April 28, 2013
12 mins read

በቬጋስ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን በስራ ማቆም አድማ ላይ ያሉ የታክሲ አሽከርካሪ ወገኖቻቸውን ለመርዳት በአንድ ላይ እንደሚቆሙ ገለጹ

የጋራ ኮሚኒቲ ለማቋቋም ሀሳብ ቀርቧል

በቬጋስ የሚገኙና በሁለት የከተማዎ ታላላቅ የታክሲ ኩባንያዎች ፈራይስና የሎ ቼከር ስታር የሚሰሩና ቁጥራቸው ከአንድ ሺህ በላይ የሚሆኑ የስራ ማቆም አድማ ተሳታፊዎችና በተቃራኒው የስራ ማቆም አድማውን ሳይቀላቀሉ የቀሩ ወገኖች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት በማርገብ የተጀመረው ትግል ውጤት እንዲያመጣ የተጠራው በኢትዮጵያውያንና ኤርትራዊያን ድጋፍ ስብሰባ ባለፈው ረቡዕ አፕሪል 24/2013 በከተማዋ ተካሔደ። የማህበረሰቡ አባላት ትግሉ ውጤት እንዲያመጣ ከአሽከርካሪዎች  ጎን እንደሚቆሙ ገልፀዋል። የስብሰባው አዘጋጆች የሥራ ማቆም አድማ ተሳታፊዎችን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ምክንያቶችን በመስጠት ከኩባንያው ጎን በመቆም

የኢትዮጵያውያንና የኤርትራውያን የድጋፍ ኮሚቴ በሚል በራሳቸው ፍላጎት የተሰባሰቡ ከማህበረሰቡ የተውጣጡና ከታክሲ ማሽከርከር ስራ ውጭ ያሉ ወገኖች በጠሩት በዚህ ስብሰባ በአሁኑ ወቅት በስራ ላይ ባሉና በተቃውሞ አድራጊዎቹ መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት በውይይት የመፍታት፣የተጀመረው የመብት ጥያቄ ተገቢውን ትኩረት እንዲያገኝ ድጋፍ እና ምክር መስጠት መሆኑን ኮሚቴውን በመወከል አቶ ሙሉነህ ጠና ተናግረዋል። በስራ ላይ ያሉ በተለይ በርካታ የፍራይስ አሽከርካሪዎች የወገናቸውን የመብት ትግል እያስተጓጎሉ  በመሆኑ ከድርጊታቸው ተቆጥበው የስራ ማቆም አድማውን እንዲቀላቀሉ የስብሰባው አዘጋጆች የመሸምገል ሃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።

በከተማው በሚገኘው ፓላስ ስቴሽን ካዚኖ በተካሄደው በዚህ ስብሰባ ላይ ቁጥራቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራዊያን የማህበረሰቡ አባላት የተገኙ ሲሆን በሥራ ማቆም አድማ ላይ የሚገኙትን ለመደገፍ መጠነኛ የገቢ ማሰባሰቢያ የሚሆን ትኬት ተዘጋጅቶ ለሽያጭ ቀርቧል።

በስብሰባው ላይ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የኔቫዳ የዩታሃና  የአሪዞና ሊቀ ጰጳስና የቅዱስ ሲኖዶሱ ም/ዋና ጸሀፊ እና ከእስልምና ዕምነት ተከታዮችም ኡስታዝ ኑር ሐሰን  በስብሰባው ላይ ተገኝተዋል።  በአሁኑ ወቅት በከተማዋ በርካታ ወገኖች የሥራ ማቆም አድማ ላይ መሆናቸውንና በሥራ ላይ ካሉ ወገኖች ጋር መካከል በአንዳንዶች የተጀመረው የእርስ በእርስ መሰዳደብ እያደገ ወደ ግጭት እንዳያመራ ስጋታቸውን ገልፀዋል። በውይይት ችግሩ ተፈቶ የሥራ ማቆም  አድማው መነሻ የሆነው የመብት ጥያቄ  በጋራ ትግል መፍትሔ እንዲያገኝ ጠይቀዋል። ጠበቃ ማቆምም ቢያስፈልግ በአንድ ላይ መምከር በአንድ መቆም ይገባል ብለዋል።

“የመብት ጥያቄ የዴሞክራሲ ጥያቄ ነው ማንም ሊደግፈው ይገባል>> ያሉት አቶ ረዳ መሀሪ የአፍሪካ ኮሚዩኒቲ ሴንተር ማኔጅንግ ዳይሬክተር ሲሆኑ ትውልደ ኢትዮጵያውያንም ሆኑ ኤርትራዊያን ተደራጅተን የድምፆቻችንን ዋጋ ማሳየትና ተደማጭነት ማግኘት አለብን ሲሉ ከወቅቱ የስራ ማቆም አድማ በላይ ማሰብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

