እማማ አብስኒያ

 በባዩሽ አበበ
አሜሪካ የምሁሮቻችን ባለአደራ
አሜሪካ እና ካናዳ ባትኖር ኖሮ ኢትዮጲያ ምሁሮቹዋ ሁሉ ያልቁ ነበር፡፡ ከድሮ ጀምሮ አሜሪካ ምሁሮቻችንን እየወሰደ አገሩ ያስቀምጥልናል፡፡ ከሀይለስላሴ የተረፈ፤ ከደርግ የተረፈ ዛሬም እየሸሸ የሚሄደውን አሜሪካ እና ካናዳ ይቀበልልናል፡፡ በትምህርት ላይ ትምህርትም እየጨመሩበት መሰለኝ፡፡ ዲግሪ በዲግሪ፡፡ አይገርምም፡፡ ደስ ይላል፡፡ ይህ አሜሪካ ባይኖር ኖሮ ውነት የኢትዮጲያ ምሁሮች ደዝባቸው ይጠፋ ነበር፡፡ ያልታደለች አገር፤ በአቅሙዋ አስተምራ ለፈረንጅ አገር፡፡ የትግሬው ምሁር፣ የአማራው ምሁር የኦሮሞው ምሁር ……ሁሉም እዛው ነው ያሉት፡፡
እንግዲህ ልብ በሉ፡፡ ምሁር እምሁር አገር ሄዶ ይደነቁራል እንዴ? በተለይ እነዚህ ሶስቱ ኦሮሞ፣ትግሬእና አማራ ንዝንዝ ጭቅጭቅ ታሪክ እየመነዘሩ አላስቀምጥ አላስተኛ ያሉን ዘሮችን ምንአለ ያሉት ምሁሮች እንኩዋን እንደአሉበት አገር እንደሰለጠነው አንድ ሁነው አርአያ ሆነው ቢያሳዩን፡፡ እኔ እኮ እምለው ህዝቡ እኮ አብሮ መሀበር ይጠጣል፤ ሰርግ ይጠራራል፣ ሰው ቢሞት ይቀባበራል፡፡ በናታችሁ እስኪ አሜሪካእና ካናዳ ያላችሁ ምሁር ፕሮፌሰሮች፣ ባለዲግሪዎች ባለ ዶክትሬቶች ትግሬዎች፣ ኦሮሞዎች እና አማራዎች እስኪ ሀ በሉና ከፖለቲካ ተገንጥላችሁ ወጥታችሁ የጥላቻ ፖለቲካ እንዲቀር አስተምሩ አርአያ ሁኑ፡፡ እንዳው እስከዛሬ በተማራችሁት ነው እንዴ ያላችሁት፤ አዲስ ከአሜሪካኖቹ አልተማራችሁም? ካልሆነ ከፖለቲካ ውስጥ ውጡ፡፡ እስኪ በቅ ብቅ በሉ እንያችሁ ምሁሮች አንድ ሆናችሁ ፍቅርን ስትሰብኩ፤ አገር ፍቅርን ስትተረጉሙ፤ ሰላምን ስታስተምሩ፡፡ ያለፈ ታሪክ ብትመልሱት ብትቀልሱት አንዱ ይወደዋል ሌላው ይጠለዋል፡፡ ገባችሁ፡፡ የኢትዮጲያ ኑሮ እኮ ሁሉ በራሱ የተጠመደ ባህል፤ ቅናት ምቀኝነት የተተናወጠው የበዛበት ነው፡፡ መሪ እኮ አሜሪካ ወይም ቻይና አላከልንም፡፡ እናንተ እራሳችሁ መጀመሪያ የትምህርት ቫሊዋችሁን አሳዩን፡፡ ታዲያ የእናንተ መማር ምንድን ነው ለምድራችን ለውጥ የሚያመጣው፡፡ አንድ ሆነው ለእናንተም አርአያ ሆነው የሚኖሩባትን አሜሪካን እናንተንም ወስዶ እንደእነሱ አንድ አድርጎ ደብልቆአችሁ፤ አማራ ኦሮሞ ትግሬ ትላላችሁ፡፡
እኔ ይቅርታ እና አማራ ትግሬ ኦሮሞ ንዝንዛቸው ሰልችቶኛል እና መቸም እዚህ ነገር ውስጥ የተማረ ካለ ዲግሪውን ገዝተህ ነው ወይስ ተምረህ ብዬ ብጠይቅ ወንጀል አይሆንብኝም፡፡ በጣም አስጠልቶኛል በናታችሁ፡፡ ተማርኩ አወኩ የሚል መቼም ይህን ንትርክ ካልተወ እኔ ብሆን እንደገና ትምህርቱ እንዲመረመር አዛለሁ፡፡ እኔ እሻላለሁ በናታችሁ ወረቀቱ የለለኝ፡፡ወይስ ወረቀቱ ነበረኝ እንዴ ወስዳችሁብኝ ይሆን? ምንድን ነው ግራ የሚያጋባችሁ፤ አማራ ስማ፣ ትግሬ ስማ፣ ኦሮሞ ስማ የሰው ዘር ሁለት ነው፡፡ አንዱ ክፉ አንዱ ደግ ነው፡፡ አንተም ዘርህን አጥና፡፡ በውነት ሶስቱ ዘር እኔ እጅ እጅ ብሎኛል፡፡ ማፈሪያ ሁላ፡፡ አብስኒያ ነበርን እኮ ትልቅ፤ ዛሬ አንሳ ኢትዮጲያ ሆነች፡፡ ደግሞ ነገ ማን ልታደርጉዋት ነው? አዳሜ ተመቸህ አልተመቸህ ሚኒሊክ ኢትዮጲያዊ፣ ሀይለስላሴ ኢትዮጲያዊ፣ መንግስቱ ኢትዮጲያዊ፤ መለስ ዜናዊም ትግሬ አድራሻውን የገለጸ ኢትዮጲያዊ ሀይለማርያምም ኢትዮጲያዊ/ሀይለማርያም አድራሻውን ገልጾ እንደሁ ንገሩኝ ደግሞ ከሞተ በሁዋላ ወደአስሩ ዘር እንዳታስጠጉት/ አዎ ውነት ነው አድራሻ ለታሪክ ጥሩ ነው፡፡ ምንትሆኑ፤ የሁሉንም ኢትዮጲያዊነት አትፍቁት እንግዲህ፡፡
ጦጣ አድርገህ ብትስላቸው ወይ አንበሳ፤ ኢትዮጲያዊ የሰው ዘር ናቸው፡፡ ባበህሪቸው ሁሉም የሚወዳቸው የሚጠላቸውም አለ፡፡ ግን እኔ የምወደውን ግድ ውደዱ፣ እኔ የምጠላውን ግድ ጥሉ ብሎ የጅምላ ፍርድ ምን የማይለወጥ አይምሮ ነው? ግን ይህ ሁሉ መሪ ብቻውን ምን እንዲሰራልህ ትፈልጋለህ፡፡ መሪ ካለሰው ምን ይሰራል፡፡ ዛሬ የሚያባላችሁ የጋራ ጠላት በማጣታችሁ ነው፡፡ አሁን አባይን አላስገድብ ብላ ግብጽ ብትነሳ ሁልህም በነቂስ ትወጣለህ፡፡
እኔም ኢትዮጲያዊት ነኝአሃ ልቤን አውቀዋለሁ፡፡ አረቦቹ ኢትዮጲያን ጨረሱ ቢባል ላንቃዬ እስከሚደርቅ የጮሁኩት እንደእናንተ የጋራ ጠላት ቢሆኑ እኮ ነው፡፡ ገዥውም ፓርቲ ተቃዋሚም እኮ ብትናከሱም ግን ሁሉም አለሁ ብሎ በአረብ አገር ታይቶአል፡፡ ታዲያ ምነው የውስጥ ትብብር አሳጣችሁ፡፡ እልከኛ ሁላ፡፡ ዘሬ የተለያዬ ነው ብትል መልክህ እና ባህሪህ ግን ፎቶ ኮፒ፡፡ ምን ትሆን፡፡ ባልመችህም ኢትዮጲያዊት ነኝ፡፡ „ጣት ገማ ተብሎ ቆርጦ አይጣልም“፡፡ ምን አለ ሰልጥናችሁ ብትሞቱ፡፡“ እኔ ኦሮሞ ነኝ፡፡ እኔ ትግሬ ነኝ፡፡ እኔ አማራ ነኝ“፡፡ ከተማረ ሰው ይህ ቃል ቢወጣ፤ ትምህርት የተማርከው ለማለፍ እንጂ ለእውቀት አልነበረም ማለት ነው፡፡ እርሻ የምታጠጣበት የመስኖ ውሃ ይመሰል ህዝብ እየከፋፈላችሁ የምትመሩት ምሪት መቸም ይህን የተማረ አይስራው፡፡ መርገም ሆኖብህ የተማረ ደንቆሮ ሆነህ ዲዳ ሆነህ እንዳትቀር፡፡ እወዳችሁዋለሁ፡፡ ምን ላድርግ የሰላም ፍቅር ይዞኝ እኮ ነው፡፡ ያስቀየምኩት ካለ በጌታዬ በእየሱስ ክርስቶስ ስም ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡
በቸር
ተጨማሪ ያንብቡ:  የወያኔ አመራሮችን ግፍ ለማጋለጥ እጄን ሰጠሁ ESAT [እውነት እና ንጋት] Oct 26 2022
Share