታሪክ ይወደሳሉ። ይህ ታላቅ መታደልና ክብር ለዘመኑ መሪዎች ትምህርት ሊሆናቸው ይገባል እንላለን።

ቀረብ ባለው የኢትዮጵያ መንግስታት ማለትም በዐፄ ሚኒሊክ ፣ በዐፄ ኃይለሥላሴ ፣ በደርግና ቅጥ ባጣው ፣ ከፋፋይና አረመኔ የወያኔ ያገዛዝ ዘመን እንካኳን  ኢትዮጵያ ውስጥ አንፃራዊ ሰላም ነበር።

የመንግስት ዋና ኃላፊነቶች ምን እንደሆኑ እንደሚከተለው በተለያዩ ፅሃፍት እንደሚከተለው ታትኗል :

“The first and the most important duty of the State are to protect the life and property of its people. The State makes laws regarding life and property. It checks others from interfering into the affairs of the individual. If any individual violates the law of the State, he is punished. The State regulates social life of the individual through laws.”

የመንግስት ዋነኛ ተግባር የሰው ልጅ ሕይወትና ንብረት ይጠበቅ ዘንድ ሕግ ማውጣት ፣ ይህም ሂደት እውን ይሆን ዘንድ ፖሊሶችን ከማሰማራት ባሻገር ፍርድ ቤቶችን በሚገባ በማደራጀት ፍትህና ርዕትህ እንዲሰፍን ማድረግ ነው። በግለሰብ ሕይወት ውስጥ ሌሎች አካላት በኃይል ጣልቃ እንዳይገቡ ዘብ መቆም። ግለሰቦች የሃገርን ሕግጋት ከጣሱ አግባብነት ያለው ቅጣት እንዲያገኙ ማድረግና የሕዝቦች ማህበራዊ ህይወት በሕግ ጥላ ስር ሆኖ እንዲሸራሸር አስፈላጊውን ጥረት ሁሉ መንግስት መከወን እንዳለበት ተመራማሪዎች አንጥረው አስቀምጠውታል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ትንሽ ስለ ‘መለሲ-ዝም’: ከኢህአዴጎች የምስማማበት ነጥብ

በዚህ አግባብ አሁን ያለውን የብልፅግና የኢትዮጵያ መንግስት ስንገመግመው እኒህን ባህርያት የተላበሰ ነው ለማለት የስቸግራል።

መንገድ መስራት ፣ ፖርክ መገንባት ፣ ችግኝ መትከል ወዘተ የተቋማትና የማህበረሰቡ ተግባራት እንጂ የመንግስት ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት ያን ያህል ሚዛን የሚደፋ አይደለም።

በአሁኑ ሰዓት ብዙዎቹ ኢትዮጵያ ናት ብለው የሚያስቡት አዲስ አበባ ብቻ እንደሆነች የመንግስት ትኩረት ፣ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ና የመሰረተ ልማት ዝርጋታወች ሂደት ያሳያሉ ። ዳሩ ከሌለ መሃል ውሽልሽል እንደሚሆን ሊታወቅ ይገባል። አዲስ አበባ የዓለም አቀፍ መስሪያ ቤቶች መናህሪያ ፣ የኢምባሲ ቆንስላ ፅ/ቤቶች መገኛና የቱባ ባለስልጣናት ምሽግ በመሆኗ አንፃራዊ ሰላም እንዲሰፍን ጥረት ተደርጎ ይሆናል። መንግስት ግን የሁሉንም አካባቢ / ክልል እንደምትሉት/ ሰላም ማስፈን ግድ ሊለው ይገባል።

በአሁኑ ሰዓት ወነጀል የሚፈፅመው የትየለሌ ነው፣ ሙስናን እንደ ዕቃ ዕቃ ጭዋታ የሚቆጥረው እርቆ መስፈርት የለውም ፣ ሃገርን የሚያራቁተው ፣ የግል ሃብት የሚያከማቸው እና የሕግ የበላይነትን ከቁብ የማይቆጥረው ወዘተ ጣራ እየነካ መጥቷል።

የህዝብ በሰላም መግባትና መውጣት አሳሳቢ ሁኗል ፣  የውጭ የጎረቤት ሃገር ኃይሎች “እሳት ቤት ገብቶ እንደሚጭር ጎረቤት” እንደአሻቸው በማን አለብኝነት ይገባሉ ይወጣሉ ፣ ንብረት ያወድማሉ ፣ እርሶ እደሩን ያፈናቅላሉ ።

አብዛኞቹ ባለስልጣናት የሕውሃት ቅሪቶች በመሆናቸው “መንግሥት ምንም አያመጣም” በሚል እሳቤ መረን የለቀቀ ስራ እንደሚሰሩ ፣ እራሳቸውን ከሃገሪቱና ከህዝብ በላይ እንደሚቆጥሩ ፣ ለህዝብ ያላቸው ከበሬታ ዝቅ ያለ መሆኑ ፣ ሕግና ስርዓትን ባልጠበቀ መልኩ ሕዝብን የሚያንጓጥጡ ፣ ሕዝብን ለማገልገል ከመጣር ይልቅ እራሳቸውን በተገኘው መልኩ ለመጥቀም የሚታትሩት እንደ ሰማይ ኮከብ በሃገረ ኢትዮጵያ በርክተዋል።

አንድ የቤት አባ ወራ ቤተሰቡን በስርዓት የሚከታተል ፣ ችግር ካለ የሚገስፅ ከሆነ በአካባቢው ህብረተሰብ ይከበራል ፣ ይደመጣል ፣ እንቱታንም ይጎናፀፋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ትምህርቱ፤ ትግሉና ከፍተኛዉ መስዋዕትነት ለዲሞክራሲና ለእድገት ነበር - በቀለ ገሠሠ (ዶ/ር)

መንግስትም የህብረተሰቡን ሰላም ፣ እንድነትና የጋራ እሴት ከጠበቀ ከአምላክ በታች መልካም ምድራዊ እረኛ የሚል መወድስ ያገኛል። ከዚህ በተቃራኒ ከሆነ ግን የሚያዳምጠውም ሕዝብ የለም ፣ በአገሪቱ ሥርዓተ አልበኝነት ይነግሳል ፣ ዝርፊያ ሙስና ይበረክታል፣ ከዚያ አልፎ ጦርነት ፣ መፈናቀል ፣ ሞት ወዘተ በየቦታው እንደ እንጉዳይ ይፈነዳል ፣ አሁን በሃገረ ኢትዮጵያ እየሆነ ያለው ይሄ ነው፣ ይህም የሆነው ሃገራችን ምድራዊ እረኛ ስላላገኘች እንደሆነ ሳይታለም የተፈታ ነው ።

ተዘራ አሰጉ

ከምድረ እንግሊዝ።

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share