አቶ ሽመልስ ደረሱ የየሎ ቼከር ስታር የታክሲ አሽከርካሪዎች የሥራ ማቆም አድማ አስተባባሪ ከማርች 3 ጀምሮ በሥራ ማቆም አድማው ላይ መቆየታቸውን ገልፆ የፍራይስ አሽከርካሪዎችም ከማርች 29 ጀምሮ በተመሳሳይ ሥራ ማቆም አድማ ላይ ቢኖሩም የተጀመረው ትግል እንዳይሳካ የገዛ ወገኖቻችን እንደ ጠላት እየተደዋወሉ አትጫኑ ካልናቸው  ቦታዎች  እንኳ ይጭናሉ ሲሉ ወቅሰዋል።

<<ከሐበሻ ባህል ውጭ የሆነ የገዛ ወገናችን እኛ የስራ ማቆም አድማ ላይ እያለን ከኩባንያው ጎን ቆሞ መስራቱ ሳያንስ እኛን ሊሰድብ የማይታየውን አካሉን አሳየን።ካሜራ አለ አጋለጠው>>  ሲሉ በምሬት የገለፁት አቶ ሽመልስ ይህንን ድርጊት የፈፀመው በአሁኑ ወቅት ከስራ ተባሮ በየትኛውም ኩባንያ እንዳይቀጠር መደረጉን አመልክቷል።

ከስራ ማቆም አድማ ተሳታፊዎች ውስጥ የአራት ልጆች አባት ባለቤቱ የማትሰራ ጭምር እያሉ ሚስቶቻቸው በተለያየ ቦታ የሚሰሩ ጭምር ከኩባንያው ጎን ቆመው የጀመርነውን የስራ ማቆም አድማ እንዳይሳካ ተሰደብን በሚል ምክንያት የገዛ ወገኖቻችን እያጠቁን ነው ብሏል።

“የኢትዮጵያና የኤርትራ ኮሚኒቲ የሚባል መነጣጠል ቆሞ አንድ ኮሚኒቱ ሊኖረን ይገባል ” ሲሉ ሃሳብ ያቀረቡት አቶ ሽመልስ ከሁለቱ ኩባንያ በስራ ላይ ያሉ ወገኖቻችን እንዲቀላቀሉን የሚሳደቡም ሰዎች ስድብ ቢያንስ ሙሉ ለሙሉ ለአንድ ሳምንት እንዲቆምና ሳምንቱ የፍቅር ሳምንት ሆኖ የተጀመረው የመብት ትግል ውጤት እንዲያመጣ እየሰሩ ያሉት ይቀላቀሉን ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል። ማህበረሰቡ ኢትዮጵያዊያን ኤርትራውያን እየተባባሉ ሳይከፋፈል በአንድ ላይ ለመብታችን እንቁም እስቲ እጅ ለእጅ እንያያዝ ሲሉ ባቀረበው ጥሪ መሰረት የሀይማኖት አባቶችን ጨምሮ ሁሉም ተሳታፊዎች እጅ ለእጅ በመያያዝ አንድነትን ለማሳየት ሞክረዋል። ለሰብሰባው አዘጋጆች የሚሰሩት ሰዎች ላይ ጫና እንዲፈጥሩ ጠይቀዋል። <<ነፃነት ባለበት አገር በቬጋስ በባርነት የምንኖር የታክሲ ሾፌሮች ነን ።ባርነት በቃን ብለን ወጥተናል አሁንም አልረፈደም  የቀሩት ወገኖቻችን ይቀላቀሉን >> ሲሉ አጽንዎት ሰጥተዋል።

ዮናስ ተሰማ በስራ ማቆም አድማ ላይ ያሉት የፍራይስ አሽከርካሪዎች ተወካይ በበኩሉ <<ትላንት መብታችን ተነካ፣ ለምን የስራ መቆም አድማ አንወጣም ሲሉ ከነበሩ ብዙዎቹ በሥራ ላይ ናቸው። በሰሩት ተግባር ሊያፍሩ ይገባል ያለ ሲሆን ሌላው በስራ ማቆም አድማ ላይ ያለ ልጁን በፀሐይ ብርሃን የሚያሳድግ ይመስል የተለያዩ ምክንያት እየሰጡ ከኩባንያው በላይ እየጎዱን ያሉት በስራ ላይ ያሉና ተቃውሞውን ያልተቀላቀሉ ወገኖቻችን ናቸው ብሏል።

በስብሰባው ላይ የተሳተፉ የኢትዮጵያና የኤርትራ ኮሚኒቲ ተወካዮች በየበኩላቸው ንግግር ያደረጉ ሲሆን የተጀመረው የመብት ትግል ውጤታማ እንዲሆን መተባበሩ ተገቢ መሆኑን ገልፀዋል።

ከሥራ ማቆም አድማ ተሳታፊዎች አንዱ የሆኑት የኤርትራ ኮሚኒቲ ሊቀመንበር አቶ ዓለም በውስጥ ሆነው የሚሰሩና ተቃውሞውን ያልተቃላቀሉ ኢትዮጵያውያን ና ኤርትራዊያንን በአንድነት ወቅሰው ስድብ የሚባለውን በግላቸው እንደማይደግፉ ነገር ግን የእያንዳንዱ ወጣት አፍ ስለማንቆልፍ የተጀመረው የመብት ትግል እንዳይሳካ ከሚሰሩትም የሚሳደቡ ስላሉ ተሰደብኩ የሚለው ምክንያት ተቀባይነት እንደሌለው ገልፀዋል።

የአቤ ጉበኛን አልወለድም ለንግግራቸው ማጣቀሻነት ያነሱት የኤርትራው ኮሚኒቲ ሊቀመንበር በዚያ መፅሐፍ ውስጥ “ወገን ሲባል ያገር ሰው ሲባል ከወገኑ ጋር የሚቆም አንጂ ነፃነትህና መብትህን የሚገፍ ወገንህ ግን ጠላትህ ነው ይባላል” የሚል ጥቅስ  አንስተው ከኩባንያው ጋር በመቆም ባርነት በቃን ላልነው ወገኖች በተቃራኒው የቆሙት ግን <<እኔ የማርክ ጄምስ ባሪያ ነኝ>> የሚል ቲሸርት አሰርተው ለብሰው ታክሲያቸውን ይንዱ ሲሉ በምሬት ተናግረዋል።

ከስብሰባው ተሳታፊዎች መካከል በስራ ማቆም አድማ ላይ ያሉ አንዳንዶች በሰጡት አስተያየት የስብሰባው አዘጋጆች ውስጥ ሆነው የሚሰሩ ሰዎችን አስቀድመው ስብሰባ መጥራት እንደነበረባቸው በመግለፅ  በማህበረሰቡ ውስጥ ሰላም የሚኖረው በሥራ ላይ ያሉ ሲቀላቀሉዋቸው መሆኑን ጠቅሰዋል።

comment pic
Previous Story

ክፉን ሰውና ክፋተኝነትን እንዴት እናውቃለን? በይሄይስ አእምሮ

eotc22
Next Story

ሕጋዊው ቅዱስ ሲኖዶስ በአማርኛ ተናጋሪ ወገኖቻችን ላይ እየተካሄደ ያለውን የዘር ማጽዳትና ማጥፋት ዘመቻ አስመልክቶ ጥሪ አቀረበ

Latest from Blog

“መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የሚለው የዲያስፖራ ከንቱ አታካራ! – ክፍል ሁለት

በላይነህ አባተ (abatebelai@yahoo.com) በአንዳንድ ስብሰባዎችና የሕዝብ መገናኛ መድረኮች የሚታየው የአንዳንድ ዲያስፖራዎች  “መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የበከተ ከንቱ አታካራ በልጅነታችን ወላጆቻችን ትምህርት እንዲሆነን ይተርኩልን የነበረውን ከጫጉላ ወጥተው ጎጆ ለመመስረት የታከቱ ሁለት ያልበሰሉ ባልና ሚስትን ታሪክ

መነሻችን አማራ መድረሻችን አማራ እና ወያኔያዊ መሠረቱ

የማይወጣ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል። የዛሬን አያድርገውና የትግሬ ልሂቆች “ትግራይ የጦቢያ መሠረት ናት ።  ጦቢያ ያለ ትግራይ፣ ትግራይ ያለ ጦቢያ ሊታሰቡ አይችሉም” በማለት ጦቢያዊ ከኛ ወዲያ ላሳር እያሉ አለቅጥ ይመጻደቁ፣ ይኩራሩ፣ ይታበዩ ነበር። ወያኔ

አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው ወንጀሎች ጥፋተኛ ተባሉ

ለአመታት በእረስር ላይ የሚገኙት  አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱባቸው የጥላቻ ንግግር ማሰራጨት እና የዕርስ በዕርስ ግጭት መቀስቀስ ወንጀሎች ጥፋተኛ መባላቸው ታውቋል፡፡ አቶ ታዲዮስ ታንቱ በተከሰሱበት ክሶች በዛሬ ቀጠሮ የጥፋተኝነት ፍርድ የሰጠው የፌደራል ከፍተኛ

ከ”ችርቻሮ” ድል አልፎ ለመሄድ የአንድነት አስፈላጊነት – ግርማ ካሳ

በአሁኑ ጊዜ ሁለት የፋኖ አሰላለፎች አሉ:: መኖር ያልነበረበት:: አንከር ሜዲያ ከሁለቱም አሰላለፎች፣ ሁለት ፋኖ መሪዎች ጋር ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ ሁለቱን አደመጥኩ፡፡ በሰማሁት ነገር ተደስቻለሁ:: ትልቅ ተስፋ እንድሰንቅም አድርጎኛል:: የአማራ ህዝባዊ ድርጅት የፖለቲካ
Go toTop